Site icon

2ኛ ቆሮ. 10፡1-6

ጥያቄ 15. በቁጥር 2 ላይ “በዚያ እምነት ግን ከእናንተ ጋር ሆኜ እንዳልደፍር አለምናችኋለሁ” ሲል ምን ማለቱ እንዳሆነ ይህን ክፍል በጥንቃቄ በመመልከት አስረዳ። 

ጥያቄ 16. በቁጥር 3 ላይ ሐዋርያው በሰው ልማድ እመላለሳለሁ ሲል ምን ማለቱ ነው? 

ጥያቁ 17. በቁጥር 2 ላይ ሁለት ወገኖች ተጠቅሰዋል፤ ማንና ማን ናቸው? 

ቁጥር 1:- ሐዋርያው ስለመስጠት ያለውን ትምህርት ጨርሶ ሌላ ርዕስ ይከፍታል። ይህ ርእስ ከምዕራፍ 10 ጀምሮ እስከ ምዕራፍ 13 ይቀጥላል። በዚህ በቁጥር 1 «በእናንተ ዘንድ ሳለሁ ትሑት የሆንሁ» ይላል። ይህንም ያለው በአሽሙር ሲናገር ነው። ዝቅ ብለን በዚሁ ምዕራፍ በቁጥር 10 ላይ በቆሮንቶስ ቤተ ክርስቲያን ሾልከው የገቡት ሐሰተኛ አስተማሪዎች ጳውሎስን “መልእክቶቹስ ከባድና ኃይለኛ ናቸው ሰውነቱ ግን ሲታይ ደካማ ነው” እያሉ ያሙት ነበር። ስለዚህ ያንን ሐሜት በአሽሙር መልክ ይደግመዋል። 

ቁጥር 2፡- ይህ ክፍል አነጋገሩ ጥምዝምዝ ነው ግን ቀጥተኛ ትርጉም ስለሆነ በጥንቃቄ እንረዳው። ሃሳቡ ይህ ነው፡- … በሥጋ የምመላለስ እየመሰላቸው የሚንቁኝ በመካከላችሁ አሉ። በእነርሱ ላይ ልደፍር ሙሉ በሙሉ ተማምኜ እመጣለሁ። ነገር ግን በእነርሱ ላይ ልደፍር በተማመንኩበት ዓይነት ድፍረት በቀራችሁትም ላይ መድፈር አልፈልግምና እባካችሁ ጥፋታችሁን በማረም ከዚያ አድኑኝ፤ … የማለት አነጋገር ነው። 

«በዓለማዊ ልማድ» ቁጥር 2፤ «በሰው ልማድ» ቁጥር 3፤ «ሥጋዊ» ቁጥር 4፤ እነዚህ የተለያዩ ቃላት የሚተረጉሙት በግሪክኛ አንድ ዓይነት ቃል ነው፤ ያም፡- «ሥጋዊ» የሚል ቃል ነው። ስለዚህ ሦስቱንም ጥቅሶች በዚህ ቃል በመተካት ጥቅሱን እናብራራ። 

በሥጋ እንደምንመላለስ በሚቆጥሩን በአንዳንዶች ላይ አምኜ ልደፍር አስባለሁ፤ በዚያ እምነት ግን ከእናንተ ጋር ሆኜ እንዳልደፍር እለምናችኋለሁ። በሥጋ ምንም እንኳ የምንመላለስ ብንሆን በሥጋ አንዋጋም፤ የጦር ዕቃችን ሥጋዊ አይደለምና። 

እንግዲህ በቁጥር 3 ላይ ከላይ እንደተተረጎመው «በሥጋ ምንም እንኳ የምንመላለስ ብንሆን» ሲል በዚህ በሰውነት ነን ማለት ነው። ለምሳሌ በዮሐንስ 1፡14 ላይ «ቃል ሥጋ ሆነ» ያለው ዓይነት ሥጋ ማለት ነው እንጂ ሥጋ የኃጢአት ኑሮ ማለቱ አይደለም። የሐዋርያው ተቃዋሚዎች ግን «ጳውሎስ ሥጋዊ ነው» ሲሉ ኃጢአተኛ ነው ማለታቸው ነበር። እንግዲህ ነገራቸውን ዘወር ያደርግና ምንም እንኳ ሥጋ ለባሽ ብሆንም እንደእነርሱ ውሸትና ሐሜት በተሞላ መንገድ በሥጋ አልዋጋም ይላል። 

ሐዋርያው ሊዋጋ የተነሣው ሾልከው ከገቡት ሐሰተኛ አስተማሪዎች ጋር ነበር። ሐሰተኛ አስተማሪዎች ሾልከው ገብተው በጎችን አንዳይሰርቁ የቤተ ክርስቲያን አገልጋዮችና ሽማግሌዎች መዋጋት አለባቸው። አዳም ሰይጣን እገነት አንዳይገባ መዋጋትና ሚስቱን ማስጠንቀቅ ነበረበት! እንዲሁም በትንቢተ ዘካርያስ 3:7 ላይ እግዚአብሔር ሊቀ ካህኑን ኢያሱን «አደባባዮቼንም ትጠብቃለህ» ይለዋል። አደባባይ ማለትም መግቢያ በር ነው። ሰይጣንን እግዚአብሔር እንደገሠጸለት ኢያሱ ደግሞ የሰይጣን ተከታዮች የሆኑትን ሐሰተኛ አስተማሪዎች ሾልከው እንዳይገቡ መከላከል ነበረበት። እንዲሁም ሐዋርያው በቆሮንቶስ የገቡትን ወንበዴዎች ሊያባርር ተዘጋጀ። 

አንደኛው የሐሰተኛ አስተማሪዎች ጸባይ ቤተ ክርስቲያንን መበጥበጥና ሰላም መንሣት ነው። ሁለተኛው ጸባያቸው አስመስሎ መግባት ወይም መሹለክ ነው። በግልጽ እውነትን ተቀብለው ገብተው ሳይሆን በመጀመሪያ በግ መስለው ገብተው ነው በኋላ የተኩላነት ጸባያቸውን የሚያሳዩት። ሦስተኛ ጸባያቸው ለራሳቸው ተከታዮችን መሰብሰብ ነው። ቤተ ክርስቲያንን የመከፋፈል ኑፋቄያዊ ባሕርይ አላቸው። የሐዋርያት ሥራ 20፡29-30 ሐሰተኛ አስተማሪዎች ለራሳቸው ተከታዮችን ይሰበስባሉ ይላል። አራተኛው ጸባያቸው እውነትን በማጣመም ማታላል ነው። 

ጥያቄ 18. ለውይይትህ እንዲረዳህ በዚህ ከአንድ እስከ አራት በተዘረዘሩት መልክ የሚገጥሙ የሐሰተኛ አስተማሪዎችን ስም ዘርዝር! 

ሐዋርያው ዝቅ ብሎ በ11፡3 ላይ እነዚህ ሐሰተኛ አስተማሪዎች የቆሮንቶስን ቤተ ክርስቲያን ሰዎች ሰይጣን ሔዋንን አንዳሳታት እንዳያጣምሟቸው ያስጠነቅቃል። 

ከቁጥር 4-5፡- ሐዋርያው ውጊያውን በሥጋዊ መልክ ሳይሆን እውነትን በመግለጥ በእውነት መሣርያ ብቻ ለመዋጋት ይነሣል። ሐሰተኛ አስተማሪዎች ሥራቸው ሐሰት የተሞላበት ስለሆነ ከመንፈሳዊነታችን ወጥተን እንደእነርሱ በሥጋ እንድንዋጋ ሊያደርጉን ስለሚችሉ በጣም መጠንቀቅ አለብን። እነርሱ ሥጋዊ በሆኑ ከላይ ከአንድ እስከ አሪት በተዘረዘሩት ሲዋጉን በሥጋ በሆነ ስድብና ንዴት እንዳንወድቅ እንጠንቀቅ። በዚህ ዓይነት መንገድ በሥጋ ብንራመድ ጣታቸውን እየጠነቆሉ ምእመናንን ከእኛ ለመጐተት ይመቻቸዋል። 

የፈለጉትን ያህል እርኩሶች ቢሆኑም፥ ሐሰተኛ መምህራንን በመንፈሳዊ ዘይቤዎች በመታገዝ መዋጋት አለብን። ሰይጣን በእነርሱ በመጠቀም ሰዎችን ከእውነት እንዲኮበልሉ ያደርጋል። ጳውሎስ በመንፈስ ቅዱስ አማካኝነት ለእኛ የተሰጠውን ኃይል ያስታውሰናል። በዚህ ኃይል በመጠቀም ነው የሰይጣንንና የሐሰተኛ መምህራንን ምሽግ? ልናፈራርስ የምንችለው። ለማሸነፍ ፈቃዳችንንና አእምሮአችንን በጥንቃቄ በመጠበቅ መዘጋጃት ይገባናል። ሙሉ በሙሉ በኢየሱስ ክርስቶስ ቁጥጥር ሥር መሆን አለብን፤ በተጨማሪም ለእርሱ ታዛዦች መሆን አለብን። ይህ ካልሆነ ግን እንሸነፋለን። 

ቁጥር 6፡- መታዘዛችሁ በተፈጸመ ጊዜ ማለቱ የእውነተኞች አማኞች ለእውነተኛው መሪ መታዘዝ ማለት ነው። ይህ ከተፈጸመ በኋላ ሐሰተኞችን መቋቋም ይቻላል። ስለዚህ ሐዋርያው ቆሮንቶስ ቤተ ክርስቲያን ከመድረሱ በፊት ምእመናኑ በመንፈሳቸው ተዘጋጅተው እንዲጠብቁት ይመክራል። ከዚያም በአንድ ልብ ሐሰተኞችን ለመቋቋም ይዘጋጃል። 

ጥያቄ 19. ሀ/ እውነተኞቹን መምህራን ከሐሰተኞቹ መምህራን ልንለይ የምንችልባቸውን መንገዶች በዝርዝር ጻፍ። 

ለ/ የሀሰተኛ መምህራንን ትምህርት ልንከላከል የምንችልበትን መመሪያ በዝርዝር ጻፍ።

Exit mobile version