Site icon

የግጥም መጻሕፍት መግቢያ

የውይይት ጥያቄ፡ ሀ) በራስህ ባህል ውስጥ የሚገኙ የተለያዩ የአጻጻፍ ወይም የአነጋገር ዓይነቶችን ዘርዝር። ለ) ከእነዚህ የአጻጻፍ ወይም የአነጋገር ስልቶች ውስጥ በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ የሚገኙት ምን ያህሎቹ ናቸው?

በእያንዳንዱ ባህል ውስጥ የተለያዩ የአጻጻፍ ወይም የአነጋገር ስልቶች ይገኛሉ። ለምሳሌ፥ ከጓደኞቻችን ጋር በምንነጋገርበት ጊዜ የምንጠቀምበት የተለመደ የአነጋገር ዘይቤ አለ፤ ነገር ግን ለተናገርነው ጉዳይ አትኩሮት ለመስጠት ምሳሌያዊ አነጋገሮችን የምንጠቀምበትም ጊዜ አለ። ብዙዎቻችን በልጅነታችን የተለያዩ ተረቶችን ሰምተናል። በተለይ በኢትዮጵያ ብቻ የሚነገር የ«ሰምና ወርቅ» የአነጋገር ዘይቤ አለ። ልዩ ተሰጥኦ ያላቸው ሰዎች፥ በተለያዩ አጋጣሚዎች የሚጽፉት፥ በንግግር የሚያቀርቡት ግጥም በመባል የሚታወቅ የአጻጻፍና አነጋገር ስልት አለ። በመጨረሻ መዝሙር በመባል የሚታወቁ በሙዚቃ ተቀናብረው የሚቀርቡ የተለዩ የግጥም ዓይነቶችም አሉ።

የውይይት ጥያቄ፥ እነዚህ ሁሉ የአነጋገር ዓይነቶች በቤተ ክርስቲያን አገልግሎት ውስጥ እንዴት በጥቅም ላይ ሊውሉ እንደሚችሉ የሚያስረዱ ምሳሌዎችን ጥቀስ።

ብሉይ ኪዳን በእነዚህ የአጻጻፍ ስልቶች በሙሉ ይጠቀማል። እስካሁን ድረስ ባካሄድነው የብሉይ ኪዳን ጥናታችን በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ በርካታ የተለያዩ የአጻጻፍ ስልቶች መኖራቸውን ተመልክተናል። እግዚአብሔር በሲና ተራራ ለእስራኤላውያን የሰጣቸው ሕግጋት አሉ። በእስራኤል ሕዝብ ላይ የደረሰውን ታሪክ ቀጥተኛ በሆነ ቋንቋ የሚናገሩ ታሪኮችን እናገኛለን። ከዚያም በብዙ ሌሎች ቋንቋዎች ውስጥ የማይገኙ የነቢያት ጽሑፎች ብለን የምንጠራቸው፥ ለየት ባለ የአጻጻፍ ስልት የተጻፉ ጽሑፎች አሉ።

ከመጽሐፈ ኢዮብ እስከ መኃልየ መኃልይ ዘሰሎሞን የሚገኙትን የብሉይ ኪዳን መጻሕፍት የሚያካትተው ሦስተኛው ክፍል በአመዛኙ ሁለት ዓይነት የአጻጻፍ ስልቶችን ይጠቀማል። የመጀመሪያው፥ በመዝሙረ ዳዊት ውስጥ የምናገኘው ዓይነት የግጥም ምንባብ ሲሆን፥ ሁለተኛው ደግሞ፥ በመጽሐፈ ምሳሌ ውስጥ የምናገኘውን ዓይነት የጥበብ ክፍል ያካተተ ነው።

ምንም እንኳ ብዙውን ጊዜ የጥበብ ጽሑፍ በመባል የሚጠራው ይህ የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍል ባመዛኙ ግጥም፥ ቅኔና ምሳሌዎችን ያካተተ ቢሆንም፥ በብሉይ ኪዳን ውስጥ ባሉት በእያንዳንዱ መጻሕፍት ውስጥ የተወሰኑ ግጥሞች፥ ቅኔዎችና ምሳሌዎች አይጠፉም። እንዲያውም የብሉይ ኪዳን አንድ ሦስተኛው ግጥም ነው። ይህ ግጥም፡- አጭር ምንባብ (ለምሳሌ ዘፍ. 4፡23-24) ወይም ሙሉ ምዕራፉ (ለምሳሌ ዘጻ.15፡1-18) ወይም (እንደ መዝሙረ ዳዊት) ሙሉ መጽሐፍ ሊሆን ይችላል።

የውይይት ጥያቄ፥ ሀ) አብዛኛው የብሉይ ኪዳን ክፍል በግጥም አጻጻፍ ስልት የተጻፈው ለምን ይመስልሃል? ለ) ሰዎች እንደ ጌታችን የልደት በዓል ባሉት ልዩ ቀናት ግጥም ማንበብ የሚወዱት ለምንድን ነው? ሐ) ሰዎች በመዝሙረ ዳዊት ውስጥ የሚገኙ ግጥሞችን የሚወዱት ለምን ይመስልሃል?

እግዚአብሔር ከቃሉ አብዛኛውን ክፍል ለሰው ልጆች ያስተላለፈበት የሥነ ጽሑፍ መንገድ ግጥምና ቅኔ መሆኑን መገንዘብ የሚያስደንቅ ነገር ነው። ምናልባት ምክንያት ሊሆን የሚችለው ነገር ከተለመዱ ቀጥተኛ የአጻጻፍ ስልቶች ይልቅ የግጥምና የቅኔ የአጻጻፍ ስልቶች ልብን የሚያነቃቁ መሆናቸው ነው። በየትኛውም ባህል ውስጥ የሚገኙ የአብዛኛዎቹ ክርስቲያኖች ተወዳጅ መጽሐፍ መዝሙረ ዳዊት የሆነው በዚህ ምክንያት ነው። የመዝሙረ ዳዊት ግጥም በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ከሚገኝ ከማንኛውም መጽሐፍ የበለጠ ስሜቶቻችንን ይገልጻል። ለእግዚአብሔር ያለንን ፍቅርና አክብሮት ይገልጻል፤ ሞት ወይም የተለያዩ ችግሮች በገጠሙን ጊዜ የሚሰማንን ኃዘን ይገልጻል፤ ሰዎች በተሳሳተ መንገድ ሊጠቀሙብን በሚሞከሩ ጊዜ የሚሰማንን የቁጣ ስሜት ይገልጻል።

ሆኖም ግን ችግሩ መዝሙረ ዳዊት ከግጥምና ከቅኔ መጻሕፍት የሚመደብና መተርጐምም ያለበት በዚሁ መልክ መሆኑን አንዳንድ ጊዜ ክርስቲያኖች መዘንጋታቸው ነው። ስለዚህ በርካታ ክርስቲያኖች በመዝሙረ ዳዊትና በሌሉች የቅዱሳት መጻሕፍት ሥነ-ግጥማዊና ቅኔያዊ ክፍሎች ውስጥ የሚገኙትን ትምህርቶች በተሳሳተ መንገድ ይተረጒሙአቸዋል። በሥነ-ግጥምና በቅኔ የሚገለጹ ነገሮች ብዙ ጊዜ ምሳሌያዊ ወይም ሥዕላዊ መሆናቸውን በመዘንጋት በቀጥታ ሊተረጕሟቸው ይሞክራሉ።

ብዙ ምሁራን የግጥምና የቅኔ መጻሕፍትን በሁለት ዐበይት ክፍሎች ይከፍሏቸዋል። የመጀመሪያው ክፍል፥ በባሕርያቸው ባመዛኙ ሥነ-ግጥማዊ የሆኑት ናቸው፤ ስለዚህ እነዚህን የግጥም መጻሕፍት ይሏቸዋል። መዝሙረ ዳዊትና መኃልየ መኃልይ ዘሰሎሞን በአብዛኛው የግጥም መጻሕፍት ናቸው። በሁለተኛው ክፍል፥ የጥበብ መጻሕፍት የሚባሉት ናቸው፤ እዚህም የተጻፉት በግጥም ሥነጽሑፍ መልክ ቢሆንም፥ ትኩረት የሚያደርጉት ግን በጥበብና ብዙውን ጊዜ ደግሞ በምሳሌያዊ አነጋገሮች ላይ ነው። መጽሐፈ ምሳሌና መክብብ ለጥበብ መጻሕፍት ጥሩ ምሳሌዎች ናቸው። 

የዕብራውያን ሥነ-ግጥምና ቅኔ

የውይይት ጥያቄ፥ ሀ) አጠር ያለ አንድ ግጥም ወይም ቅኔ ጻፍ። ለ) አንድ ደብዳቤ በመጻፍና አንድ ግጥም ወይም ቅኔ በመጻፍ መካከል ያለው ልዩነት ምንድን ነው? ሐ) ሰዎች ግጥምን ለመጻፍ የሚጠቀሙባቸውን የተለያዩ ሕግጋት ጥቀስ (ምሳሌ፡- በየስንኙ መጨረሻ ቤት የመምታት ጉዳይ)። 

እያንዳንዱ ባህል ስለ ግጥም ይዘት የራሱ የሆነ አመለካከት አለው። በብሉይ ኪዳን የምናገኘው የዕብራውያንን ግጥም ነው። የዕብራውያን የግጥም አጻጻፍ በእኛ ባህል ውስጥ ካለው የሥነ-ግጥም አጠቃቀም የተለየ ስለሆነ፤ የዕብራውያን የግጥም ይዘትና ሥን-ግጥማቸውን ለመቅረጽ አሳቦችንና ድምፆችን እንዴት እንደሚያቀናብሩ መረዳት አስፈላጊ ነው። የዕብራውያን የሥነ- ግጥም ቅንብር ከእኛ ባህል የሥነ-ግጥም ቅንብር የተለያየ ስለሆነ በቀጥታ ይዘቱን ሳይቀይር መተርጐም አስቸጋሪ ነው። የዕብራውያንን ሥነ ግጥም ትክክለኛና ተገቢ በሆነ መንገድ ለመተርጐም፤ አይሁድ ግጥማቸውን የሚጽፉባቸውን የተለየ መንገዶችና ከእኛ ግጥም እንዴት እንደሚለይ መረዳት አስፈላጊ ነው።

ሥነ-ግጥም ማለት የግጥም ጥበብ ማለት ነው።

አይሁድ የተለያዩ የጽሑፍ አደረጃጀቶችን በመጠቀም አስደናቂ የሆኑ ሥነ- ግጥሞችን ይጽፉ ነበር። እነዚህ የተለያዩ የአጻጻፍ መሣሪያዎች በትርጕም ሂደት ውስጥ ስለጠፉ በአማርኛም ሆነ በእንግሊዝኛ ቋንቋ ውስጥ ውበታቸውን ለማየት አለመቻላችን የሚያሳዝን ነው። ይህም ቢሆን እንኳ የዕብራውያን ግጥም በተለያዩ ሂደቶች ውስጥ አልፎ በእግዚአብሔር ፊት ስሜታችንን ይገልጻል፤ ይነካናልም። በመጀመሪያ ደረጃ የዕብራውያን ግጥም የተቀናበረው በተመሳሳይ ድምፆች ነበር። ይህ የእያንዳንዱን ስንኝ የመጨረሻ ቃል አንዱ ከሌላው ጋር በድምፅ እንዲስማማ ከሚያደርገው ከእኛ ግጥም ጋር ተመሳሳይ ነው።

በሁለተኛ ደረጃ፥ አይሁድ በግጥሞቻቸው ውስጥ አሳቦች አንድ ዓይነት ሂደት እንዲኖራቸው አድርገው ያቀናብሯቸዋል። ይህ በጽሑፉ ውስጥ «ፓራላሊዝም» ተነጻጻሪነት በመባል ይታወቃል። ለምሳሌ፦ መዝሙር (103)፡10 በዕብራይስጡ መጽሐፍ ቅዱስ እንደተጻፈው በቀጥታ ብንተረጕመው የሚነበበው እንደሚከተለው ነው፡- «እንደ ኃጢአታችን አላደረገብንም፤ እንደ በደላችን አልከፈለንም።» 

የዚህ መዝሙር ጸሐፊ አንድ ዓይነት ድምፅ ያላቸውን ቃላት ማቀናበር ብቻ ሳይሆን፥ የያዙትን አሳብ በማያያዝ እንዴት እንዳቀናጃቸው ልብ በል።

አይሁድ ግጥምን በሚጽፉበት ጊዜ አሳባቸውን የሚያቀርቡበት አራት መንገዶች አሉ፡-

  1. የመጀመሪያ ደረጃ፥ እጅግ የተለመደው መንገድ አንድን አሳብ በጣም ተቀራራቢ በሆኑ ቃላት መድገም ነው። ይህ «ሲኖኒመስ ፓራለሊዝም» (ተመሳሳይ የሆነ ተነጻጻሪነት) ሊባል ይችላል። ይህን ቅንብር በመዝሙር (103)፡10 እናገኛለን። በዚህ ስፍራ የግጥሙ ጸሐፊ ለአንድ አሳብ ሁለት የተለያዩ፥ ነገር ግን በእጅጉ የተያያዙ ቃላትን ይጠቀማል፤ እነዚህም ኃጢአትና በደል የሚሉ ናቸው። መዝሙረ ዳዊትን በምናነብበት ጊዜ ይህን ነገር በአትኩሮት መመልከት በጣም አስፈላጊ ነው። ጸሐፊው ለማስተላለፍ የፈለገው መልእክት አንድ ሆኖ ሳለ ብዙ ሰዎች ለእነዚህ ቃላት የተለያዩ ትርጕሞችን ይፈልጋሉ። ለምሳሌ፥ ጸሐፊው መዝሙር (103):3 የዚህ ዓይነቱን የግጥም ስልት ይጠቀማል፤ እዚህ ላይ «ኃጢአት» እና «ደዌ» የሚሉት ቃላትም አንድን አሳብ የሚገልጹ ናቸው። 
  2. በሁለተኛ ደረጃ፥ እጅግ የተለመደው መንገድ ሁለተኛው ስንኝ ከመጀመሪያው ስንኝ ተቃራኒ ወይም ተነጻጻሪ ሆኖ መቅረቡ ነው፡፡ (ይህ አንቲቴቲክ ፓራለሊዝም) ተቃራኒ የሆነ ተነጻጻሪነት ይባላል። ለዚህ ዓይነቱ ሥነ-ግጥም በጣም ጥሩ ምሳሌ የሚሆነው መዝሙረ ዳዊት 1፡6 ነው። በዚህ ስፍራ ጸሐፊው በመጀመሪያው ስንኝ የጻድቃንን መንገድ፣ በሁለተኛው ስንኝ ደግሞ የክፉዎችን መንገድ ያነጻጽራል። 
  3. በሦስተኛ ደረጃ፥ አንዳንድ ጊዜ ጸሐፊዎች በመጀመሪያው ስንኝ ምሳሌያዊ አነጋገር ወይም ተምሳሌት ይጠቀሙና በሁለተኛው ስንኝ ደግሞ ያንኑ አሳብ በቀጥተኛ ቋንቋ ይገልጹታል። ይህንንም «ሲምቦሊክ ፓራለሊዝም» ተምሳሌታዊ ተነጻጻሪነት ልንለው እንችላለን። ለምሳሌ መዝሙረ ዳዊት (42)፡1 ዋላ ወደ ውኃ ምንጭ ስለ መናፈቁ በመጀመሪያው ስንኝ ይናገርና፤ በሁለተኛው ስንኝ ደግሞ ጸሐፊው ነፍሱ ወደ እግዚአብሔር እንደምትናፍቅ ይናገራል። 
  4. በአራተኛው ደረጃ፥ አንዳንድ ጊዜ ጸሐፊው የጻፈው እያንዳንዱ ስንኝ በመጀመሪያው መስመር ላይ ባለው አሳብ ላይ ጥቂት ነገርን ይጨምራል። (ኢንቴቲክ ፓራለሊዝም) ተጨማሪ የሆነ ተነጻጻሪነት ይባላል። በመዝሙረ ዳዊት (29)፡1-2 ለእግዚአብሔር ልንሰጠው ስለሚገባ ነገር በየስንኙ ጥቂት አሳቦችን ይጨምራል።

የውይይት ጥያቄ፥ የሚከተሉትን ግጥሞች ተመልከትና ጸሐፊው የተጠቀመባቸውን የቅንብር ዓይነቶች ጥቀስ፡- ኢሳይያስ 44፡22፤ ሆሴዕ 7፡14፤ ምሳሌ 15፡1፤ አብድዩ 21፤ ምሳሌ 4፡23፤ መዝሙረ ዳዊት (49)፡1፤ ኤርምያስ 17፡11።

አይሁድ ግጥምና ቅኔ በሚጽፉበት ጊዜ የተጠቀሙባቸው ሌሎች የአጻጻፍ ስልቶችም ነበሩ። መጀመሪያ፥ በአብዛኛው መዝሙራት ጸሐፊው በግጥሙ እያንዳንዱን ስንኝ ወይም ጥቅስ በተለያየ ፊደል ይጀምረዋል። በዕብራውያን ሆሄያት ውስጥ ሃያ ሁለት የተለያዩ የፊደል ቅርጾች ነበሩ። ለዚህ ዓይነቱ አጻጻፍ በጣም ጥሩ ምሳሌ መዝሙረ ዳዊት 119 ነው። ይህ መዝሙር በተለያዩ ክፍሎች መከፈሉን እንመለከታለን፡- የመጀመሪያው ክፍል አሌፍ፥ ሁለተኛው ክፍል ቤት ወዘተ ይላል። እነዚህ የዕብራይስጥ ፊደላት ስሞች ሲሆኑ ጸሐፊው በመዝሙሩ ውስጥ በእያንዳንዱ ስንኝ ላይ ተጠቅሞባቸዋል።

የውይይት ጥያቄ፥ መዝሙረ ዳዊት (25) አንብብ። በዚህ መዝሙር ውስጥ ያሉት ጥቅሶች ስንት ናቸው?

ሁለተኛ ደረጃ፥ አይሁድ በመዝሙራቱ ሁሉ ቁልፍ የሆነን ስንኝ በተለየ መንገድ ይደግሙ ነበር። እነዚህ መዝሙራት በአሁኑ ጊዜ በገጠሪቱ ኢትዮጵያ እንደሚደረገው ይጠቀሙባቸው ነበር። በኢትዮጵያ ባህላዊ የሆነ መዝሙር ሲዘመር ሕዝቡ መሪውን እየተከተለ እንደሚዘምረው ዓይነት ነው። 

የውይይት ጥያቄ፥ መዝሙር 136 አንብብ። በዚህ መዝሙር ውስጥ በተደጋጋሚ የምናገኘው ሐረግ የትኛው ነው?

አይሁድ ሥነ-ግጥምና ቅኔን ለተለያዩ ሁኔታዎች ይጠቀሙባቸው ነበር። በብሉይ ኪዳን የነበሩ የሥነ-ግጥምና ቅኔ ዓይነቶች አንዳንዶቹ ቀጥሉ ተዘርዝረዋል፡

  1. ታሪካዊ ግጥሞች፥ ዘኁልቁ 21፡14፡ ኢያሱ 10፡12-13 
  2. በጠላቶች ላይ ስለተገኘ ድል የቀረቡ ግጥሞች፥ ዘጸአት 15፡1-8
  3. ሰዎችን የሚረግሙ ግጥሞች፥ ዘኁልቁ 21፡27-30 
  4. በቀብር ሥነ-ሥርዓት የሚቀርቡ ግጥሞች፥ 2ኛ ሳሙኤል 1፡17-27
  5. መለኮታዊ ጥበብን የሚገልጡ ግጥሞች፥ መዝሙር 1 (37) 
  6. ለነገሥታት የሚቀርቡ ግጥሞች፥ መዝሙር (20) 
  7. እግዚአብሔርን ለማምለክ የሚቀርቡ ግጥሞች፣ መዝሙር 8 
  8. በእግዚአብሔር ላይ መታመንን የሚገልጡ ግጥሞች፥ መዝሙር (1)
  9. እግዚአብሔርን የሚያመሰግኑ ግጥሞች፥ መዝሙር (18) 
  10. የኃዘን ግጥሞች፥ መዝሙር(27)፣ 28) 
  11. ንስሐ መግባትን የሚገልጡ ግጥሞች፣ መዝሙር (32) 
  12. ስለ ፍቅር የተገጠሙ ግጥሞች፣ መኃልየ መኃልይ ዘሰሎሞን 4፡1-7 
  13. ስለ ጋብቻ የተገጠሙ ግጥሞች፥ መዝሙር (45) 
  14. የትንቢት ግጥሞች፥ ዘፍጥረት 49፡1-27። 

በመዝሙረ ዳዊት ውስጥ የሚገኙ ግጥሞች የሚነበቡ ብቻ አልነበሩም ነገር ግን መዝሙረ ዳዊት የአይሁድ የመዝሙር መጽሐፍ ነበር። እስራኤላውያን እግዚአብሔርን ለማምለክ ይረዳቸው ዘንድ የተጻፈ ነበር፤ ስለሆነም አብዛኛዎቹ በጉባኤያቸው እንዲዘመሩ የተጻፉ ነበሩ። ሌሎቹ ደግሞ ለእግዚአብሔር መሥዋዕት በሚያቀርቡበት ጊዜ የሚያገለግሉ ነበሩ። 

ግጥሞችን ለመተርጐም የሚረዱ መመሪያዎች 

  1. ግጥሞችና ቅኔዎች ታልመው የሚጻፉት ከአእምሮአችን ይልቅ ለስሜታችን ነው፤ ስለዚህ በሥነ-ግጥም አማካይነት ስሜታችን ጠልቆ እንዲሰማውና እንዲነካ መፍቀድ አለብን። እያንዳንዱን ቃልና አሳብ በአእምሮ እውቀት አስቀድመን ለመረዳት መሞከር የለብንም። ሥነ-ግጥምን በምናነብበት ጊዜ ጸሐፊው ግጥሙን በሚጽፍበት ወቅት የተሰማውን ስሜት እንዲሰማን ያስፈልጋል። ጽሑፉን በሚጽፍበት ጊዜ የነበረው ዝንባሌ ወይም ውስጣዊ ስሜት ምን እንደነበረ መረዳት ያስፈልገናል። በግጥሙ ውስጥ ሊገልጥ የፈለገው ስሜት ቁጣ፥ ፍቅር፥ አክብሮት፥ ምስጋና ወይም ኃዘን የመሳሰለውም መሆኑን ለመወሰን መሞከር አለብን። ይህም ግጥሙን በተሻለ ሁኔታ ለመረዳት ያስችለናል።

የውይይት ጥያቄ፥ መዝሙር (102) አንብብ። ሀ) የዚህ መዝሙር ጸሐፊ ይህንን መዝሙር በሚጽፍበት ጊዜ የነበረው ስሜት ምን ይመስልሃል? ለ) ይህን ነገር አንዳንድ ጊዜ በተመሳሳይ መንገድ ተሰምተህ የሚያውቀው እንዴት ነው?

  1. ግጥሞች ብዙውን ጊዜ የሚጻፉት በተምሳሌት እንጂ በቀጥተኛ ቋንቋ አይደለም። በሕይወት ውስጥ ተምሳሌታዊ እውነቶችን የሚገልጡ በርካታ ነገሮችን ይጠቀማል። ለምሳሌ፥ በመዝሙረ ዳዊት ምዕራፍ 1 ውስጥ ጸሐፊው ስለ ዛፎች፥ የውኃ ፈሳሾች፥ ገለባና ፍርድቤት ይናገራል። የጸሐፊው ዋና ፍላጎት እነዚህን ነገሮች መግለጥ አይደለም፤ ነገር ግን ጸሐፊው አንባቢዎቹ እንዲያውቁትና እንዲሰማቸው ወደሚፈልገው መንፈሳዊ እውነቶች የሚጠቁሙ ምልክቶች ናቸው። በግጥም ውስጥ፥ ጸሐፊዎች የሚናገሩአቸውን ነጥቦች አጉልቶ ለማሳየት ሲባል አንዳንድ ጊዜ የተጋነኑ የንግግር ዘይቤዎችን ይጠቀማሉ። ጸሐፊው የሚጽፈው፥ ሰዎች አሳቡን በሙሉ ይቀበሉታል በማለት አልነበረም። ለምሳሌ፥ በመዝሙር (42)፡3 ጸሐፊው በእርግጥ እንባውን እንደተመገበ መናገሩ ሳይሆን በገጠመው ከፍተኛ ኃዘን ምክንያት ብዙ እንዳለቀሰ መግለጡ ነው።

በሌላ ጊዜ ደግሞ ጸሐፊዎች ሰብአዊ ያልሆኑ ነገሮችን ልክ ሰብአዊ እንደሆኑ አድርገው ይናገራሉ። ለምሳሌ፥ በመዝሙር (85)፡10 ምሕረትና እውነት እንደ ሁለት ጓደኛሞች ሲገናኙና፥ ጽድቅና ሰላም ሲስማሙ እንመለከታለን። በሌላ ቦታ ደግሞ ዛፎችና ድንጋዮች እንደዘመሩና በእጆቻቸው እንዳጨበጨቡ ተጽፎ እናነባለን። እነዚህን ሁሉ ማድረግ የሚቻለው በሥነ- ግጥም ብቻ ነው።

ይህም ማለት ሥነ-ግጥምን በተለየ ሁኔታ መተርጐም ይኖርብናል ማለት ነው። የምናተኩረውም ቀጥተኛ ትርጕሙን በማግኘቱ ላይ ሳይሆን፥ በተምሳሌታዊ ትርጕሙ ላይ ነው፤ ለዚህ ነው ስለ እግዚአብሔር በምናነብበት ጊዜ እጆች፥ ዓይኖችና አፍ እንዳሉት ሆኖ የምንመለከተው። እግዚአብሔር መንፈስ እንደሆነና ሥጋዊ አካል እንደሌለው እናውቃለን። በሥነ- ግጥም ውስጥ ግን እግዚአብሔር ከሰው ሥጋዊ አካል ጋር ተነጻጻሮ ቀርቧል። በተጨማሪም እግዚአብሔር እረኛ፥ አምባ፥ ዓለትና መሸሸጊያ ተብሉ ተጠርቷል።

ሥነ-ግጥማዊ ይዘት ያላቸውን ጽሑፎች በሚገባ ለመረዳት ተምሳሌታዊ መግለጫ ሆኖ የቀረበውን ጉዳይ በሚገባ መረዳት ያስፈልጋል። እግዚአብሒር ዓለት ነው፥ መጠለያ ነው፥ እረኛ ነው ማለት ምን ማለት ነው? እነዚህ ተምሳሌታዊ አባባሉች ለጸሐፊውና ለመጀመሪያዎቹ ጻሐፊዎች ምን ትርጕም እንደነበራቸው በሚገባ ጠይቀን መረዳት አለብን። ዛሬ ለእኛ የሚሆነውን ተምሳሌታዊ አባባል እውነተኛ ትርጉም ለመረዳት የምንችለው ከዚህ በኋላ ብቻ ነው።

የውይይት ጥያቄ፥ እግዚአብሔር ዓለትና መሸሽጊያ ነው ማለት ምን ማለት ነው? መዝሙር (18)፡2፤ (31)፡2 ተመልከት። እነዚህን ቃላት በመጽሐፍ ቅዱስ መዝገበ ቃላት ውስጥ ተመልከት።

  1. በመዝሙረ ዳዊት ውስጥ የሚገኙ መዝሙሮች ብዙ ጊዜ ስሜቶቻችንን ለመግለጽ የተጻፉ ሙዚቃዊ ግጥሞች ናቸው። በአእምሮአዊ እውቀት ላይ የተመሠረቱ እውነቶችን ለመግለጽ የተጻፉ አይደሉም፤ ስለዚህ የመሠረታዊ እምነት ትምህርታችንን በግጥም ወይም በመዝሙር ላይ ከመመሥረት መጠንቀቅ ይኖርብናል።
  2. በግጥም መልክ በተጻፈ አንድ ጥቅስ ላይ ብዙ ትኩረት ማድረግ የለብንም። አንድ ግጥም ሲጻፍ እውነተኛው የጸሐፊው ትርጕም የሚገኘው በጠቅላላው ግጥም ውስጥ እንጂ በአንድ ጥቅስ ላይ አይደለም። በአንድ ጥቅስ ላይ ብዙ ካተኮርን፥ ጸሐፊው እንድናስብ ከሚፈልገው በላይ በመሄድ የጽሑፉን ሃሳብ ልንስት እንችላለን።
  3. ቢቻል ጸሐፊው ያንን ግጥም እንዲጽፍ ያስገደደው ወይም ያነሣሣው ነገር ምን እንደሆነ ለመወሰን ሞክር። አንዳንድ ጊዜ በግጥሙ መጀመሪያ ግጥሙ መቼ እንደተጻፈ የሚያሳይ ፍንጭ እናገኛለን። ለምሳሌ፥ መዝሙረ ዳዊት (51) የተጻፈው ዳዊት ከቤርሳቤህ ጋር ኃጢአት ካደረገ በኋላ ነው። ግጥሙ የተጻፈበትን ሁኔታ ማወቅ ግጥሙን የበለጠ ለመረዳት ይጠቅማል።
  4. አብዛኛዎቹ ሙዝሙራት በአምልኮና በእግዚአብሔር ላይ የሚያተኩሩ ስለሆኑ፥ በዚያ መዝሙር የቀረበው የእግዚአብሔር ሥዕላዊ ሁኔታ ምን እንደሆን ወስንና ለዚያ ባሕርይ ልብህ እግዚአብሔርን እንዲያመልክ ፍቀድለት።

ሥነግጥምን በትክክል ለመረዳት የሚከተሉትን አምስት ነገሮች ማድረግ ይጠቅማል፡- 

  1. በዚያ ግጥም ውስጥ ጸሐፊው ያለውን ስሜት ለመረዳት ሞክር። የግጥሙ ምሳሌ ሊያሳይ ወደሚሞክረው ስሜት ውስጥ ለመግባት ሞክር። በዓይነ ሕሊናህ ጸሐፊው የተመለከተውን ተመልከት፤ እርሱ የነካቸውን ነገሮች ለመንካትና የተሰማውን ስሜት ለማግኘት ሞክር።
  2. ጸሐፊው የተጠቀመባቸውን የተለያዩ ተምሳሌታዊ አባባሎች ለይተህ አውጣ። እነዚህን አባባሎች ዛሬ አንተ በተረዳኸው መንገድ ሳይሆን፥ ከእስራኤላውያን ግንዛቤ ጋር በሚዛመድ መልኩ ማወቅህን አረጋግጥ። ግልጽ ያልሆኑልህን ምሳሌዎች ለመረዳት የመጽሐፍ ቅዱስ መዝገበ ቃላት ወይም ትርጓሜ ለመጠቀም ሞክር። 
  3. ከምሳሌያዊ ወይም ከተምሳሌታዊ አባባሎቹ መካከል ጸሐፊው ሊያተኩርበት የሚሞክረው ክፍል የትኛው እንደሆን ወስን። ለምሳሌ፥ ጸሐፊው እግዚአብሔር ዓለት ነው የሚል ከሆነ፥ በዚህ አባባሉ ለማመልከት የፈለገው ነገር ምንድን ነው? እግዚአብሔር የማይለወጥና በማንኛውም ጊዜ ልንታመንበት የምንችል አምላክ እንደሆነ ነው ወይስ ጠንካራና ወደ እርሱ ጠልቀን ልንገባ የማንችል እንደሆን ነው? ማንኛውም ተምሳሌታዊ አባባል የሚገለጠውን ጉዳይ ሙሉ በሙሉ ሊወክል አይችልም፤ ስለዚህ ተምሳሌቱ የሚያመለክተውን ጉዳይ በመቀበል የማይመለከተውን ክፍል ግን መተውን ተማር።
  4. «ጸሐፊው ሌሎች ተምሳሌቶችን ትቶ ይህን የተጠቀመው ለምንድን ነው?» ብለህ ራስህን ጠይቅ፤ ይህ የተምሳሌቱን ትርጒም ለመረዳት ይጠቅምሃል።
  5. ተምሳሌቱን ከእውነተኛው ትምህርት ለመለየት መቻልህን አረጋግጥ። ተምሳሌቱን እንደ እውነተኛው ትምህርት ካየነው፥ መዝሙሩን በተሳሳተ መንገድ ልንተረጉመው እንችላለን። «ይህ ነገር ተምሳሌት ነው ወይስ እውነተኛው ጭብጥ?» ብለህ ራስህን ጠይቅ።

የውይይት ጥያቄ፥ መዝሙረ ዳዊት (42) አንብብ። ሀ) ጸሐፊው ይህንን መዝሙር በሚጽፍበት ጊዜ የነበረውን መሠረታዊ ስሜት ለመግለጽ አጭር ዐረፍተ ነገር ጻፍ። ለ) ጸሐፊው የፈለገው መሠረታዊ እውነት ምንድን ነው? 

(ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የብሉይ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)

Exit mobile version