Site icon

በብሉይ ኪዳን የክርስቶስ ተምሳሌቶች

በብሉይ ኪዳን ውስጥ ብዙ የክርስቶስ ተምሳሌቶች አሉ። «ተምሳሌት» ማለት እግዚአብሔር ወደ ፊት እንዲመጣ ስላቀደው ሰው ወይም ነገር አመልካች ምስል ነው። የመጽሐፍ ቅዱስ ተማሪዎች እነዚህን በብሉይ ኪዳን ውስጥ የሚገኙ ተምሳሌቶችን ለይተው ትርጉም በመስጠት ረገድ ትልቅ ጥንቃቄ ማድረግ ይኖርባቸዋል። እንደዚሁም አንዳንድ ጊዜ በብሉይ ኪዳን ውስጥ ባሉ ሰዎች፥ ክስተቶች፥ ቁሳቁሶችና በአዲስ ኪዳን ውስጥ ባሉ ሰዎችና ነገሮች መካከል ተመሳሳይነትን በማጤን የፈለጉትን ተምሳሌት እንዳገኙ በማሰብ ቸኩለው ወዲያው ወደ ውሳኔ ይደርሳሉ። ይሁን እንጂ፥ በብሉይ ኪዳን ውስጥ ያገኘናቸው ተምሳሌቶች ወይም አመልካቾች እግዚአብሔር ለአዲስ ኪዳን ተምሳሌቶች እንዲሆኑ ያቀዳቸው ለመሆናቸው በዚህ ረገድ እርግጠኞች መሆን አንችልም። እርግጠኞች መሆን የምንችለው፥ አዲስ ኪዳን ተምሳሌቶችን ለይቶ ሲያሳውቀን ብቻ ነው። ለምሳሌ፡-ዕብራውያን ከ3፡7 እስከ 4፡11 ያለው የእስራኤላውያን ወደ ከነዓን መግባት፥ በአዲስ ኪዳን ውስጥ የአማኞች ወደ ደኅንነት ተስፋ የመግባታቸው ተምሳሌት መሆኑን ይገልጽልናል። ስለሆነም፥ አዲስ ኪዳን በብሉይ ኪዳን ውስጥ የሚገኝ ሰው ክስተት ወይም ነገር ተምሳሌት ነው ብሎ ካላረጋገጠ በስተቀር የመጽሐፍ ቅዱስ ተማሪው ማለት የሚችለው ተምሳሌት ሳይሆን አይቀርም ከማለት ያለፈ አይደለም። 

በመሠረቱ በብሉይ ኪዳን ውስጥ ለክርስቶስ ተምሳሌት ሆነው ይቆማሉ ተብለው የተጠቀሱትን በሙሉ በዝርዝር ማጥናት አይቻልም። እንዲያውም ኢየሱስ ክርስቶስ በመጽሐፍ ቅዱስ እያንዳንዱ ገጽ ላይ ይገኛል መባሉ ይታወቃል። እንግዲህ ነገሩ ይህ ከሆነ፥ በብሉይ ኪዳን ውስጥ ለክርስቶስ ተምሳሌት ወይም አመልካች የሆኑትን አጥርቶ ለማጥናት የሕይወት ዘመናችንን ይጠይቃል። በዚህ ፈንታ እኛ ዛሬ የምናጠናው በብሉይ ኪዳን ውስጥ የክርስቶስን አመልካቾች ወይም ተምሳሌቶች ከሆኑት መካከል የተረጋገጡትን ብቻ ይሆናል። እነዚህም አዲስ ኪዳን የክርስቶስ ተምሳሌቶች ወይም አመልካቾች አድርጎ የለያቸው የብሉይ ኪዳን የክርስቶስ ተምሳሌቶች ናቸው። በተጨማሪም በብሉይ ኪዳን የክርስቶስ ተምሳሌት ይሆናሉ ተብለው የተወሰዱትንና የመጽሐፍ ቅዱስ ተማሪዎችም ይሆናሉ ብለው የሚስማሙባቸውን በአጭሩ እንመለከታቸዋለን። 

1. አንዳንድ የክርስቶስ ተምሳሌቶች 

አዲስ ኪዳን በርካታ ሰዎችን፥ ክስተቶችንና ነገሮችን እንደ ክርስቶስ ተምሳሌቶች አድርጎ ይጠቅሳል። ስለዚህ እነዚህን የብሉይ ኪዳን የክርስቶስ ተምሳሌቶች በማጥናት ብዙ ትምህርቶችን ልናገኝ እንችላለን። 

1.1 ሰብአዊ ተምሳሌቶች 

ጥያቄ፡– ሮሜ 5፡12-14፥ 18-19 አንብቡ። ሀ) በዚ9 ክፍለ ምንባብ ውስጥ የክርስቶስ ተምሳሌት የሆነው ማን ነው? ለ) ይህ ሰው በምን መንገድ በክርስቶስ ይመሰላል? ሐ) ሮሜ 5፡15-7 አንብቡ። ደግሞስ ይህ ሰው በምን ሁኔታ ነው በክርስቶስ የማይመሰለው? 

የክርስቶስ የመጀመሪያው ተምሳሌት የሆነው ሰው አዳም ነው። አዳም የፈጸመው ተግባር ከእርሱ በኋላ የመጡትን ትውልዶች ሁሉ የነካ በመሆኑ፥ በክርስቶስ ይመሰላል። ስለሆነም፥ አዳም ኃጢአት ከሠራ በኋላ፥ የእርሱ ኃጢአት ለዘሮቹ ሁሉ ተዳረሰ። የክርስቶስ በመስቀል ላይ ሞት በእምነት የእርሱ ተከታይ የሆኑትን ሁሉ «ጻድቃን» ያደረገ (5፡18) እና «የመታዘዝ» (5፡19) ተግባር ነው። ነገር ግን በአዳም ብቸኛ ድርጊትና በክርስቶስ ብቸኛ ድርጊት መካከል ልዩነት አለ። ሐዋርያው ጳውሎስ የአዳም ብቸኛ ድርጊት ሞትንና ፍርድ በሰው ሁሉ ላይ እንዳመጣ፥ የክርስቶስ ብቸኛ ሥራ ግን ለሚከተሉት ሁሉ ሕይወትንና ጽድቅን እንደ ሰጠ ይነግረናል። እንግዲህ ከዚህ በመነሣት በብሉይ ኪዳን ውስጥ የክርስቶስን ተምሳሌቶች ስንመለከት ከክርስቶስ የሚለዩበት ጠንካራ ነጥብ እንዳላቸው እናስተውላለን። ምንም እንኳን ተመሳሳይነት ቢኖርም በአንጻሩ ደግሞ ልዩነት ይታያል። 

ጥያቄ፡- ዕብራውያን 4፡14-5፡10 አንብቡ። ሀ) ክርስቶስ ሊቀ ካህናት እንዴት ! ይመሰላል? ለ) ከሊቀ ካህናት የሚለየውስ እንዴት ነው? 

በብሉይ ኪዳን ውስጥ የታየው የአሮን ክህነት ሌላው የክርስቶስ ተምሳሌት ነው። ታዲያ እንደ እነዚህ ካህናት ክርስቶስ የክህነቱን ሥልጣን ራሱ አልወሰደም፥ ነገር ግን ለሥልጣን ክህነቱ በእግዚአብሔር ተሾመ እንጂ። ልክ እንደ ካህናቱ እርሱም ስለ ኃጢአት ስጦታዎችንና መሥዋዕቶችን ለማቅረብ የተሾመ ነበር። እንደ ካህናቱ ኃጢአትን ለመፈጸም ተፈትኖ ከአጋጠመውም ፈተና በአሸናፊነት ለመውጣት በጸሎት ታግሏል። እንደ ካህናቱ ፈተና በደረሰበት ጊዜ ቀና የሆነውን ለመፈጸም በመምረጥ ለእግዚአብሔር በእውነተኛ መታዘዝ ምን እንደሆነ ተምሯል። እንደ ብሉይ ኪዳን ካህናት እርሱም በኃጢአት ተፈትኖ ስለነበር ወደ እርሱ ዘንድ ለሚመጡ ኃጢአተኞች ይራራላቸዋል። ምክንያቱም እርሱም በኃጢአት ተፈትኖ ነበርና ነው። ይሁን እንጂ ክርስቶስ የአሮንን ፈለግ የተከተለ ካህን አልነበረም። የእርሱ ክህነት የመልክ ጼዴቅን ሥርዓተ ክህነት የተከተለ ነበር። መልከ ጼዴቅ በብሉይ ኪዳን ውስጥ የታወቀ ሌላው የክርስቶስ ተምሳሌት ነው። 

ጥያቄ፡- ዕብራውያን 7፡1-4፥ 17-25 እንብቡ። ክርስቶስ መልከ ጼዴቅን የሚመስለው እንዴት ነበር? 

አብርሃም ከብዙ ነገሥታት ጋር ተዋግቶ ድል በማድረግ እንደ ተመለሰ፥ የሳሌም ንጉሥ ተቀበለው (ዘፍጥረት 14)፡፡ የዕብራውያን ጸሐፊ ይህን ሰው አስፈላጊ የክርስቶስ ተምሳሌት አድርጎ ጠቅሶታል። መልከ ጼዴቅ ልክ እንደ ክርስቶስ ንጉሥና ካህን ነበር። እንደዚሁም እንደ ክርስቶስ ሁሉ እርሱም የእድቅና የሰላም ንጉሥ ነበር «መልከ ጼዴቅ» የሚለው ስም ራሱ «የጽድቅ ንጉሥ» ማለት ነው። መልከ ጼዴቅ የሳሌም ከተማ ንጉሥ ነበር። «ሳሌም» ማለት ሰላም ማለት ነው። የኢየሩሳሌም ጥንታዊ መጠሪያም ነበር። ምንም እንኳን ኦሪት ዘፍጥረት የብዙ ታዋቂ ሰዎችን ቤተሰብና የዘር ሐረግ የሚዘረዝር መጽሐፍ ቢሆንም፥ የመልከ ጼዴቅን የዘር ሐረግ አይጠቅስም። መጽሐፉ የዚህን ሰው አባት፥ እናትና ቤተሰብ ሳይጠቅስና ስለ ሞቱ ሳይናገር ያልፈዋል። በታሪኩ ውስጥ ድንገት ብቅ ብሎ ጥፍት ያለ ሰው ነው። በዚህ ሁኔታው በእግዚአብሔር ልጅ ተመስሎ መጀመሪያና መጨረሻ የለውም። ኢየሱስ በፍጹም ስለማይሞት ምን ጊዜም ሊቀ ካህናት ሊሆን ይችላል። 

አንዳንድ የትምህርተ መለኮት ተማሪዎች መልከ ጼዴቅ ከክርስቶስ ተምሳሌትነት ይልቃል ይላሉ። በእነርሱ እምነት መልከ ጼዴቅ የራሱ የክርስቶስ ቅድመ-ተሠገብአዊ መገለጥ ነው። ይህ እንግዲህ የዕብራውያን ጸሐፊ ካመላከተው ጋር ሲመዘን፥ አንደኛው የግንዛቤ አቅጣጫ ሊሆን ይችላል። ነገር ን ወደ መሠረቱ ወደ ዘፍጥረት ስንሄድ፥ መልከ ጼዴቅ ራሱ መለኮታዊ መሆኑን ታሪኩ አይጠቅስም። የእግዚአብሔር ልጅ በሥጋ ወደ ምድር ከመምጣቱ በፊት በታዩት መገለጦች፥ በሰውም ይሁን በመልአክ አምሳል ይገለጥና እርሱ ራሱ አምላክ ለመሆኑ ግልጽ የሆነ ጠቋሚ ነገር ያሳይ ነበር። ዳሩ ግን ዘፍጥረት ምዕራፍ 14 መልከ ጼዴቅ አምላክ ለመሆኑ ምንም ፍንጭ አይሰጥም። ስለዚህ መልከ ጼዴቅ ፍጹም፥ የማይሻር የክርስቶስ ተምሳሌት የሆነ ትልቅ የጽድቅና የሰላም ንጉሥ ነበር ብሎ ማጠቃለሉ የላቀ ድምዳሜ ይመስላል። 

1.2 ነገሮች ወይም ዕቃዎች 

ጥያቄ፡- ዕብራውያን 9፡-14 19-23 10፡1-4 አንብቡ፡፡ የመገናኛው ድንኳን ሥርዓትና መሥዋዕቱ እንዴት የክርስቶስ ተምሳሌት ይሆናሉ? 

ዕብራውያን ምዕራፍ 9 እና 10 በግልጽ እንደሚያስገነዝቡት የመገናኛው ድንኳንና የመሥዋዕቱ ሥርዓቶች የክርስቶስ የሕይወቱና የሞቱ ጠቃሚ ተምሳሌቶች ናቸው። ሌሉች የአዲስ ኪዳን ክፍሎችም ኢየሱስ በብሉይ ኪዳን ውስጥ በነበሩት መሥዋዕቶች እንደሚመሰል ገልጸዋል (ዮሐንስ 1፡29፤ የሐዋ. 8፡32፤ ሮሜ 3፡5፤ 1ኛ ጴጥሮስ 1፡19፤ ራእይ 5፡12)። የብሉይ ኪዳን መሥዋዕቶች የሚያበረክቱት አገልግሎት፥ ሥነ ሥርዓታዊ (ውጪአዊ የኀጢአት መንጻትን) መስጠትና (ዕብ 9፡13) ሰዎች ኃጢአታቸው ከእግዚአብሔር እንዳልለያቸው ማሳሰብ (ዕብ 10፡፡) ነበር። ኀጢአትን ፍጹም ሊያስወግዱ የሚችሉ አልነበሩም (ዕብራውያን 10፡4)። ተግባራቸው በሞቱ ለአንዴና ለሁልጊዜ የኃጢአት ይቅርታን በማስገኘት (ዕብ. 9፡26-28)፥ ፍጹም መሥዋዕት ወደሆነው ክርስቶስ አቅጣጫን ማመልከት ነበር። የመሥዋዕት አቀራረብ ሥርዓቱ ፍጹም ለሆነው የክርስቶስ መሥዋዕት ምሳሌ ስለሚሆንበት በዝርዝር እናጠናም። ነገር ግን በዘሌዋውያንና በዕብራውያን የትመማ መጻሕፍት በመጠቀም በግላችሁ ሙሉ ጥናት ልታካሂዱ ትችላላችሁ። 

ጥያቄ፡- ዮሐንስ 3፡14 አንብቡ። ሀ) በዚህ ክፍለ ምንባብ ውስጥ ለክርስቶስ ተምሳሌት ሆኖ የተገኘው ምንድን ነው? ለ) ይህ ነገር የክርስቶስ ተምሳሌት የሚሆነው በምን አኳኋን ነው? 

በዮሐንስ 3 ላይ እንዴት ዳግም መወለድ እንደሚችል ኢየሱስ ለኒቆዲሞስ ይነግረዋል። ዳግም መወለድ መሠረቱ በምድረ በዳ እንደተሰቀለው የነሐስ እባብ የሰው ልጅም የመሰቀሉ እውነታ ነው ብሎ ነገረው፡፡ ኢየሱስም ይህን ሲናገር በዘኁልቁ ምዕራፍ 21፡4-9 ያለውን ክፍል መጥቀሱ ነው። የእስራኤል ልጆች በእግዚአብሔርና በሙሴ ላይ ስላጉረመረሙ፥ እግዚአብሔር ሊቀጣቸው መርዛም እባብ ሰደደባቸው። በዚህ ጊዜ ሕዝቡ ከኃጢአቱ ስለ ተመለሰ፥ ሙሴ የናስ እባብ ሠርቶ በድንኳኖቻቸው መካከል እንዲሰቅል እግዚአብሔር አዘዘው። ከዚህ በኋላ እባብ የሚነክሰው ሰው እግዚአብሔር በሚሰጠው ፈውስ በማመን የነሐሱን እባብ ሲመለከት ከሞት ይተርፍ ነበር። ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስም ሊናገር ሙሴ በምድረ በዳ የነሐስ እባብ እንደ ሰቀለና ሕዝቡ በሕይወት እንደ ኖረ ሁሉ፥ ሰዎች የዘላለም ሕይወት ያገኙ ዘንድ የሰው ልጅ ይሰቀላል አለ። በተመሳሳይ መንገድ እግዚአብሔር ሰዎች ከሞት ድነው ሥጋዊ ሕይወት እንዲያገኙ እንዳደረገው ሁሉ፥ የደኅንነትን መንገድ አዘጋጅቶ የዘላለምን ሕይወት ሰጣቸው። እናም በተመሳሳይ መንገድ እስራኤላውያን በእግዚአብሔር ታምነው ወደ ተሰቀለው እባብ እያዩ ደኅንነትን እንደ ፈለጉ ሁሉ፥ ሰዎች ደግሞ የእግዚአብሔርን የማዳኛ መንገድ የክርስቶስን መስቀል በማመን ከኀጢአታቸው ለመዳን ወደ እርሱ ሊመለከቱ ይገባል። የነሐሱ እባብ አስደናቂ የሆነ የክርስቶስና የደኅንነቱ ተምሳሌት ነው። 

ጥያቄ፡- 1ኛ ቆሮንቶስ 10፡1-5 አንብቡ። ሀ) እግዚአብሔር ለእስራኤላውያን ምን አስደናቂ መንፈሳዊ በረከት ሰጣቸው? ለ) በአብዛኛዎቹ እስራኤላውያን ላይ ምን ደረሰ? 

ሐዋርያው ጳውሎስ በ1ኛ ቆሮንቶስ ምዕራፍ 10 ላይ የቆሮንቶስ አማኞች የነበራቸው ታላቅ መንፈሳዊ በረከት ስለፈጸሙት ኃጢአት በእግዚአብሔር ከመቀጣት እንደማያድናቸው ያስጠነቅቃል። እግዚአብሔር ቀደም ሲል የባረካቸውን ኃጢአት ስለሠሩ እንደ ቀጣ ለማሳየት ወደ እስራኤል አመለከተ። እስራኤላውያን በምድረ በዳ እያሉ እግዚአብሔር ከጥፋት ያዳናቸውና የሚያስፈልጋቸውን ሁሉ ያደረገላቸው ሕዝብ ናቸው። ስለሆነም በብዙ መንገዶች ባርኮአቸው ነበር። ከግብጻውያን እጅ ሊያድናቸው ብሉ ቀይ ባሕርን ለሁለት ከፈለው። በደመና ዓምድ መራቸው። እንዲሁም የሚበሉትን መና ከሰማይ የሚጠጡትን ውኃ ከዓለት ሰጣቸው (ዘፀአት 17፡1-7፤ ዘኁልቁ 20፡2-1ህ፡፡ ሐዋርያው ጳውሎስ የምድረ በዳው ዓለት የክርስቶስ ምሳሌ ነው ይላል። ምን ማለቱ እንደሆነ ግን በግልጽ አላስረዳም፡ ምናልባትም ከዓለት የፈለቀው ውኃ ለእስራኤል ሕዝብ ሕይወትንና ርካታን እንደ ሰጣቸው ሁሉ ክርስቶስ ስለሚሰጠው ደኅንነትና የሕይወት መብዛት መናገሩ ይሆናል። ሆኖም እዚህ ላይ የጳውሎስ ዋንኛ ዓላማ ማስጠንቀቅ ነው። ምንም እንኳን እስራኤላውያን ይህን መሰሉን በረከት ከእግዚአብሔር ዘንድ ቢያገኙም፥ በሠሩት ኃጢአት ግን ቅጣታቸውን ተቀብለዋል። በዚሁ መሠረት እግዚአብሔር ኃጢአተኛ ቤተ ክርስቲያንን ይቀጣል። ልክ በቆርንቶስ በነበረችው ቤተ ክርስቲያን ላይ እንደ ፈጸመው ማለት ነው። ምንም እንኳን በርካታ የእግዚአብሔርን መንፈሳዊ በረከተች ሲቀበሉም ስፈፅሙት በደል ከቅጣት አላመለጡም። 

1.3 ሁኔታዎች (ክስተቶች) 

ጥያቄ፡- 1ኛ ቆሮንቶስ 5፡6-8 አንብቡ። ሀ) ጳውሎስ የክርስቶስ ተምሳሌት ነው ያለው ምንድን ነው? ለ) ክርስቲያኖች በቅድስና ሕይወት ይኖሩ ዘንድ ይህ እንዴት ሊቀሰቅሳቸው ይችላል? 

ሐዋርያው ጳውሎስ በ1ኛ ቆሮንቶስ በመላው ቤተ ክርስቲያናቸው ውስጥ ያለውን ኀጢአትና ትዕቢት ማስወገድ እንዳለባቸው ያስጠነቅቃቸዋል። በ1ኛ ቆሮንቶስ በምዕራፍ 5 ላይ ከአባቱ ሚስት ጋር የግብረ-ሥጋ ግንኙነት በአደረገው ሰው ላይ የሥነ ሥርዓት እርምጃ እንዲወስዱ አጥብቆ ያሳስባቸዋል። እነዚህን የመሰሉትን ኀጢአቶች ለማስወገድ ይችሉ ዘንድ ሊያበረታታቸው ብሎ የእይሁድን የፋሲካ አከባበር ምሳሌ እድርጎ ያቀርብላቸዋል። አይሁዳውያን የፋሲካን በዓል ከማክበራቸው በፊት እርሾ ከቤታቸው ማስወገድ እንዳለባቸው ሁሉ አማኞችም ከግል ሕይወታቸውና ከቤተ ክርስቲያን ማንኛውንም ኀጢአት ማስወገድ እንዳለባቸው ያስጠነቅቃቸዋል። አይሁድ እርሾ ያልገባበትን ቂጣ በፋሲካ ቀን እንደሚመገቡ ሁሉ፥ ክርስቲያን አማኞችም ኃጢአት የሌለበትን ሕይወት ሊኖሩ ይገባል። እንዲህ ባለው መንገድ መኖር ለምን አስፈለጋቸው? ለዚህ ምክንያት የእስራኤል በኩር ልጆች በመጀመሪያው የፋሲካ ዕለት በተሠዉ የበግ ጠቦቶች እንደ ተዋጁ ሁሉ፥ ክርስቲያን አማኞችም በተመሳሳይ መንገድ በክርስቶስ በመዋጀታቸው ነው። የፋሲካው በግ መሥዋዕትነት፥ የክርስቶስ የመስቀል ሞት ተምሳሌት ነው። ክርስቶስ የኀጢአት ይቅርታን ለማስገኘት ሲል፥ በፋሲካ ቀን መሥዋዕት የሆነ ፍጹም የእግዚአብሔር የፋሲካ በግ ነው። ይህ የመሥዋዕትነት ሞቱ የቅድስና ሕይወት ያለበትን አገልግሎት እየሰጠን ለመኖር የሚቀሰቅሰን ሊሆን ይገባል። 

2. ይሆናሉ ተብለው የሚታሰቡ የክርስቶስ ተምሳሌቶች 

ከእነዚህ በአዲስ ኪዳን ውስጥ ከተገለጹት የክርስቶስ ተምሳሌቶች በተጨማሪ፥ አዲስ ኪዳን ያልጠቀሳቸው በርካታዎች በብሉይ ኪዳን ውስጥ ይገኛሉ። ምን ያህል የሚሆኑ የክርስቶስ ተምሳሌቶች በብሉይ ኪዳን ውስጥ እንዳሉ በዝርዝር ማወቅ ያዳግታል። በብሉይ ኪዳን ውስጥ ሰዎችን ወደ ክርስቶስ ለማመልከት የተጠቀመባቸውን ሰዎች፥ ሁኔታዎችና ነገሮች ሊያውቅ የሚችል መንፈስ ቅዱስ ብቻ ነው። ሆኖም በብሉይ ኪዳን ውስጥ የሚገኙ ሰዎች፥ ነገሮችና ሁኔታዎች የክርስቶስ ተምሳሌቶች መሆናቸው በአዲስ ኪዳን ውስጥ ተለይቶ ባይጠቀስም፥ ተምሳሌትነታቸውን የመጽሐፍ ቅዱስ ተማሪዎች ይስማሙበታል። 

2.1 ሰዎች 

ጥያቄ፡– የያዕቆብ ልጅ ስለሆነውና ታሪኩ ከዘፍጥረት 37 እስከ 50 ተጽፎ ስለሚገኘው ስለ ዮሴፍ ታሪክ አስቡ። በዚህ ክፍል ዮሴፍ በምን አኳኋን በኢየሱስ ይመሰላል? 

አዲስ ኪዳን ባምንም አኳኋን ዮሴፍ የኢየሱስ ተምሳሌት ነው ሲል ለይቶ አይናገርም። አብዛኛዎቹ የመጽሐፍ ቅዱስ ተማሪዎች ግን፥ ዮሴፍ በተለያዩ ሁኔታዎች፥ ከክርስቶስ ሕይወትና አገልግሎት ጋር ተመሳሳይነት አለው ሲሉ ይስማማሉ። ዮሴፍ ወንድሞቹ ኃጢአት እንደ ሠሩ እንደ መሰከረባቸውና በኋላም እንደ ብሉት፥ ኢየሱስም የወገኖቹን ኃጢአት ስለ አጋለጠና ስለ መሰከረባቸው ጠሉት። እንዲሁም ዮሴፍን ወንድሞቹ እንደ ናቁት ሁሉ፥ ክርስቶስም በራሱ ሕዝብ ዘንድ ተናቀ። ዮሴፍ በገዛ ወንድሞቹ ለባርነት ለአረማውያን እንደ ተሰጠ ሁሉ፥ ኢየሱስም ከደቀ መዛሙርቱ በአንዱ ተሽጦ ለአረማውያን አልፎ ተሰጠ። እግዚአብሔር የዮሴፍን አልፎ መሰጠት ቤተሰቡን ለማዳን በአስደናቂ ሁኔታ እንደ ተጠቀመ ሁሉ፥ እግዚአብሔር የኢየሱስንም ሞት ለሕዝቡ ደኅንነት ተጠቅሞበታል። እንደዚሁም ዮሴፍ፥ ኃጢአትን እንዲፈጽም ቢፈተንም ራሱን ለኃጢአት እንዳልሰጠ ሁሉ፥ ክርስቶስም ተፈትኖ በፈተናው አልተሸነፈም። ስለዚህ ዮሴፍ በመንፈስ ቅዱስ የታቀደ የክርስቶስ ተምሳሌት ነበር ማለት ይቻላል። 

2.2 ሁኔታዎች 

ጥያቄ፡- ዘፍጥረት 3፡8-1፥ 21 አንብቡ። ) አዳምና ሔዋን ራቁትነታቸውን እንዴት ሊሸፍኑት ሞከሩ? ለ) እግዚእብሔርስ እርቃናቸውን እንዴት ሸፈነላቸው? 

ዘፍጥረት ምዕራፍ 3 ስለ አዳምና ሔዋን ኃጢአት ይገልጻል። አዳምና ሔዋን መልካምንና ክፉን ከሚያሳውቀው ዛፍ ፍሬ ከበሉ በኋላ፥ ራቁታቸውን እንደሆኑ አወቁ። ይህን ኃጢአት ከመፈጸማቸው በፊት፥ ነጻነትን በተጎናጸፈ ግብረገባዊነትና ንጽሕና ውስጥ ይኖሩ ነበር። ዳሩ ግን አሁን ኃጢአተኛች መሆናቸውን ስለተረዱ፥ ራቁታቸውን በእግዚአብሔር ፊት ሊቆሙ እንደማይችሉ ገባቸው። በመሆኑም እርቃናቸውን ለመሸፈን ከዛፍ ቅጠል ልብስ ሠሩ። እግዚአብሔርም ለኃጢአታቸው ፍርዱን ከሰጠ በኋላ፥ የተለየ ልብስ አለበሳቸው። ልብሱንም ከእንስሳት ቆዳ ሠራላቸው። በእርግጥ ከእንስሳ ቆዳ ልብስ ሲሠራላቸው፥ እንስሳት መግደል የግድ አስፈላጊ ነበር። አዳምና ሔዋንን ከኃጢአት ሐፍረታቸው ለመሸፈን ደም መፍሰስ ነበረበት። ምንም እንኳን አዲስ ኪዳን ይህን ድርጊት ለክርስቶስ ተምሳሌት አድርጎ ባይወስደውም፥ የመጽሐፍ ቅዱስ ተማሪዎች ይህ ሁኔታ ክርስቶስ የሰዎችን ሁሉ የኃጢአት ዋጋ ለመክፈል ሲል በመስቀል ላይ ተሰቅሎ ለመሞቱ ተምሳሌት ሆኖ ሊቀርብ እንደሚችል ይስማሙበታል። ኃጢአትም እንዲቀጣ ሞት መኖር አለበት። የዚህ እንስሳ መገደል የአዳምንና የሔዋን ኃጢአትና ሐፍረት ብቻ ነበር የሸፈነው። የክርስቶስ ሞት ግን ለሚያምኑ ሁሉ ለዘላለም ኀጢአትንና ሐፍረትን ያስወግድላቸዋል። 

ጥያቄ፡- ሀ) ከእነዚህ የክርስቶስ ተምሳሌቶች ውስጥ፥ በአካባቢአችሁ መንፈሳዊ እውነታን ለማስተማር የትኞቹ አመቺነት አላቸው? ለ) በእነዚህ ተምሳሌቶች በመጠቀም ምን መንፈሳዊ እውነታዎችን ማስተማር ትችላላችሁ? 

ስለ ክርስቶስ ተምሳሌቶች በማጥናት የምንማራቸውና የምናስተምራቸው ብዙ ጠቃሚ ትምህርቶች አሉ። ስለ አጻም ካደረግነው ጥናት ተነሥተን ሁልጊዜ፥ ኀጢአታችን መዘዝ እንደሚኖረው እንነዘባለን። ከአሮን ታሪክ በመነሣት፥ እኛ በምንፈተንበትና ድካም በሚሰማን ጊዜ፥ ጌታ ኢየሱስ እንደሚራራልን እንረዳለን። ከመልከ ጼዴቅም በመነሣት ኀጢአት በምንሠራበት ጊዜ፥ ኢየሱስ ይቅር ሊለን ከእኛ ጋር እንደሚሆን እንማራለን። የነሐስ እባቡን ታሪክ ስንመለከት ደግሞ ደኅንነት በእምነት እንጂ፥ እኛ በምናከናውነው መልካም ሥራ እንደማይገኝ እንነዘባለን። ከቆሮንቶስ ሰዎችና ከእስራኤላውያን ታሪክ ደግሞ፥ እግዚአብሔር ትልቅ በረከትን ቢሰጠንም፥ በኀጢአታችን እንደሚገሥጸንና እኛም ይህን አውቀን ኃጢአትን ከመካከላችን ለማስወገድ ከልብ መጣር እንዳለብን እንረዳለን። እነዚህ የክርስቶስ ተምሳሌቶች እያንዳንዳቸው በሕይወታችን ውስጥ ልንጠቀምባቸው የሚገቡን ከፍተኛ ዋጋ ያላቸው መንፈሳዊ ትምህርቶችን ያስተምሩናል።

ምንጭ፡- “አስተምህሮ ክርስቶስና ደኅንነት”፤ ጽሑፍ፣ በዶ/ር ስቲቭ ስራውስ፤ ትርጉም በኃይሉ ልመንህ

Exit mobile version