Site icon

የኦሪት ዘጸአት መግቢያ

የውይይት ጥያቄ፥ ሀ) ከሁሉም በላይ አስፈላጊ የሆነና በሕይወትህ የተፈጸመ መንፈሳዊ ክስተት ምንድን ነው? ለ) ይህ ለአንተ በጣም አስፈላጊ የሆነው ለምንድን ነው? ሐ) ስለዚህ ጉዳይ እግዚአብሔርን በጸሎትና በመዝሙር ምን ያህል ጊዜ ታመሰግነዋለህ?

ብዙዎቻችን በሕይወታችን የተፈጸመውና ከሁሉ በላይ አስፈላጊ የሆነው መንፈሳዊ ክስተት  ድነታችን (ደኅንነታችን) ነው በማለት ነው ለላይኛው ጥያቄ መልስ የምንሰጠው። ወደ ኋላ መለስ ብለን ስናስብ ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስን ለመከተል የወሰነበትን ጊዜ እናስታውሳለን። ብዙዎቻችን ስለ ድነታችን በጸሎታችን ወይም በመዝሙር እግዚአብሔርን እናመሰግነዋለን።

አይሁድ፥ በታሪካቸው ከሁሉም አብልጠው የሚያስታውሱት አንድ ድርጊት ነበር። ያም ድርጊት እግዚአብሔር ከባርነት ነፃ አውጥቶአቸው በምድረ በዳ ወደ ሲና ተራራ፥ ከዚያም ወደ ከነዓን የመራበት ነበር። ይህ ታሪክ በኦሪት ዘጸአት ውስጥ ይገኛል። በመዝሙረ ዳዊትና በነቢያት መጻሕፍት ጸሐፊዎቹ እግዚአብሔር የእስራኤልን ሕዝብ ከባርነት ነፃ አውጥቶ ወደ ከነዓን ስለ መራበት ጊዜ ወደ ኋላ መለስ ብለው ይጠቅሳሉ።

የውይይት ጥያቄ፡- መዝ. 78ን ተመልከት። ይህ ምዕራፍ የሚናገረው ስለየትኛው ታሪካዊ ድርጊት ነው? 

የውይይት ጥያቄ፥ ሀ) «መቤዠት» የሚለው ቃል ትርጉም ምንድን ነው? ለ) «መቤዠት» የሚለውን ቃል በመጽሐፍ ቅዱስ መዝገበ ቃላት ተመልከት። ሐ) እግዚአብሔር እስራኤልን ከግብፅ ባርነት ነፃ ስላወጣበት ድርጊት ይህ ቃል ለምን ተጠቀሰ? መ) ይህ ቃል ስለ ክርስቲያኖች ድነት (ደኅንነት) ለመናገርስ ለምን አገለገለ?

ኦሪት ዘፍጥረትና ሌሎች የታሪክ መጻሕፍት ያካተቱት የብዙ ዓመታትን ታሪክ ሲሆን፥ ከኦሪት ዘጸአት እስከ ኦሪት ዘዳግም ያለው ታሪክ ግን በ50 ዓመታት ጊዜ ውስጥ የተፈጸመ ነው። እንዲያውም ከዘጸአት እስከ ዘዳግም ባሉት ክፍሎች ውስጥ ከተፈጸመው ታሪክ አብዛኛው የአንድ ዓመት ታሪክ ነው። እግዚአብሔር እስራኤላውያንን ከባርነት እንዴት ነፃ እንዳወጣቸው በመናገር ይጀምርና በሲና ተራራ ከእስራኤላውያን ጋር እንዴት ቃል ኪዳን እንደገባ ይተነትናል። ከጠቅላላው የብሉይ ኪዳን ታሪክ አንድ ስድስተኛው (1/6ኛው) በእስራኤል ሕዝብ ታሪክ ውስጥ ስላለፈው ስለዚህ ጊዜ የሚናገር ነው። እስራኤል በእግዚአብሔር ዕቅድ ውስጥ ስላላት ልዩ ስፍራ ለመረዳት ከፈለግን፥ ሕዝቡ ስለሆነው ስለ እስራኤል የሚናገረውን ነገርና አጀማመራቸውም እንዴት እንደነበረ መረዳት የግድ ያስፈልገናል።

እግዚአብሔር እስራኤልን ከባርነት እንዴት ነፃ እንዳወጣና፥ ከዚያም በምድረ በዳ ለ40 ዓመታት እንዴት እንደተንከራተቱ የሚናገረው ታሪክ በአራት የብሉይ ኪዳን መጻሕፍት ተጽፎ እናገኘዋለን፤ ኦሪት ዘጸአት ዘሌዋውያን፥ ዘኁልቁና ዘዳግም። ይህ ታሪክ በአራት ዋና ዋና ክፍሎች ሊከፈል ይችላል፡-

  1. የእስራኤል ሕዝብ ነፃ መውጣትና ወደ ሲና ተራራ መጓዝ፥ (ዘጸ. 1-18) 
  2. በሲና ተራራ የሕግ መሰጠት፥ (ዘዳ. 19-ዘኁ. 10፡10) 
  3. 40 ዓመታት በምድረ በዳ መንከራተታቸው (ዘኁ. 10፡11 -ምዕራፍ 21) 
  4. የእስራኤል ሕዝብ ወደ ከነዓን ከመግባታቸው በፊት በዮርዳኖስ ወንዝ ዙሪያ ያደረጉት ቆይታ፥ (ዘኁል. 22 – ዘዳ. 34)

የውይይት ጥያቄ፥ ስለ ኦሪት ዘጸአት ከመጽሐፍ ቅዱስ መዝገበ ቃላት ተመልከት። ስለ ኦሪት ዘጸአት ካነበብካቸው ነገሮች መካከል ዋና ዋና እውነቶች የትኞቹ ናቸው?

የመጽሐፉ ስም 

የውይይት ጥያቄ፥ በአማርኛ «ዘጸአት» ማለት ምን ማለት ነው?

ዕብራውያን (አይሁድ) የፔንታቱክን ሁለተኛ መጽሐፍ በመጀመሪያው ዐረፍተ ነገር «የ … ስሞች እነዚህ ናቸው» ብለው ሰይመውታል። ይህም ስያሜ የተገኘው ከመጽሐፉ የመጀመሪያ ዐረፍተ ነገር ነው። የግሪኩ ሴፕትዋጀንት መጽሐፍ ቅዱስ ግን የመጽሐፉን ርእስ «ዘጸአት» ብሎታል። ለእንግሊዝኛውም ሆነ ለአማርኛው መጽሐፍ ቅዱስ ርእስ መሠረት የሆነው ይህ የግሪኩ መጽሐፍ ቅዱስ ርእስ ነው። ዘጸአት ማለት «መውጣት» ወይም «መለየት» ማለት ነው። ለሁለተኛው የፔንታቱክ መጽሐፍ ይህ ርእስ የተሰጠበት ምክንያት በውስጡ የሚገኘው ዋናው ታሪክ የሚናገረው እግዚአብሔር የእስራኤልን ሕዝብ በግብፃውያን ባርነት ሥር ከነበሩበት ሁኔታ እንዴት ነፃ እንዳወጣቸውና ከግብፅ ተለይተው ወደ ተስፋይቱ ምድር መጓዝ ስለ መጀመራቸው የሚናገር በመሆኑ ነው። 

ጸሐፊው

የውይይት ጥያቄ፥ ሀ) ኦሪት ዘጸአትን እንደጻፈ የሚታመነው ሰው ማን ነው? ለ) ዘጸ. 17፡14፤ 24፡4 አንብብ። እግዚአብሔር ሙሴን ምን እንዲያደርግ አዘዘው? ሙሴስ ምን አደረገ?

ከጥንት ዘመን ጀምሮ አይሁድም ሆኑ ክርስቲያኖች የኦሪት ዘጸአት ጸሐፊ ሙሴ እንደሆነ ይስማሙ ነበር። የእግዚአብሔር ቃል ሙሉ በሙሉ የእግዚአብሔር ቃል እንደሆነ የማያምኑ ምሁራን መጠራጠር የጀመሩት ባለፉት 200 ዓመታት ብቻ ነው።

ስለ ኦሪት ዘጸአት ጸሐፊ ሰዎች ሦስት ዋና ዋና አሳቦች ይሰነዝራሉ።

  1. አንዳንድ ሰዎች የዚህ መጽሐፍ ጸሐፊ ኢያሱ ወይም በኢያሱ ጊዜ ሊቀ ካህን የነበረው ኤሊዔዘር ነው ብለው ያስባሉ። ኦሪት ዘጸአትን የጻፈውም ከሙሴና ከአሮን በሰማው አፈ-ታሪክ መሠረት ነው ይላሉ። ይሁን እንጂ ይህን አስተሳሰብ ለመደገፍ ያለው ማረጋገጫ በጣም ጥቂት ነው። 
  2. ጄ.ኢ.ፒ.ዲ. የሚለውን ንድፈ ሐሳብ የሚከተሉ ሰዎች ኦሪት ዘጸአት የተጻፈው በሦስት ዋና ዋና ጸሐፊዎች ነው ይላሉ። እነዚህም «ጄ» ጄሆቫ፥ «ኢ» ኤሎሂም፥ «ፒ» ፕሪስት (ካህን) ተብለው የተሰየሙ ናቸው። የኦሪት ዘጸአት የመጨረሻ ቅጅ የተዘጋጀው ከ600-400 ዓ.ዓ. ከነበረው ጊዜ በፊት አልነበሩም ብለው ያስተምራሉ። ይህ አመለካከት በጣም ጥቂት መረጃ ያለው ሲሆን በርካታ የዘመኑ ምሁራንም አይቀበሉትም።
  3. ሙሴ የኦሪት ዘጸአት የመጀመሪያ ጸሐፊ ነው። ስለዚህ መጽሐፉ የተጻፈው በ1400 ዓ.ዓ. አካባቢ ነው። ሆኖም ሙሴ ከሞተ ከጥቂት ጊዜ በኋላ ሌሉች አዘጋጆች የኦሪት ዘጸአት ታሪክ ከተፈጸመ በመቶዎች ከሚቆጠሩ ዓመታት በኋላ ማንበብ ለሚችሉ አይሁድ የበለጠ ግልጽና በቀላሉ የሚረዱት ለማድረግ አንዳንድ ነገሮችን አክለውበታል። ይህም በሚከተሉት ምክንያቶች ከሁሉ የተሻለው አመለካከት ነው፡-

ሀ. ሙሴ እንዲጽፍ በእግዚአብሔር ታዘዘ። ደግሞም እርሱ እንደጻፈ በግልጥ ተጠቅሷል፤ (ዘጸ. 17፡14፤ 34፡1-5 ተመልከት)። 

ለ. የኦሪት ዘጸአት ጸሐፊ ሙሴ መሆኑን ኢየሱስ በግልጥ ተናግሯል፤ (ማር. 7፡10 ተመልከት)። 

ሐ. ሙሴ በቂ እውቀት ስለነበረውና ስለተፈጸሙት ድርጊቶች ሁሉ ደግሞ የዓይን ምስክር ስለነበር ሊጽፉት ከሚችሉት ሰዎች ዋነኛው እርሱ ነው። 

መ. ከአንዳንድ ክፍሎች በግልጥ እንደምንመለከተው ኦሪት ዘጸአት በኋላ የተነሣ አዘጋጅ እንደገና አቀናብሮታል። የሚከተሉትን ተመልከት፡-

  1. አብዛኛው ታሪክ የሚያወራው ስለ ሙሴ ሲሆን በሙሴ በራሱ የተጻፈ ግን አይመስልም፤ (ምሳሌ፡- ዘጸ. 6፡13፤ 11፡3)። 2. ከሙሴ ሞት በኋላ የተጨመሩ የሚመስሉ መግለጫዎች በበርካታ ስፍራዎች አሉ፤ (ለምሳሌ፡- ዘጸ. 16፡31-36)።

የጸሐፊው የሙሴ ሕይወት

የውይይት ጥያቄ፥ ሀ) ዘጸ. 2-3 አንብብ። እነዚህ ምዕራፎች ስለ ሙሴ የመጀመሪያዎቹ 80 ዓመታት የሚናገሩትን ዘርዝር። ለ) ስለ ሙሴ በመጽሐፍ ቅዱስ መዝገበ ቃላት የተጻፈውን አንብብ። በጻፍከው ዝርዝር ላይ ስለ ሙሴ ያገኘኸውን ተጨማሪ ነገር ጻፍ።

የኦሪት ዘጸአት ታሪክ የጊዜ ርዝመት 

የውይይት ጥያቄ፥ ዘጸ. 1-2፡10 አንብብ። የዘጸአት ታሪክ የሚጀምረው ከምንድን ነው?

የውይይት ጥያቄ፥ ዘጸ. 19 አንብብ። በዚህ ምዕራፍ ውስጥ የእስራኤል ሕዝብ ያለው የት ነው?

የኦሪት ዘጸአት ታሪክ የእግዚአብሔር ሕዝብ የሆኑት እስራኤላውያን በግብፅ ለመኖር እንዴት እንደመጡ አጭር መግለጫ ከሰጠን በኋላ፥ የሙሴን ልደት ታሪክ ይጀምራል። ከዘጸአት እስከ ዘዳግም ባሉት መጻሕፍት ውስጥ ከሁሉም የላቀው ሰብዓዊ ገጸ ባሕርይ ሙሴ ነው። ኦሪት ዘጸአት የሚደመደመው እስራኤላውያን ወደ ሲና ተራራ ደርሰው ሲሰፍሩ ነው። እግዚአብሔር ከሕዝቡ ጋር ቃል ኪዳን የገባው በዚህ ስፍራ ነው።

የእስራኤል ሕዝብ በሲና ተራራ የሰፈሩት ለአንድ ዓመት ያህል ነው። በዚያም እግዚአብሔር እነርሱን በአስደናቂ ኃይል ተገናኛቸው። የእርሱ ቅዱስ ሕዝብ ሆነው እንዴት እንደሚኖሩ የሚያስረዱ ሕግጋትን ሰጣቸው። ከእርሱ ጋር የሚገናኙበትን የማደሪያውን ድንኳን እንዴት እንደሚሠሩም ነገራቸው። አብዛኛው የዘጸአትና የሌዋውያን ታሪክ የተፈጸመው በሲና ተራራ ነው።

(ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የብሉይ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)

Exit mobile version