Site icon

1ኛ ዮሐ 5፡1-21

፩. እውነተኛ አማኞች እና አስተማሪዎች ከክርስቶስ ጋር ትክክለኛ ግንኙነት ይኖራቸዋል (1ኛ ዮሐ 5፡1-12)

አብዛኞቹ እውነቶች እንዳልተበጠሰ ሰንሰለት ናቸው። እግዚአብሔር አብን ለመውደድ ከፈለግህ፥ በኢየሱስ ክርስቶስ ማመን እና እርሱንም መውደድ ይኖርብሃል። ወልድን በማመን ለአብ ያለህን ፍቅር ትገልጻለህ። በወልድ ማመንህን እና ለእርሱ ያለህን ፍቅር ደግሞ ሰዎችን በመውደድ እና የእርሱን ትእዛዛት በመፈጸም ታሳያለህ። ዓለምን ለማሸነፍ የሚያስችልህ ኃይል የሚፈልቀው ከዚሁ የማይበጠስ ሰንሰለት ውስጥ ነው። ከዚህ ሰንሰለት ውስጥ አንደኛው መገጣጠሚያ ቢበጠስ፥ ችግሮች መከሰት ይጀምራሉ። እግዚአብሔር አብን ባንወደው ወይም ባናምነው፥ በክርስቶስ ባናምን፥ ወይም በፍቅር ባንመላለስ፥ በእምነታችን ውስጥ አንድ ችግር እንደ ተከሰተ ከእነዚህ ሁሉ መረጃ ዎች መመልከት ይቻላል።

የውይይት ጥያቄ፡– ሀ) ከእነዚህ የሰንሰለቱ መገጣጠሚያዎች አንዱ ብዙ ወንጌል አማኝ ክርስቲያኖች የሚሸነፉባቸው የትኞቹ ናቸው? ለ) «ኢየሱስ ብቻ» የሚሉ የእምነት ክፍሎች የሚሸነፉት የትኛውን እውነት በመሳሳታቸው ነው?

ዮሐንስ የሚከላከለው ሐሰተኛ ትምህርት ኖስቲሲዝም በመባል ይታወቃል። ኖስቲሲዝም ክርስቶስ ፍጹም አምላክ ወይም ፍጹም ሰው እንዳልሆነ ያስተምራል። ነገር ግን ዮሐንስ ክርስቶስ ፍጹም ሰውና ፍጹም አምላክ ነው የሚሉት ሁለቱም አሳቦች ወሳኝ መሆናቸውን ይናገራል። ዮሐንስ አማኞች ክርስቶስ አምላክ እንደሆነ እንዲያምኑ፥ «ኢየሱስም የእግዚአብሔር ልጅ እንደሆነ ከሚያምን በቀር ዓለምን የሚያሸንፍ ማን ነው?» ሲል ይጠይቃል። ዮሐንስ በተጨማሪም አማኞች በክርስቶስ ፍጹም ሰብአዊነት እንዲያምኑ ያበረታታል። ዮሐንስ ይህን እውነት የገለጸው ክርስቶስ በመንፈስ፥ በውኃና በደም እንደ መጣ በመመልከት ነው። (ዮሐንስ ምናልባት በሁለት ወይም በሦስት ምስክሮች ነገር እንደሚጸና የሚናገረውን የብሉይ ኪዳን ግንዛቤ እየተጠቀመ ይሆናል። እነዚህም ሦስት ምስክሮች ክርስቶስ ሰው መሆኑን እንደሚያመለክቱ ያስረዳል።)

እነዚህን ጥቅሶች ለመረዳት ሐሰተኛ አስተማሪዎቹ ሲያስተላልፉ የነበረውን መልእክት መረዳቱ ጠቃሚ ነው። እነዚህ ሰዎች መለኮታዊ መንፈስ የሆነው ክርስቶስ በጥምቀት ጊዜ በሰብአዊው ኢየሱስ ላይ እንደ ወረደ እና ከመስቀል ላይ ሞቱ በፊት ተመልሶ እንደ ሄደ ይናገራሉ። በመስቀል ላይ የሞተው ሰብአዊው ኢየሱስ ብቻ ነው ሲሉ ያስተምራሉ። ዮሐንስ ይህንን ትምህርት በመቃወም ክርስቶስ ከጥምቀቱ እስከ ሞቱ ድረስ አምላክም ሰውም እንደ ነበር ያስረዳል። ለዚህም ሦስት ነገሮችን በምስክርነት ይጠቅሳል።

ሀ) ውኃ፡- ምሁራን ዮሐንስ ውኃ ሲል ምን ማለቱ እንደሆነ ይከራከራሉ? አንዳንዶች ይህ የክርስቶስን ሥጋዊ ውልደት ያሳያል ይላሉ። ይህም ሕጻኑ በእናቱ ማሕጸን ውስጥ ሳለ የሚኖርበትና በሚወለድበት ጊዜ የሚፈሰው ውኃ ነው ይላሉ። ሌሎች ደግሞ ይህ ኢየሱስ በተሰቀለ ጊዜ ወታደሮች ጎኑን በጦር ሲወጉ የፈሰሰውን ውኃና ደም ያመለክታል ይላሉ ( ዮሐ. 19፡34)። ዮሐንስ የሚናገረው ክርስቶስ በውኃ መጠመቁን ለማመልከት ይመስላል። በዚያን ጊዜ፥ እግዚአብሔር አብ ክርስቶስ የእርሱ ልጅ መሆኑን የገለጸ ሲሆን፥ እንደ ሰው ይፋዊ አገልግሎቱን ጀምሯል። ስለሆነም ክርስቶስ በተጠመቀ ጊዜ ፍጹም ሰውና ፍጹም አምላክ መሆኑ ታይቷል።

ለ) ደም፡- ይህ የከርስቶስን ሥጋዊ ሞት ያመለክታል። ክርስቶስ በጥምቀት ጊዜ በኢየሱስ ላይ የወረደ እና ከስቅለት በፊት የሄደ መንፈስ ብቻ አይደለም። ድነት (ደኅንነት) ሊገኝ የሚችለው የእግዚአብሔር ዘላለማዊ ልጅ የሆነው ኢየሱስ ክርስቶስ ሰው ሲሆን ብቻ ነው። ክርስቶስ እንደ ሰውና አምላክ መሞቱን የሚያረጋግጠው ደሙን በመስቀል ላይ ማፍሰሱ ነው። ዮሐንስ ክርስቶስ በተሰቀለበት ስፍራ ስለነበር፥ የክርስቶስን ደም እንደ ተመለከተ ገልጾአል።

ሐ) መንፈስ፡– ክርስቶስ በተጠመቀ ጊዜ፥ መንፈስ ቅዱስ በእርሱ ላይ ወረደ። ኢየሱስ መንፈስ ቅዱስን መቀበል የሚያስፈልገው እንደ ሰው ብቻ ነበር። እንደ አምላክ፥ ኢየሱስ የመንፈስ ቅዱስን ዓይነት ኃይል ነበረው። ስለሆነም መንፈስ ቅዱስ ወደ ክርስቶስ መምጣቱ አምላክ ብቻ ሳይሆን ፍጹም ሰው ጭምር እንደ ነበር ያመለክታል። ይኸው መንፈስ ቅዱስ ክርስቶስ ፍጹም አምላክና ሰው መሆኑን በመጽሐፍ ቅዱስ አማካይነት መመስከሩን ይቀጥላል። በአማኞች ልብ ውስጥ ይህንኑ ምስክርነት ይሰጣል።

ኢየሱስ ፍጹም ሰውና ፍጹም አምላክ መሆኑን የማያምን ማንም ቢሆን ከእግዚአብሔር ጋር ምንም ዓይነት ግንኙነት የለውም። ዮሐንስ እንደሚያስረዳው፥ ድነት (ደኅንነት) በጠባቡ በር የሚገባበት ነው። ይህም እምነታችንን የምናሳድርበትን ቁርጥ ያለ ግንዛቤ ይጠይቃል። ስለሆነም ዮሐንስ ድነትን (እርሱ የዘላለም ሕይወት የሚለውን) የሚያገኙት በክርስቶስ የሚያምኑ ሰዎች ብቻ መሆናቸውን ይናገራል (እነዚህም ሰዎች ክርስቶስ ሰው ሆኖ ለሰው ልጆች ኃጢአት በመስቀል ላይ እንደ ሞተ የእግዚአብሔር መለኮታዊ ልጅ አድርገው ሊቀበሉት ይገባል።) ይህን እውነት ለማመን የማይፈልግ ወይም የሚያዛባ ማንም ቢሆን የዘላለም ሕይወት የሌለው እና የእግዚአብሔር ልጅ የመሆን ሥልጣን ያላገኘ መሆኑ ተገልጾአል።

የውይይት ጥያቄ፡- ዮሐንስ ሰዎች የዘላለም ሕይወት ለማግኘት ክርስቶስ ማን እንደሆነ በግልጽ ሊገነዘቡ እንደሚገባ ያስረዳል። ዛሬ በቤተ ክርስቲያን ውስጥ የሚገኙ ሌሎች ሐሰተኛ ትምህርቶች ምን ምን ናቸው? እነዚህ ትምህርቶች ከመጽሐፍ ቅዱስ ዐበይት ትምህርቶች ጋር የሚቃረኑበትን እና አቀንቃኞቹም ድነትን አግኝተው በመንፈስ ቅዱስ እንዳልተሞሉ የሚያሳዩበትን ሁኔታ ግለጽ።

፪. እውነተኛ አስተማሪዎች እና አማኞች የእግዚአብሔር ልጆች መሆናቸውን ያውቃሉ። ይህንንም በተቀደሰ አኗኗር ያሳያሉ (1ኛ ዮሐ 5፡13-21)

ዮሐንስ አማኞች ሊያስታውሷቸውና ተግባራዊ ሊያደርጓቸው የሚገባቸውን አንዳንድ ቁልፍ እውነቶች በመዘርዝር መልእክቱን ይደመድማል።

ሀ) ሰው ድነትና የዘላለም ሕይወት ሊያገኝ የሚችለው በኢየሱስ ክርስቶስ በማመን ብቻ ነው። ከዚህ ውጪ ሌላ መንገድ የለም።

ለ) እግዚአብሔር ጸሎታችንን እንደሚመልስ በድፍረት የምንተማመነው የእግዚአብሔርን ፍቃድ ስናውቅ እና እንደ ፈቃዱ ስንጸልይ ነው። ይህም ከእግዚአብሔር ጋር የቅርብ ግንኙነት ሊኖረን እንደሚገባ ያሳያል። አንዳንድ ክርስቲያኖች እግዚአብሔርን የፈለግነውን ነገር ልንጠይቀው እንደምንችል እና እርሱም የጠየቅነውን ሁሉ የመስጠት ግዴታ እንዳለበት ያስባሉ። እነዚህ ሰዎች እንደ ኢሳ. 45፡11 ያሉትንና «ጠይቁ ይሰጣችኋል» (ማቴ. 7፡7-8) የሚሉትን ጥቅሶች በተሳሳተ መንገድ ይተረጉማሉ። በእነርሱ አስተሳሰብ ማድረግ ያለብን ነገር ቢኖር እግዚአብሔር አንድን ነገር እንዲሰጠን በተደጋጋሚ መጠየቅ እንደሆነና እርሱም በዚህ ጊዜ ሊሰጠን እንደሚገደድ ያስባሉ። (ማስታወሻ፡ የኢሳይያስ 45፡11 የአማርኛው ትርጉም ይህን ያህል ጥሩ አይደለም። ትክክለኛው ትርጉም «እዘዙኝ» የሚል ሳይሆን፥ «ስለ እጆቼ ሥራ ታዙኛችሁ?» የሚል ነው።) አንዳንድ ሰዎች «ፈቃድህ ከሆነ» ብሎ መጸለይ ጥርጣሬን ያሳያል ይላሉ። ይህ እርግጥ አንዳንድ ጊዜ ጥርጣሬን ሊያሳይ ይችላል። ነገር ግን ክርስቶስ በማቴ. 6፡10 እንዳስተማረው እና ወደ መስቀል ሞት ከመሄዱ በፊት እንደ ጸለየው (ሉቃስ 22፡42)፥ ለጸሎት ወደ እግዚአብሔር በምንቀርብበት ጊዜ ፈቃዳችንን ከመሻት ይልቅ ለእርሱ ፈቃድ የመገዛት ባህሪ ሊኖረን ይገባል። መጽሐፍ ቅዱስን ብንመለከት፥ እግዚአብሔርን ምንም ነገር እንዲያደርግ ልናዘው አንችልም። እርሱ ፈጣሪያችን ነው፥ እኛም ፍጥረቱ ነን (ኢሳ. 45፡12)። እንዲሁም መጽሐፍ ቅዱስ በልባችን ኃጢአትና፥ ራስ ወዳድነት እስካለ ድረስ ጸሎታችን እንደማይመለስ ይናገራል (ያዕ. 4፡1-3)።

እግዚአብሔር ጸሎታችንን እንደሚመልስ የምንተማመነው እንዴት ነው? ዮሐንስ በሁኔታው ውስጥ የእግዚአብሔርን ፈቃድ ካወቅን እግዚአብሔር ጸሎታችን ይመልሳል ብለን ልንተማመን እንደምንችል ይናገራል። መጽሐፍ ቅዱስ አንድ ነገር ሊሰጠን በግልጽ ተስፋ ከገባልንና እግዚአብሔርም ለዚያ ሁኔታ የሚፈልገው ይህንኑ እንደሆነ ካወቅን፥ በልበ ሙሉነት ልንጸልይ እንችላለን። ነገር ግን እግዚአብሔር በአንድ ሁኔታ ውስጥ ምን እንደሚፈልግ ካላወቅን፥ ልክ ክርስቶስ በጌቴሴማኒ እንደ ጸለየው «የእኔ ፈቃድ ሳይሆን የአንተ ፈቃድ ይፈጸም» በሚል የትሕትና መንፈስ መጸለይ ይኖርብናል።

ሐ) እንደ እግዚአብሔር ፈቃድ ለመጸለይ ምሳሌ የሚሆነን በኃጢአት፥ በተለይም ባለማመን ኃጢአት ለሚቅበዘበዙ ሰዎች አማኞች የሚቀርበው ጸሎት ይሆናል። እግዚአብሔር የራሳችን ፍላጎቶች እንዲያሟላ ብቻ ሳይሆን፥ በሌሎች ሰዎችም ሕይወት እንዲሠራ መጸለይ ይኖርብናል። ዮሐንስ «ሞት የሚገባው ኃጢአት» ሲል ምን ማለቱ እንደሆነ ምሁራን ይከራከራሉ። ምክንያቱም ዮሐንስ ስለ ምን ኃጢአት እንደሚናገር አያብራራም። ዮሐንስ የሚናገረው ስለ ዘላለማዊ ሕይወት (ድነት (ደኅንነት) ወይም ስለ ሥጋዊ ሕይወት መሆኑ አልተገለጸም። በማርቆስ 3፡28-29 እንደ ተገለጻው ስለማይሰረይ ኃጢአት ከመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ የሚከተሉትን ነገሮች ልንማር እንችላለን፡

  1. መጽሐፍ ቅዱስ አንድ ሰው በክርስቶስ ለማመን ፈልጎ አንድ ኃጢአት ከመፈጸሙ የተነሣ ተቀባይነትን ያጣበትን ሁኔታ አይገልጽልንም። ስለሆነም፥ አንድ ሰው በሕይወት ዘመኑ ንስሐ ከገባ እግዚአብሔር ይቅር የማይለው ኃጢአት አይኖርም።
  2. በአዲስ ኪዳን ትምህርት መሠረት፥ አንድ ሰው ከሞተ በኋላ ወደ ሲኦል የሚወርደው በኢየሱስ ክርስቶስ ካላመነ ብቻ ነው።
  3. መጸለይ የማይቻልበት ኃጢአት አንድ ሰው ክርስቶስ በሥጋ የተገለጠ የእግዚአብሔር ልጅና የድነት (ደኅንነት) መንገድ መሆኑን ሳያምን የሞተ እንደሆነ ይመስላል። ሰውየው ከሞተ በኋላ እግዚአብሔር ምሕረት እንዲያደርግለትና እንዲያድነው መጸለይ አይኖርብንም።
  4. አንዳንድ ምሁራን ዮሐንስ የሚናገረው ስለ መንፈሳዊ ሞት ሳይሆን፥ ስለ ሥጋዊ ሞት ነው ይላሉ። በመሆኑም አንድ ሰው ብዙ ልመና እየተደረገለት ለክርስቶስ ጀርባውን ሰጥቶ ሐሰተኛ ትምህርትን ቢከተል፥ ወይም የእግዚአብሔር ፈቃድ አለመሆኑን እያወቀ በኃጢአት ቢመላለስ፥ እግዚአብሔር በሥጋዊ ሞት እንደሚቀጣው ይናገራሉ። ይህም እግዚአብሔር ሐናንያንና ሰጲራን (የሐዋ. 5)፥ እንዲሁም አንዳንድ የቆሮንቶስ ክርስቲያኖችን እንደ ቀጣ ማለት ነው (1ኛ ቆሮ. 11፡30)። እንዲህ ዓይነት ሰው በሚታመምበት ጊዜ እግዚአብሔር እንዲለውጠው ከመጠየቅ ይልቅ ኃጢአቱን እንዲናዘዝ መጠየቅ ይኖርብናል።

መ. ዮሐንስ ዐቢይ ትምህርቱን አማኞች ሊያደርጓቸው ይገባል ባላቸው ሦስት ነገሮች ይደመድማል። በመጀመሪያ፥ የእግዚአብሔር ልጅ የሆነ ማንኛውም ሰው በልማድ ኃጢአት ውስጥ አይኖርም። ከእግዚአብሔር የተወለዱ ሰዎች ኃጢአትን ሊያሸንፉ ይችላሉ። እግዚአብሔርም ከዲያብሎስ ይጠብቀናል። ሁለተኛ፥ በክርስቶስ የምናምን ሰዎች የእግዚአብሔር ልጆች መሆናችንን ማወቅ ይኖርብናል። ነገር ግን በክርስቶስ የማያምኑና የሚያሳድዱ፥ ሰዎች በሰይጣን ቁጥጥር ሥር ያሉ ናቸው። ሦስተኛ፥ የእግዚአብሔር መለኮታዊ ልጅ የሆነው ክርስቶስ በሥጋ እንደ ተገለጠ ማወቅ አለብን። እርሱ እውነተኛ አምላክና የዘላለም ሕይወት ምንጭ ነው።

ሠ. አማኞች እንደ መሆናችን፥ ሕይወታችንን ከጣዖት አምልኮ መጠበቅ አለብን ምንም እንኳን ዮሐንስ ይህን ሲል ከእንጨትና ድንጋይ የተሠሩትን ጣዖታት ማመልከቱ ሊሆን ቢችልም፥ በአእምሮ ውስጥ ከዚህ የሰፋ አሳብ ሊኖር ይችላል። ከእግዚአብሔር በላይ የምወደው ማንኛውም ነገር ጣዖት ነው። ቤተሰባችንን፥ ሀብታችንን፥ ትምህርታችንን፥ ሥራችንን ከእግዚአብሔር አብልጠን ከወደድን፥ ያ ነገር ጣዖታችን ነው ማለት ነው። አንድን ነገር ከእግዚአብሔር አብልጠን መውደዳችንና ከዚህም የተነሣ ጣዖት እንደሆነብን በምን እናውቃለን? እግዚአብሔርን በእነዚያ ነገሮች ዙሪያ መታዘዝ አለመታዘዛችንን ራሳችንን ጠይቀን መረዳት አለብን። ለአንዲት ዓለማዊ ልጅ ያለን ፍቅር እንድናገባት የሚያስገድደን ከሆነ፥ ጣዖታችን ሆናለች ማለት ነው። ገንዘብ የማግኘት ፍላጎታችን ጉቦ እንድንሰጥ ካስገደደን፥ ገንዘብ ጠዖታችን ሆኗል ማለት ነው። በትምህርትና በደረጃ ከፍ የማለት ፍላጎታችን በፈተና ላይ እንድናጭበረብር ካደረገን፥ ትምህርት ጣዖታችን ሆኗል ማለት ነው። ዮሐንስ ልባችንን በመመርመር ከእግዚአብሔር አብልጠን የምንወደው ነገር እንዳለ እንድንመለከት ያስጠነቅቀናል።

ከአብዛኞቹ መልእክቶች በተቃራኒ፥ ዮሐንስ መልእክቱን የሚጨርሰው በስንብት ሰላምታ፥ የሰዎችን ሰላምታ በማስተላለፍ ወይም በቡራኬ አይደለም። ዮሐንስ ኃይለኛ መልእክቱን የሚደመድመው በዚህ ትእዛዝ ነው፣ “ልጆች ሆይ፥ ከጣዖታት ራሳችሁን ጠብቁ።”

የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) በአንድ አማኝ ሕይወት ውስጥ ጣዖታት ሊሆኑ የሚችሉትን ሌሎች ነገሮች ዘርዝር። ለ) ሕይወትህን መርምር። በሕይወትህ ውስጥ ጣዖት አለን? ከሆነ፥ የጣዖት አምላኪነት ኃጢአትህን ተናዘዝና ክርስቶስን በሙሉ ልብህ ወደ ማፍቀር ተመለስ። ሐ) ከ1ኛ ዮሐንስ ጥናት ያገኘሃቸው አስፈላጊ ትምህርቶች ምን ምን ናቸው?

(ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የአዲስ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)

Exit mobile version