Site icon

የኢየሱስ ተከታዮች እንደ መሆናችን እንዴት መመላለስ እንዳለብን (ዕብ.13፡1-25)

ጸሐፊው አይሁዳውያን ክርስቲያኖች እግዚአብሔርን የሚያስከብር ሕይወት ለመኖር ሊያደርጉ የሚገዷቸውን አንዳንድ ነጥቦች በመዘርዘር መልእክቱን ያጠቃልላል። እነዚህ ትምህርቶች ሩጫችንን በሚገባ እንዳንሮጥ የሚከተሉት መሰናክሎች ወይም ኃጢአቶች በመንፈሳዊ ሩጫችን ውስጥ መኖር አለመኖራቸውን ለማረጋገጥ ደግመን ደጋግመን የምንመለከታቸው ነገሮች ናቸው።

ሀ) በክርስቶስ ወንድሞቻችሁና እኅቶቻችሁን ውደዱ።

ለ) ምንም ያህል ስደት ቢበዛም፥ እማኞችን በእንግድነት ለመቀበል ትጉ።

ሐ) በኢየሱስ በማመናቸው ምክንያት የታሰሩትን ወገኖች አትርሷቸው።

መ) የጋብቻ ሕይወታችሁን ጠብቁ። የወሲብ ሕይወታችሁ ንጹሕ ይሁን። እግዚአብሔር ከሚጠላቸው ኃጢአቶች አንዱ ከትዳር ውጭ የሚፈጸም የግብረ ሥጋ ግንኙነት ነው።

ወ) የገንዘብ ፍቅር ሕይወታችሁን እንዳይቆጣጠር ተጠንቀቁ። እግዚአብሔር በሰጣችሁ መርካትን ተማሩ። ሁልጊዜም ተጨማሪ ገንዘብ ለማግኘት አትጣሩ። ሁኔታችሁ ምንም ዓይነት ቢሆን፥ እግዚአብሔር ከእናንተ ጋር እንደሆነና እንደሚረዳችሁ ተገንዘቡ።

ረ) መንፈሳዊ ሕይወታችሁን የመጠበቅ አስቸጋሪ አገልግሎት የሚወጡትን የቤተ ክርስቲያን መሪዎቻችሁን አክብሩ።

ሰ) ራሳችሁን ከሐሰተኛ አስተማሪዎች ጠብቁ። በውጫዊ ሕጎችና ደንቦች ላይ ትኩረት አትስጡ። ነገር ግን ከኢየሱስ ጋር ያላችሁን ግንኙነት እንደ መሠዊያ ቁጠሩ። ይህም ተምሳሌታዊ ሲሆን፥ የማያምኑ ሰዎች ከእርሱ መንፈሳዊ ምግብ ሊያገኙ አይችሉም ነበር። (ይህ ከኢየሱስ ጋር ኅብረት የማድረጋችን መሠዊያ የብሉይ ኪዳን ካህናት ከእንስሳት መሥዋዕቶች ወስደው ለመብላት ከነበራቸው ዕድል የሚሻል ነው። ዘሌዋ. 7፡28-34)።

ሸ) ለክርስቶስ ስም ስደትና ውርደትን ለመቀበል ፈቃደኞች ሁኑ። በብሉይ ኪዳን ዘመን የኃጢአት መሥዋዕት በሚቀርብበት ጊዜ ኃጢአት የፈጸሙት ሰዎች በሚሠዋው እንስሳ ላይ እጆቻቸውን ይጭኑ ነበር። እንስሳው ከታረደ በኋላ፥ ሥጋው በመሠዊያው ላይ ይቃጠላል። ቆዳውና የሆድ ዕቃው ግን ከከተማ ውጭ ተወስዶ ይቃጠሳል (ዘሌዋ. 4፡1-12)። የዕብራውያን ጸሐፊ፥ ይህ በኢየሱስ ላይ የተፈጸመውን ሁኔታ የሚያብራራ መሆኑን ይናገራል። ክርስቶስ የተሰቀለው ከኢየሩሳሌም ከተማ ውጭ ነበር። የአይሁድ ክርስቲኖችም ተመሳሳይ ምርጫ ማድረግ ነበረባቸው። ሰዎችን ለማስደሰት ከሌሎች አይሁዶች ጋር ተባብረው አሕዛብ ክርስቲያኖችን ለማሳደድና ስደትን ፈርተው ክርስቶስን ለመተው በመወሰን፥ በከተማይቱ ውስጥ ለመቆየት ይመርጣሉ? ወይስ የመስቀሉን ስደት የሚያስከትልባቸው ቢሆንም እንኳን ከማኅበረሰቡ ወጥተው ከክርስቶስ ጋር ይተባበራሉ? ከከተማይቱ ወጥተው ከክርስቶስ ጋር የሚተባበሩና ስደትን የሚቀበሉ ሰዎች የተሻለች የመንግሥተ ሰማይ ከተማ እንደ ተዘጋጀችላቸው ያውቃሉ።

ቀ) ሁኔታዎች ያሻቸውን ቅርጽ ቢይዙም እግዚአብሔርን ማመስገናችሁን ቀጥሉ። ከእንግዲህ ወዲህ የእንስሳት መሥዋዕቶች አያስፈልጉንም። አሁን ለእግዚአብሔር ከምናቀርባቸው መሥዋዕቶች አንዱ ምስጋና ነው።

በ) ለሌሎች መልካም ማድረጋችሁን ቀጥሉ። እግዚአብሔር ከእኛ የሚፈልገው ሌላኛው መሥዋዕት ይኼ ነውና።

ተ) ከእግዚአብሔር ሥልጣንን ለተቀበሉና በእግዚአብሔር ፊት ለነፍሳችሁ ተጠያቂዎች ለሆኑት የቤተ ክርስቲያን መሪዎች ተገዙ። በዚህም አገልግሎታቸው ከትግል ይልቅ ደስታ እንዲሆን አድርጉ። ይህም የኋላ ኋላ እናንተኑ ይጠቅማችኋል። ምክንያቱም ደስ በሚሰኙበት ጊዜ የተሻለ አገልግሎት ሊሰጧችሁ ይችላሉ።

የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) እነዚህን በሕይወታችን ውስጥ ልንለማመዳቸው የሚገቡንን ነገሮችን ከልስ። እነዚህ ነገሮች ጠቃሚ የሆኑት ለምንድን ነው? በዚህ ክፍል ውስጥ ከተሰጡት ትእዛዛት አንጻር ሕይወትህን ገምግም። ጸሐፊው በዚህ ክፍል ውስጥ ከቀረበው ትምህርት ጋር የሚዛመድ ሕይወት ትመራ ዘንድ በሕይወትህ ውስጥ ሊለወጥ የሚገባው ነገር ምንድን ነው?

ማጠቃለያ (ዕብ. 13፡18-25)

ጸሐፊው አንባቢያኑ በጸሎት እንዲያግዙት በመጸለይ መልእክቱን ይደመድማል። በቅርቡ ከጢሞቴዎስ ጋር መጥቶ እንደሚጎበኛቸው ይነግራቸዋል። ከኢጣሊያ የሆኑት ወደሚያቀርቡትም ሰላምታ ያልፋል፡፡

ጸሐፊው ለእነዚህ አይሁዳውያን አማኞችና ለእኛ በሚሰጠው ቡራኬ ትምህርቱን ያጠቃልላል። ሀ) የሰላም ምንጭና ኢየሱስን ከሞት ያስነሣው እግዚአብሔር አብና ለ) የእግዚአብሔር በጎች እረኛ የሆነው ስለ ክርስቶስ ለእግዚአብሔር ደስ የሚያሰኘውን ሕይወት እንድንኖር በውስጣችን እንዲሠሩና እርሱን ለማገልገል ብቁዎች እንድንሆን እንዲያስችሉን ይጠይቃል።

የውይይት ጥያቄ፡- ዕብ. 13፡20-21 አንብብ። እግዚአብሔር ለራስህ ሳይሆን ለራሱ ክብር በሕይወትህ ውስጥ እንዲሠራ ጠይቀው።

(ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የአዲስ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)

Exit mobile version