Site icon

2ኛ ቆሮ. 11:16-21

ጥያቄ 1. በቁጥር 1 ላይ በሞኝነቴ ታገሡኝ ይላል፤ አሁን ደግሞ በቁጥር 16 ላይ “ለማንም ሞኝ የሆንሁ አይምሰለው” ሲል በሁለቱ መካከል አስታራቂ ሃሳብ ስጥ። 

ጥያቄ 2. ሐዋርያው ደብዳቤዎቹን ይጽፍ የነበረው በመንፈስ ቅዱስ መሪነት ነው፤ በቁጥር 17 ላይ ያለውን ንግግር ከዚህ ጋር አስታርቅ። 

ጥያቄ 3. በቁጥር 20 የቆሮንቶስ ሰዎች ከሐሰተኛ አስተማሪዎች የተቀበሏቸውን ግፎች ይዘረዝራል፤ ምን ምን ናቸው? 

ምንም እንኳ በቁጥር 1 ላይ «በጥቂቱ ሞኝነቴ ታገሱኝ» ቢልም በእርግጥ ሞኝ ሆና እንዳልነበረ በዚህ በቁጥር 16 ላይ ያረጋግጣል። ግን እነርሱ ይህን በመናገሩ እንደሞኝ ከቆጠሩት «እንደ ሞኝ እንኳ ሆኜ ተቀበሉኝ» እያለ በአሽሙር ይናገራል። 

በቁጥር 17 ላይ እንደዚያ ስለራሱ በመናገር ሞኝ የመሆን ዝንባሌ ሲያሳይ የክርስቶስን ምሳሌ ይዞ ሳይሆን እዚያን በሥጋ ይመኩ የነበሩትን ሐሰተኞች በገዛ መሣሪያቸው ለማጋለጥ የወሰደው እርምጃ ብቻ ነበር። ስለዚህ “በሞኝነቴ እንጂ ጌታ እንዳዘዘኝ አልናገርም» ይላል። የተናገረው በመንፈስ ቅዱስ ተመርቶ አይደለም ማለት ሳይሆን፥ ነገር ግን የዚህ ዓይነቱ ስለራስ መናገር የሥጋ ፀባይ እንጂ የክርስቶስ ፀባይ አይደላም ማለቱ ነው። 

በቁጥር 18 ላይ “ብዙዎች በዓለማዊ ነገር ስለሚመኩ እኔ ደግሞ እመካለሁ” ይላል። በቁጥር 1 ላይ «በጥቂት» እመካለሁ ይላል። ሐሰተኞች በሥጋ ይመካሉ፤ እርሱ ግን ምንም እንኳ እንደእነርሱ ስለራሱ ቢናገር እነርሱን በማጋለጥ የቆሮንቶስን ክርስቲያኖች ከእነርሱ ለማላቀቅ ነበር። ይህ ዓይነት ታክቲክ በምሳሌ 26፡5 “ለራሱ ጠቢብ የሆነ እንዳይመስለው ለሰነፍ አንደ ስንፍናው መልስለት» በሚለው መሠረት ነው። 

ከቁጥር 19-20፡- የጳውሎስ አሽሙር አሁን አይሏል። እነዚያን ሐሰተኞች ሲያጉላሉአቸው ከታገሷቸው እርሱ በጥቂቱ ሐሰተኞችን ለማሳጣት ያሳየውን ሞኝነት መታገሥ ሊከብዳቸው አይገባም! እነዚያ ሐሰተኞቹ፡- 

1ኛ / ባሪያዎች ያድርገዋቸው ነበር፤ ይህም ማለት የሐሰት ትምህርት በማስተማር ክርስቶስ በወንጌል ከሰጣቸው ነፃነት ወደ ባርነት ይጕትቷቸው ነበር። ምናልባት ወደ ተሻረው ወደ ኦሪት ሥርዓት ማለት ሊሆን ይችላል። 

2ኛ / ይበሏቸው ነበር፤ ይህም ማለት ገንዘብ ወዳድ ስለነበሩ ከመጠን በላይ ገንዘብ ይሰበስቡ ነበር። ከዚህ ጋር ማቴ.28፡ 14ን አስተያይ። 

3ኛ / ይቀሟቸው ነበር፤ ይህም ማለት በማታለል ሌሎች ሲጠቀሙባችሁ ማለት ነው። 

4ኛ/ «ማንም ቢኮራባችሁ»፤ 

5ኛ / «ማንም ፊታችሁን በጥፊ ቢመታው» ሲል በባህላችሁ የሕዝብ መሪዎች የነበሩ ዝቅተኞቻቸውን በጥፊ ያስመቱ ወይም ይመቱ እንደነበር ያመለክታል፤ (የሐዋ.23፡2፤ 1ኛ ቆሮ. 4፡11፤ 1ኛ ጢሞ.3፡3፤ ቲቶ 1:7፤ ማቴ.5፡39፤ 1ኛ ጴጥ.2:19)። 

እንግዲህ የቆሮንቶስ ሰዎች ይህንን ሁሉ ከሐሰተኞች አስተማሪዎች እጅ በትዕግሥት ከተቀበሉ ከሐዋርያው ጳውሎስ «ጥቂት ሞኝነት» መታገሥ ሊከብዳቸው አይገባም። 

ጥያቄ 4. ዛሬ ተከታዮቻቸውን የሚያሳዝኑና የሚያናድዱ ሐሰተኛ መምህራን ስንት ናቸው? 

ቁጥር 21:- ጳውሎስ እንደ ሐሰተኞቹ አስተማሪዎች የቆሮንቶስን ቤተ ክርስቲያን ስላልተጫና «ደካማ ሆኜባችኋለሁ» በማለት በአሸሙር ይናገራል!

Exit mobile version