Site icon

የ1ኛ እና የ2ኛ ሳሙኤል መዋቅር 

የ1ኛ እና የ2ኛ ሳሙኤል ጸሐፊ አንድ እንደሆነ ተመልክተናል፤ ስለዚህ በመጽሐፉ ውስጥ ተመሳሳይ የሆኑ ዓላማዎችና የአጻጻፍ ስልቶችን መጠበቃችን ትክክል ነው። የሳኦልና የዳዊትን ታሪክ ማወዳደር ትኩረትን የሚስብ ነው፤ በ1ኛ ነገሥት ውስጥ የሚገኘው የሰሎሞን ታሪክም እንደዚሁ ነው። መጻሕፍቱን በቅርበት በምንመረምርበት ጊዜ፥ ጸሐፊዎቹ ሕይወታቸውንና የእርሱንም ውጤት በማወዳደር ለማመልከት እንዴት ተመሳሳይ መዋቅር እንደተጠቀሙ እንረዳለን። ሕይወታቸውን የሚያነጻጽረውን የሚቀጥሉትን አንቀጾች ተመልከት፡-

ሳኦል

በሳሙኤል አቀባበል ተቀባ፤ ሕዝቡ ፈጣን አቀባበል አደረገለት፤ በአሞናውያን ላይ ድልን አገኘ፣ ያልተፈቀደለትን መስዋዕት አቀረበ፤ ሕዝቡን በተሳሳተ መሐላ ውስጥ እንዲገባ አደረገ፤ ስለ አማሌቃውያን እግዚአብሔር የሰጠውን ትዕዛዝ ሳይፈጽም ቀረ፤ ንጉሥነቱን ተቀማ፤ በፍልስጤማውያን ተሸነፈ፤ የቤተሰብ ሞት አጋጠመው፤ ራሱን ገደለ

ዳዊት

በሳሙኤል አቀባበል ተቀባ፤ ሕዝቡ እስኪቀበለው ረጅም ጊዜ ወሰደበት፤ ኢየሩሳሌምን ወሰደ፤ ፍልስጤማውያንን አሸነፈ፤ ታቦቱን ወደ ኢየሩሳሌም ወሰደ፤ ከእግዚአብሔር ጋር ቃል ኪዳን አደረገ፤ መንግስቱን አስፋፋ፤ ዝሙት ፈጸመና ነፍስ ገደለ፤ በተሳሳተ ምክንያት የሕዝብ ቆጠራ አስደረገ፤ ልጆቹን አልተቆጣጠረም፤ በልጆቹ መካከል ደም መፍሰስ ሆነ (አምኖን፣ አቤሰሎምና አዶኛስ በሙሉ ሞቱ)፤ ልጆቹ አመጹበት፤ በሕዝብ ቆጠራው ምክኛት ብዙ እስራኤላውያን ሞቱ

ሰለሞን

በዳዊት ተሾመ፤ ሕዝቡ ወዲያው ተቀበለው፤ ጥበብን ለመነ፤ ብልህ አስተዳደርን አደረገ፤ ቤተ መቅደስና ቤተ መንግሥቱን ሰራ፤ ብዙ ባእዳን ሚስቶችን አገባ፤ ጣኦትን አመለከ፤ ሕዝቡን በከባድ ሥራና በከፍተኛ ቀረጥ (ግብር) አስጨነቀ፤ በዳዊት ተሸንፈው የተገዙትን ሕዝቦች መቆጣጠር አቃተው፤ ከሞተ በኋላ የእስራኤል መንግሥት ለሁለት ተከፈለ 

ከላይ እንደምትመለከተው፥ የሦስቱም ነገሥታት ታሪክ የሚጀምረው ሦስቱም ወደ ሥልጣን የመጡበትን ወይም የተመረጡበትን ሁኔታ በመግለጥ ነው። ቀጥሎም የሠሯቸው አንዳንድ መልካም ነገሮች ተጠቅሰዋል። ታሪኮቹ ሁሉ ደግሞ የሚያጠቃልሉት ኃጢአት በሕይወታቸው ስላመጣው ነገር በመናገር ነው።

የውይይት ጥያቄ፥ ከዚህ ሠንጠረዥ ስለ አመራር የምንማረው ነገር ምንድን ነው? 

የ1ኛ ሳሙኤል አስተዋጽኦ

  1. የዓሊና የሳሙኤል ታሪክ (1-7)

ሀ. የሳሙኤል መወለድ (1-2፡11) 

ለ. በዔሊና በቤተሰቡ ላይ የተፈጸመ ፍርድ (2፡12-4፡22)

ሐ. ነቢይና ፈራጅ የሆነው ሳሙኤል (5-7) 

  1. የንጉሥ ሳኦል ታሪክ (8-15)

ሀ. ሕዝቡ ንጉሥ እንዲያነግሥላቸው እግዚአብሔርን ጠየቁ (8) 

ለ. ሳኦል ለንጉሥንት ተመረጠ (9-10) 

ሐ. በአምናውያን ላይ የተገኘ ድል (11፡1-13)

መ. እስራኤላውያን ከእግዚአብሔር ጋር የነበራቸውን ቃል ኪዳን አደሱ (11፡14-12፡25) 

ሠ. የሳኦል አለመታዘዝና እግዚአብሔር እንደናቀው (13-15) 

  1. የዳዊት መነሣትና የሳኦል ዘመነ መንግሥት ፍጻሜ (16-31)

ሀ. ዳዊት በሳሙኤል ተቀባ (16) 

ለ. ጻዊት በሳኦል መንግሥት ውስጥ አገለገለ (17-20) 

ሐ. ሳኦል ዳዊትን ለመግደል ሞከረ (21-26) 

መ. የሳኦል ሽንፈትና ሞት (27-31)

የ1ኛ እና የ2ኛ ሳሙኤል የጊዜ ቀደም ተከተል 

የዔሊ፥ የሶምሶን፥ የሳኦልና የዳዊትን የጊዜ ቅደም ተከተል በእርግጠኝነት ማወቅ አስቸጋሪ ነው፤ ምክንያቱም ስለ ጊዜያት የሚናገሩ ጥቅሶች በጣም ጥቂት ናቸው። አንዳንዶቹ በእነዚህ መጻሕፍት የተጻፉ ታሪኮች ለጸሐፊው ዓላማ ሲባል በአንድነት የቀረቡ እንጂ የጊዜ ቅደም ተከተላቸው የተጠበቀ አይደለም ይላሉ። አንዳንዱም ምሁራን ዔሊ የሞተው ሶምሶን መሥራት በጀመረበት ጊዜ አካባቢ በ1075 ዓ.ዓ. ነው ይላሉ። ሶምሶን የሠራው ከ1075-1055 ዓ.ዓ. ነው ይላሉ። ሳሙኤል የተወለደው በ1105 ዓ.ዓ. ሲሆን እስከ 1022 ዓ.ዓ. ድረስ ኖሯል። ይህ ማለት ሶምሶንና ሳሙኤል የኖሩትና ያገለገሉት በተመሳሳይ ጊዜ ነው ማለት ነው። የሳሙኤል፥ የሳኦልና የዳዊት ሕይወትን በሚመለከት ስለኖሩበት ዘመን ቀጥሉ አንድ አሳብ ቀርቦአል። እነዚህ በምሁራን የተሰጡ ግምታዊ የሆኑ ጊዜያት ናቸው፤ ምክንያቱም ትክክለኛውን ጊዜ ለመናገር በቂ የሆነ መረጃ ባለመኖሩ።

1105 ዓ.ዓ. ሳሙኤል ተወለደ። 

1080 ዓ.ዓ. ሳኦል ተወለደ። 

1050 ዓ.ዓ. ሳኦል ለንጉሥነት ተቀባ። 

1040 ዓ.ዓ. ዳዊት ተወለደ። 

1025 ዓ.ዓ. ዳዊት በሳሙኤል ተቀባ። 

1010 ዓ.ዓ. ሳኦል ሞተ፤ ዳዊት በይሁዳ ላይ መንገሥ ጀመረ። 

1003 ዓ.ዓ. ዳዊት በእስራኤል ሁሉ ላይ ነገሠ። 

970 ዓ.ዓ. ዳዊት ሞት።

የውይይት ጥያቄ፥ ስለ 1ኛ ሳሙኤል ከመጽሐፍ ቅዱስ መዝገበ ቃላት ውስጥ አንብብ። በዚያ ስፍራ የተጠቀሱትን ዋና ዋና እውነቶች ዘርዝር።

(ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የብሉይ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)

Exit mobile version