ሰውና ሰይጣን በእግዚአብሔር ግዛት ላይ የሚያሳዩት ዓመፅ ሁሉ በሺህ ዓመት ማብቂያ ላይ ለመጨረሻ ጊዜ ይታያል። እግዚአብሔር በሺሁ ዓመታት ውስጥ መልካምን ነገር ሁሉ ለሰዎች በመስጠት ምድር በጌታ እውቀት እንድትሞላ ያደርጋል። ከዚህ ሁሉ በረከት በኋላ ሰዎች እግዚአብሔርን በግልጥ መቃወማቸው ስለሚከሰት፥ ውጫዊ ለውጥ የሰውን መሠረታዊ ፍላጎት የማያሟላ መሆኑ ይረጋገጣል። ሰው በዳግም ልደት የልብ ለውጥ እስካላደረገ ድረስ ውስጡ ዓመፀኛ እንደሆነ ይኖራል። በዘመኑ መጨረሻ ከሚወለዱት ልጆች ብዙዎቹ የንጉሡን (የክርስቶስን) ጸጋ ለመቀበል አይሹም። ውጫዊ ሁኔታቸው ሲታይ ግን ለክርስቶስ የሚገዙ ይመስላሉ። ነገር ግን በዘመናት ሁሉ እንደታየው፥ ሰዎች አዳኙን እንዲቀበሉ እግዚአብሔር አያስገድድም። ብዙ በሺህ ዓመቱ አገዛዝ ማብቂያ ላይ የሚኖሩ ሰዎች ከርስቶስን እንደ መንግሥቱ ገዥ በማየት ቢታዘዙትም፥ ለደኅንነታቸው አልተቀበሉትም።
ሰይጣን ሲፈታ ነው በክርስቶስ ላይ የሚካሄደው ዓመፅ የሚጀምረው (ራእይ 20፡7-9)። ሰይጣን ሲፈታም መንግሥታትን ያስታል (ከመታሠሩ በፊት እንደነበረም)፤ በተጽዕኖውም ዓለምን ያዳርሳል። ዓመፀኞች ኃይላቸውን አስተባብረው የክርስቶስ አስተዳደር ማዕከል የሆነችውን ኢየሩሳሌም ለመውረር ሲዘጋጁ፤ ሰይጣንም ለዓመፅ ይጠናከራል። እነርሱም ቅድስቲቱን ከተማ ለማጥቃት ሲቃጡ፥ እግዚአብሔር ከሰማይ እሳት በመላክ ያጠፋቸዋል። የዓመፃው ተባባሪዎች ሁሉ በእሳት ይጠፋሉ። ይህም በጌታ ላይ የሚነሳውን ተቃውሞ ለዘላለም ያስወግዳል። ሰይጣንም ወደ እሳት ባሕር ይጣል (ራእይ 20፡10)። ይህ የመጨረሻው ዓመፅ ተሀድሶ ከዳግም ልደት፥ መሻሻልም ከመለወጥ ጋር አንድ አለመሆናቸውን ያመለክታል። የመለኮታዊ ጸጋ አሠራር የሚያስፈልገው የሰው ልጅ ልብ መሆኑን በድጋሚ ያረጋግጣል።
ምንጭ፡- “የመጽሐፍ ቅዱስ ሥርዓተ ትምህርት ጥናት”፣ በዶክተር ቻርልስ ሲ. ራይሪ ተጽፎ፣ በሲሳይ ደሳለኝ የተተረጎመ እና በየላፕስሊ/ብሩክስ ፋውንዴሽን የታተመ ነው፡፡ ለዚህ ድንቅ አገልግሎታቸው እግዚአብሔር ይባርካቸው፡፡ ይህን ጽሁፍ ኮፒ እና ፕሪንት አድርጎ መጠቀም ይቻላል፤ ሆኖም ጽሁፉን መለወጥና ለሽያጭ ማዋል በሕግ የተከለከለ ነው፡፡
