Site icon

ሉቃስ 21፡1-38

ትንቢቶች በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ሰዎች በተሳሳተ መንገድ ከሚረዷቸው የሥነ ጽሑፍ ዐይነቶች መካከል የሚመደቡ ናቸው። ትንቢት የተሰጠው ወደፊት ስለሚፈጸሙት ክስተቶች ዝርዝር መረጃዎችን እንድናገኝ ነውን? እንደዚያ ከሆነ፣ የእያንዳንዱን ትንቢት ትርጉም አስመልክቶ የተለያዩ አመለካከቶች የሚንጸባረቁት ለምንድን ነው? ምንም እንኳ ብዙዎቻችን ነቢይ ወደፊት የሚከሰተውን አስቀድሞ የሚተነብይ አገልጋይ እንደሆነ ብናስብም፤ በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ነቢይ ከእግዚአብሔር ዘንድ መልእክት የተቀበለ ሰው ነው። አንዳንድ ጊዜ መልእክቱ የወደፊት ክስተቶችን የሚመለከት ሊሆን ይችላል፤ ብዙውን ጊዜ ግን በዘመኑ ለነበሩት ሰዎች የሚያገለግል ነው። ወደፊት ነገሮች እንዴትና መቼ እንደሚፈጸሙ የሚያብራሩ ዝርዝር መረጃዎችን የያዙ ትንቢቶች ጥቂቶች ናቸው። በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ የምናገኛቸው ትንቢቶች ዋናው መልእክት ምንም ይሁን ምን እግዚአብሔር ነገሮችን በመቆጣጠር ላይ እንደሚገኝ ማሳየት ነው። እግዚአብሔር ሙሉ በሙሉ ታሪክን በመቆጣጠር ላይ ነው። አገሮችና ነገሥታት በእርሱ ቁጥጥር ሥር ናቸው። መጨረሻው ደግሞ በመከራ ጊዜ ታምነን የምንወርሰው የእግዚአብሔር መንግሥት ነው።

በሉቃስ 21 ላይ ነቢይ የሆነው ኢየሱስ ለተከታዮቹ ወደፊት የሚመጣውን ዘመን አንዳንድ ባሕርያት ነግሯቸዋል። ምንም እንኳ ከኢየሱስ ዘመን ጀምሮ እስከ ዳግም ምጽአቱ ድረስ ከተተነበዩት ነገሮች መካከል አንዳንዶቹን መረዳት ብንችልም፣ እነዚህ ነገሮች መቼ ወይም እንዴት እንደሚፈጸሙ አናውቅም። ይሁን እንጂ ኢየሱስ ዳግም ተመልሶ በመምጣት በታማኝነት የሚጠባበቁትን ወደ መንግሥተ ሰማይ እንደሚወስዳቸው እናውቃለን። ስለሆነም ዋናው ጥያቄ፣ «እኛን ለመውሰድ በሚመለስበት ጊዜ በታማኝነት በፊቱ ስንመላለስ ያገኘን ይሆን?» የሚለው ነው።

  1. ኢየሱስ ለደቀ መዛሙርቱ እግዚአብሔር መስጠትን እንዴት እንደሚመለከት አስተማረ (ሉቃስ 21፡1-4) እግዚአብሔር አንድን ስጦታ የሚመዝነው በትልቅነቱ ወይም በትንሽነቱ ሳይሆን፣ ስጦታው ልባዊ ሆኖ በመሰጠቱ ነው። ስለሆነም የዚያች መበለቲቱ አሥር ሣንቲም (እኛ እንደ አንድ ሣንቲም የምንመለከተውና ምንም የማይጠቅም የአይሁዶች ገንዘብ)፣ በእግዚአብሔር ዐይን ፊት አንድ ነጋዴ ከሚሰጠው መቶ ብር በላይ የሚገመት ነበር።

የውይይት ጥያቄ፡- ለእግዚአብሔር በልግስና በመስጠትህ ምክንያት የገንዘብ አቅምህ ስለተጎዳበት ጊዜ ተናገር።

  1. ኢየሱስ በሚመለስበት ጊዜ ስለሚከሰቱት ምልክቶች ተናገረ (ሉቃስ 21፡5-38)

ኢየሱስ ስለ ቤተ መቅደሱ መፍረስ የተናገረው አሳብ፥ ደቀ መዛሙርቱ ቤተ መቅደሱ ስለሚፈርስበት ጊዜና ከዚያ በፊት ስለሚከሰቱት ምልክቶች እንዲጠይቁ አነሣሣቸው። ኢየሱስ በትንቢቱ በቅርብ ጊዜ ውስጥ የሚፈጸሙትን (የኢየሩሳሌም በ70 ዓ.ም. መደምሰስ)፣ በዘመናት ሁሉ የሚሆነውን የሕይወት ዕጣ ፈንታና ኢየሱስ ዳግም ሊመለስ ሲል በመጨረሻ ዘመን የሚከሰቱትን ነገሮች በሙሉ አካትቷል። ምሑራን ኢየሱስ በተለያዩ ክፍሎች የሚጠቅላቸው ነገሮች በየትኛው ጊዜ እንደሚፈጸም በትክክል ስለማያውቁ በአሳብ አይስማሙም። አስፈላጊው ነገር እያንዳንዱ ትንቢት የትኛውን ጊዜ እንደሚያመለክት ማወቁ ሳይሆን፣ ኢየሱስ ደቀ መዛሙርቱ የጊዜውን ባሕርይ እንዲያውቁ ማዘጋጀቱ ነው። በተጨማሪም ኢየሱስ እስከ መጨረሻው ድረስ ነገሮችን ሁሉ እንደሚቆጣጠር መረዳቱ ጠቃሚ ነው። (ከእነዚህ ትንቢቶች የተወሰዱትን የተለያዩ ግንዛቤዎች ማቴዎስ ምዕራፍ 24 ላይ የተሰጠውን ማብራሪያ ተመልከት።)

ሀ. መጨረሻው የኢየሩሳሌም መፍረስም ይሁን ወይም የዘመን መጨረሻ ገና ከብዙ ዘመን በኋላ የሚፈጸም ስለሆነ፣ ደቀ መዛሙርቱ በፍጥነት ይሆናል ብለው መጨነቅ አልነበረባቸውም። በመጀመሪያ ሰዎችን የሚያታልሉ ሐሰተኛ መሢሖች ከመነሣታቸውም በላይ፣ ብዙ ጦርነቶች ይካሄዳሉ። ኢየሩሳሌም ልትፈርስ አቅራቢያ የተለያዩ መሢሖች የተነሡ ሲሆን፣ ብዙ ውጣ ውረዶችና ጦርነቶችም ተካሂደው ነበር። ኢየሱስ በትምህርቱ ላይ ለማመልከት የፈለገው ይህንኑ ሁኔታ ሳይሆን አይቀርም። ወይም ደግሞ ሊመለስ ሲል የሚከሰቱትን ሁኔታዎች መጥቀሱ ይሆናል። (ይህ እጥፍ ፍጻሜ በመባል ይታወቃል።)  

ለ. በአገሮች፣ በተፈጥሮና በሰማይ ላይ እንኳ ሳይቀር የመጨረሻውን ዘመን የሚያሳዩ ብጥብጦች ይፈጸማሉ።

ሐ. ፍጻሜው ከመድረሱ በፊት፣ የኢየሱስ ተከታዮች ከአይሁዶች (ምኩራብ) እና ከአሕዛብ (ነገሥታት፣ ጎዥዎች) ብዙ ስደት ይደርስባቸዋል፡ በተጨማሪም ለማመን ከማይፈልጉ ወገኖች ብርቱ ቤተሰባዊ ስደት ይከሰታል። ሰዎች ክርስቲያኖችን ይጠላሉ። ነገር ግን እግዚአብሔር ከእኛ ጋር ስለሚሆን፣ መንፈስ ቅዱስ ምን እንደምንል ያስተምረናል። ኢየሱስ ሳይፈቅድ ከራሳችን ፀጉር እንኳ አንድ አይነቀልም። የኢየሱስ ተከታዮች የሆንን ሁላችንም በእምነታችን ጸንተን ለመኖር መቁረጥ ይኖርብናል። ይህ ለዘላለም ሕይወት ያበቃናልና!

መ. ኢየሩሳሌም በሠራዊት በምትከበብበት ጊዜ፣ ውድመቱ ፈጣንና ዘግናኝ ይሆናል። ይህም በኢየሩሳሌም ከሮም ሠራዊት የሚሰነዘረውን አደጋ ወይም በመጨረሻው ዘመን የሚደርስባትን ውድመት የሚያመለክት ሊሆን ይችላል። ሮም ኢየሩሳሌምን ከደመሰሰች በኋላ፣ እግዚአብሔር እስራኤልን ዳግም እስኪጎበኝ ድረስ አሕዛብ ከተማይቱን ይቆጣጠሯታል። (ይህም የአሕዛብ ዘመን በመባል ይታወቃል።)

ሠ. ኢየሱስ ሊመለስ ሲል በፀሐይና በጨረቃም በከዋክብትም ምልክት ይሆናል። (ማስታወሻ፡ አንዳንድ ምሑራን ይህ የአገርችን ከፍተኛ ውዝግብ እንጂ በፀሐይ፣ በጨረቃና በከዋክብት ላይ የሚደርሰውን ሁኔታ አያመለክትም ይላሉ።)

ረ. ኢየሱስ በክብር ደመና ይመለሳል። ይህ ከዚህ ክፉ ዓለም ነፃ መውጣታችንን የሚያመለክት ይሆናል።

እንግዲህ ደቀ መዛሙርቱ ምን ማድረግ ይኖርባቸዋል? ኢየሱስ ስለ መጨረሻው ዘመን በሚያስተምርበት ጊዜ ሁሉ ደቀ መዛሙርቱን ያስተምር ወደነበረው አሳብ ይመለሳል። ኢየሱስ እስኪመለስ ድረስ በታማኝነት ልናገለግለው ይገባል። በዓለም ፍቅር ተተብትበን ኢየሱስን ለመጠበቅ መቸገር አይገባንም። ወይም ደግሞ ከሚገባው በላይ ተጨንቀን ተስፋ መቁረጥ አይገባንም። ነገር ግን የኢየሱስን ዳግም ምጽአት ተግተን እንድንጠብቅና በእምነታችን እንድንጸና አጥብቀን መጸለይ ይገባናል። የኢየሱስ ተከታዮች የምጽአቱን ጊዜ ሳይዘነጉ ተግተው መጠበቅ ይሻሉ።

የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) በቅርቡ ስለ መጨረሻው ዘመን ሲሰበክ የሰማኸው መቼ ነው? ለ) የኢየሱስን ምጽአት እየጠበቅህ ሳለህ የምታከናውናቸው ተግባራት ምንድን ናቸው? ሐ) የኢየሱስ መመለስ የጸሎት ሕይወትህን የሚነካው እንዴት ነው?

(ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የአዲስ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)

Exit mobile version