ኢየሱስ በምድራዊ ሕይወቱ መጨረሻ ላይ የጌታን እራት ሥርዓት አስጀመረ። የጌታ እራት እንዴት እንደ ተጀመረ በአዲስ ኪዳን ሰአራት ዋና ዋና ምንባቦች ውስጥ ተጽፎ ይገኛል። ማቴ. 26፡17 30፤ ማር. 14፡17-26፤ ሉቃስ 22፡14-20 እና በ1ኛ ቆሮ. 1፡23-34። (እነዚህን ምንባቦች በዝግታ ለማንበብ ጊዜ ውሰድ።
ከመሰቀሉ በፊት በነበረችው ሌሊት ኢየሱስ የአይሁድን የቂጣ በዓል (ፋሲካን) ሊያከብር ከደቀ መዛሙርቱ ጋር ተሰበሰበ። የፋሲካ በዓል እግዚአብሔር በአስገራሚ ማዳኑ አይሁዶችን ከግብፅ ባርነት ነፃ ያወጣበትን ቀን በማሰብ የሚከበር ነበር (ዘጸአት 12፡1-30)። ኢየሱስም አዲስ ፋሲካ ሊጀምር የተቃረበበት ወቅት ነበር። በማግስቱ በመስቀል ላይ ሲሞት ለአይሁዶች ብቻ ሳይሆን፥ ለሚያምኑበት ሕዝብ ሁሉ ከኃጢአት ነፃ መሆንን አምጥቷል።
ደቀ መዛሙርት በዙሪያው እንዳሉ ኢየሱስ የጌታን እራት ሥርዓት ወሰነ። የእርሱ ተከታዮችም የጌታን እራት ሥርዓት በዘመናት ሁሉ እንዲፈጽሙ ተናግሯል። ይህ ሥርዓት ኢየሱስ ዘላለማዊ መንግሥቱን ለመመሥረት እስከሚመለስበት ጊዜ ድረስ ይቀጥላል። በፋሲካ በዓል መጨረሻም ኢየሱስ እንጀራን ያዘ። ሲቆርሰውም ይህ ስለ እነርሱ የሚቆረሰው አካሉ መሆኑን ነገራቸው። እንጀራውንም ሲበሉ ኢየሱስን ማስታወስ አለባቸው። ከዚያም ኢየሱስ ወይን ያለበትን ዋንጫ አንስቶ ደቀ መዛሙርት እንዲጠጡት ሰጣቸው። ወይኑም
ለኃጢአታቸው ይቅርታ የሚፈሰው ደሙ መሆኑን ነገራቸው። ደቀ መዛሙርት መጠጣት የነበረባቸው ኢየሱስን በማስታወስ ነው። በቀጣዩ ቀን ኢየሱስ በመስቀል ላይ ሲሞት ሥጋው ተቆረሰ፤ ደሙም ፈሰሰ። እርሱ ስለ እያንዳንዳችን ሲል ሞተ። የሥጋው መቆረስና የደሙ መፍሰስ በእግዚአብሔርና በሰው መካከል የተደረገ የኃጢአት ይቅርታ ማስገኛ ኪዳን መሆኑን ኢየሱስ ተናግሯል።
ምንጭ፡- “የጌታ እራት”፣ በቲም ፌሎስ ተጽፎ፣ ተሾመ ነጋሽ የተተረጎመ እና በኤስ አይ ኤም የታተመ ነው፡፡ ለዚህ ድንቅ አገልግሎታቸው እግዚአብሔር ይባርካቸው፡፡ ይህን ጽሁፍ ኮፒ እና ፕሪንት አድርጎ መጠቀም ይቻላል፤ ሆኖም ጽሁፉን መለወጥና ለሽያጭ ማዋል በሕግ የተከለከለ ነው፡፡
