Site icon

የቲቶ መልዕክት ልዩ ባሕርያት እና አስተዋጽኦ

የቲቶ ልዩ ባሕርያት

1) ቲቶ ስለ ክርስቶስ አምላክነት ግልጽ የሆነ ትምህርት ያቀርባል። በቲቶ መልእክት ውስጥ ክርስቶስ ታላቅ አምላክና አዳኝ ተብሎ ተጠቅሷል። ይህም ብዙውን ጊዜ ለእግዚአብሔር አብ የሚያገለግል ስያሜ ነው (ቲቶ 2፡13)።

2) የቲቶ መጽሐፍ በ1ኛ ጢሞቴዎስ ውስጥ የሚገኙትን አብዛኞቹን ጉዳዮች ይዳስሳል። የሽማግሌዎች ምርጫ፥ የሴቶችና የባሪያዎች ሚና፥ እንዲሁም ሐሰተኛ ትምህርቶችን መከላከል የሚሉ ዐቢይ ነጥቦች በሁለቱም መጻሕፍት ውስጥ ይገኛሉ።

3) ቲቶ ከማናቸውም የጳውሎስ መልእክቶች በላይ በተገቢው እምነትና መንፈሳዊ ባሕሪ መካከል ያለውን ግንኙነት በግልጽ ያሳያል። ከተገለጹት ሐረጎች መካከል «መልካም ባሕሪ» የሚለው ይገኝበታል። ይህም የክርስቶስን ስም የሚጠሩ ሰዎች እንደ እግዚአብሔር ልጆች ሊመላለሱ እንደሚገባ ያሳያል።

4) ቲቶ ወንጌል ምን እንደሆነ ጠቅለል አድርጎ ያቀርባል። በቲቶ 2፡11-13 የጸጋው ወንጌል ምን ዓይነት ውጤቶችን እንደሚያስከትል ተገልጾአል። ወንጌል፥ መንፈሳዊ ያልሆኑትን ባሕሪዎች እንዳንከተልና መንፈሳዊ አኗኗርን እንድንሻ ያደርገናል። በቲቶ 3፡4-8፥ ጳውሎስ መንፈስ ቅዱስ በክርስቶስ ወደሚያምኑት ሕይወት ስለሚያመጣቸው እንደ ምሕረት፥ ድነት (ደኅንነት) እና ተሐድሶ በመሳሰሉት ነገሮች ላይ ያተኩራል። አሁንም ጳውሎስ ትክክለኛ እምነት እንዴት ወደ መንፈሳዊ አኗኗር እንደሚመራ አጽንኦት ሰጥቶ ገልጾአል።

የቲቶ አስተዋጽኦ

ይህ የቲቶ መልእክት አንድ የቤተ ክርስቲያን መሪ በአዲስ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ ሊያደራጃቸው ስለሚገቡ የተለያዩ ነገሮች የሚናገር ተግባራዊ መልእክት ነው። በመሆኑም፥ እነዚህ ነገሮች መሪዎች ጤናማ ቤተ ክርስቲያን ለመመሥረት የሚጠቀሙባቸውን መሠረታዊ እውነቶች ያቀርባሉ። ጳውሎስ ጢሞቴዎስ አዲሷን ቤተ ክርስቲያን እንዴት እንደሚያደራጅ በሚመክርበት ጊዜ ግልጽ አስተዋጽኦ ከመከተል ይልቅ ከርእሰ ጉዳይ ወደ ርእሰ ጉዳይ እያለፈ የተለያዩ ትምህርቶችን ያቀርባል። የቲቶ መልእክት አጠቃላይ መዋቅር የሚከተለውን ይመስላል፡

  1. ብቃት ያላቸውን መሪዎች መሾም (ቲቶ 1፡1-9)

ሀ) መግቢያ (ቲቶ 1፡1-4)

ለ) በቤተ ክርስቲያን ውስጥ ተገቢውን አመራር መመሥረት (ቲቶ 1፡5-9)።

  1. የሐሰት ትምህርቶችን ስለመከላከል (ቲቶ 1፡10-16)
  2. ለሁሉም የዕድሜ ክፍሎች ግልጽ ትምህርት በማቅረብ ቤተ ክርስቲያንን ማጠናከር (ቲቶ 2፡1-10)

ሀ) አረጋውያንን ማስተማር (ቲቶ 2፡1-2)

ለ) አረጋውያን ሴቶችን ማስተማር (ቲቶ 2፡3-5)

ሐ) ወጣት ወንዶችን ማስተማር (ቲቶ 2፡6-8)

መ) ባሮችን ማስተማር (ቲቶ 2፡9-10)

4 የጸጋው ወንጌል የተለወጠ አኗኗርን እንደሚያስከትል ማስተማር (ቲቶ 2፡11-3፡5)

ሀ) ወንጌል አማኞች መንፈሳዊ ያልሆኑትን ልምምዶች እንዳይከተሉ ያደርጋል (ቲቶ 2፡11-3፡8)፡፡

ለ) የቤተ ክርስቲያን መሪ ከሐሰተኛ አስተማሪዎች ጋር ማቆሚያ የሌለው ክርክር መግጠም የለበትም (ቲቶ 3፡9-11)፡፡

ሐ) ድምዳሜ (ቲቶ 3፡12-15)

(ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የአዲስ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)

Exit mobile version