Site icon

2ኛ ቆሮ. 12:11-21

ጥያቄ 15. በቁጥር 11 ላይ «እናንተ እኔን ልታመሰግኑ ይገባ ነበርና» ሲል ምን ማለቱ ነው? 

ጥያቄ 16. በቁጥር 13 «ይህን በደሌን ይቅር በሉኝ» ሲል ምን ማለቱ ነው? በደሉ ምን ነበር? 

ጥያቄ 17. በቁጥር 16 ላይ «ነገር ግን ሸንጋይ ሆኜ በተንኮል ያዝኋችሁ» ሲል ምን ማለቱ እንደሆነ አብራራ። 

ጥያቁ 18. ከቁጥር 19 እስከ ቁጥር 21 ሐዋርያው ወደ ቆሮንቶስ በተመለሰ ጊዜ ይደርስብኛል ብሎ የፈራውን ነገር አብራራ። 

ቁጥር 11-13:- ሐዋርያው ስለራሱ አገልግሎት እራሱን መደገፍ አያስፈልገውም ነበር። የአገልግሎቱ ተጠቃሚ የሆኑት የቆሮንቶስ ክርስቲያኖች ሊከራከሩለት ይገባ ነበር። ግን የጠላቶቹን ክስ በመስማት ስለራሱ እንዲናገር አደረጉት፤ በዚህም ቅር እንደተሰኘ ይነገራቸዋል፡፡ ስለአገልግሎቱ እነሱ በእርግጥ ያውቃሉ፤ ምክንያቱም በመካከላቸው የጳውሎስ ሐዋርያነት በብዙ ተአምራት ተረጋግጦላቸዋል፡፡ 

በቆሮንቶስና በሌሎቹ አብያተ ክርስቲያናት መካከል የነበረው ልዩነት፥ ጳውሎስ የቆሮንቶስን ሰዎች ገንዘብ በመጠየቅ ሸክም ሊሆንባቸው አለመፈለጉ ብቻ ነው። 

ክቁጥር 14-18- ሐዋርያው ወደ ቆሮንቶስ በሚሄድበት ጊዜ እንዳማይከብድባቸው ያረጋገጥላቸዋል። የሚፈልገው ገንዘባቸውን ሳይሆን እነርሱን ነው። ይህም ገዘቡን ሳይቀር ሕይወቱን እንኳ የሚሠዋላቸው መሆኑን ይመሰክርላቸዋል። እንደ ጥሩ አባት ለልጆቹ ያጠራቅማል እንጂ በልጆቹ ላይ ሸክም አይሆንም። 

በቁጥር 16 ላይ «ሸንጋይ ሆኜ በተንኮል ያዘኋችሁ» ማለቱ ሐሰተኛ አስተማሪዎቹ የሰነዘሩበትን ክስ በአሽሙር ሲያከሽፍ ነው። ምናልባት እንዲህ ብለው ይሆናል፤ «ጳውሎስ በቀጥታ ገንዘብ ከእናንተ ያልተቀበለው ለኢየሩሳሌም ድሆች ብሎ የሰበሰበውን እኪሱ እያስገባ ነው»። 

በሚከተሉት ጥቅሶች (ቁጥር 17ና 18) ራሱ ጳውሎስም ገንዘቡን እንዲሰበስቡ የላካቸውም በታማኝነት እንደነበሩ ያስታውሳቸዋል። ችግር ከተነሣ በኋላ ለችግርና ለሐሜት መፍትሔ ለመፈለገ ከመራወጥ አስቀድሞ ጥንቃቄ ማድረግ አስፈላጊ እንደሆነ ከዚህ ከሐዋርያው ሕይወት እንማር። 

ከቁጥር 19-21:- በቁጥር 19 ላይ «ለእናንተ ስለራሳችን እንድንመልስ ሁልጊዜ ይመስላችኋልን?» ማለቱ ሐዋርያው ይህንን ስለራሱ ንጽሕና አጥብቆ የቆሮንቶስን ሰዎች ለማሳመን መናገሩ እነርሱ ዳኛ ሆነው እርሱ ተከሳሽ ሆኖ በእነርሱ ፊት አቤቱታ ማቅረቡ አለመሆኑን ማስታወቁ ነው። ይህንም ያደረገው እነርሱ በእርሱ እንዳይሰናከሉ ለእነርሱ ጥቅም እንጂ በእነርሱ ዘንድ ንጹሕ ሆና መታየት ለእርሱ አስፈላጊ ነገር ሆኖ አልነበረም። ራሱን ግን በእግዚአብሔር ፊት ማቅረብና ፍርድን ከእግዚአብሔር  መጠበቅ ያስፈልገው እንደነበር ያስታውቃቸዋል። 

በቁጥር 20 እና 21 በፊት የደረሰበት አሁንም እንዳይደርስበት ይፈራ እንደነበር ይናገራል። በፊት ሊጎበኛቸው በሄደ ጊዜ ብዙዎች በኃጢአት ወድቀው አገኛቸው። በዝሙት በመከፋፈል በመጣላት። አሁን ግን እንደዚያ ሆነው ቢያገኛቸው ጥብቅ ቅጣት እንደሚያደርስባቸውና እርሱም በእነርሱ ውድቀት ከባድ ኃዘን እንደሚደርስበት ይገልጻል። 

Exit mobile version