Site icon

ኢየሱስ እንደ ጌታ 

በመላው አዲስ ኪዳን ውስጥ ብዙ ጊዜ ለኢየሱስ መጠሪያነት ያገለገለ የማዕረግ ስም «ጌታ» የሚለው ነው። ጳውሎስ ኢየሱስን «ጌታ» ብሎ መጥራት በጣም ይወድ ነበር። ይሁንና ጳውሎስና ሌሎች የአዲስ ኪዳን ጸሐፊዎች ኢየሱስን «ጌታ» ብለው ሊጠሩት ምን ማለታቸው ነበር? 

1. «ጌታ» የሚለው ቃል በመጽሐፍ ቅዱስና በጥንቱ ዓለም እንዴት ነበር በጥቅም ላይ ይውል የነበረው? 

በግሪክ ቋንቋ «ጌታ» የሚለው ቃል፥ ኩሪዮስ (kurios) ይባላል። ኩሪዮስ የተባለው ቃል እዲስ ኪዳን በተጻፈበት ጊዜ በብዙ የተለያዩ መንገዶች በጥቅም ላይ ውሎአል። ይህ ቃል፥ የባሪያ ባለቤት፥ የቤት ጌታ (ባል) ወይም የሴት ልጅ አባት (ጌታ) ሊሆን ይችላል። በእነዚህ ገለጻዎች መሠረት ቃሉ፥ በሌላው ላይ ባለሥልጣንና ተቆጣጣሪ የሆነ ማለት ነው። ወይም ኩሪዮስ (kurios) ማለት በቀላሉ በክብርና በጨዋ አጠራር፥ አድራሻ ላይ የሚያሳፍረው ነው። 

በብሉይ ኪዳኑ የግሪክ ትርጉም፥ ኩሪዮስ የሚለው የብዙ ቃላት ትርጓሜ ሆኖ ይገኛል። 

ጥያቄ፡- መዝሙር 110፡1 አንብቡ። ተናጋሪውን ለመግለጽ ምን ቃል በጥቅም ላይ ውሎአል? አድማጭንስ ለመግለጽ ምን ቃል በጥቅም ላይ ዋለ? 

አዶናይና ያህዌ የተባሉትን ሁለት የዕብራይስጥ ቃላትን ወደ ግሪክ ቋንቋ ለመተርጎም ይኸው ኩሪዮስ (kurios) የተባለ ቃል በጥቅም ላይ ውሎአል። አዶናይ የሚለው ቃል ዕብራውያን «ጌታ» ለማለት እንደ አጠቃላይ መጠሪያ አድርገው የተጠቀሙበት ስም ነው። ይህ ቃል የተለመደ የእግዚአብሔር መጠሪያ ቢሆንም፥ «ጌታ ወይም ባለቤትም» ማለት ይሆናል። (ያህዌ) የሚለው ቃል የእግዚአብሔር የግል መጠሪያ ስሙ ነው። ዕብራውያን ያህዌ የሚለውን ቃል እጅግ ከማክበራቸው የተነሣ፥ ብሉይ ኪዳንን በሚያነቡበት ጊዜ ይህ ቃል ሲያጋጥማቸው ሳያነቡት ያልፉ ነበር። ታዲያ በዚህ ቃል ፈንታ አዶናይ የሚለውን ተክተው ይጠቀሙ ነበር። በመዝሙር 10፡1 ላይ በአማርኛው ትርጉም «እግዚአብሔር ጌታዬን ተናገረው» ይላል። በዕብራይስጡ ግን፥ «ያህዌ ለእኔ አዶናይ ተናገረ» ይላል። የዕብራይስጡ የብሉይ ኪዳን የግሪኩ ትርጉም፥ «ኩሪዮስ ለእኔ ኩሪዮስ ተናገረ» ይላል። አንዱ የግሪክ ቃል (ኩሪዮስ) በሁለት የተለያዩ መንገዶች እንዴት በጥቅም ላይ እንደሚውል ይህ ጥቅስ ጥሩ ምሳሌ ነው። እንዲሁም «ያህዌ» እና የእውነተኛ እግዚአብሔርን የግል መጠሪያዎች «አዶናይ» ማለትም ጌታዬ የሚሉትን ለመተርጎም በጥቅም ላይ ውሎአል። ስለዚህ አይሁዳውያን ግሪክኛ ይናገሩ ወይም የግሪኩን የብሉይ ኪዳን ትርጉም ያነቡ በነበሩበት ጊዜ፥ «ኩሪዮስ» የሚለውን ቃል በብዙ መንገዶች ይጠቀሙበት ነበር። እናም «ኩሪዮስ» ማለት፥ «ያህዌ» ማለትም «ጌታ እግዚአብሔር» ወይም «ባለቤት» የሚል ትርጉም ይዞ ነበር። 

ኩሪዮስ (kurios) የሚለው ቃል ሐሰተኛ አማልክትንና ጣዖታትን ለመግለጥና እንዲሁም አንዳንድ የግሪክና የሮማውያንን ገዢዎችን ለማመልከትም አገልግሎእል። ኩሪዮስ የተሰኘው ይህ ቃል የግሪክ ንጉሥንና የሮማውያን ንጉሠ ነገሥትን ለመግለጽ አገልግሎት ላይ በዋለበት ወቅት ሁለት አሳቦች የያዘ ይመስላል። በመጀመሪያ፥ የንጉሡን ፍጹም ኃይልና ሥልጣን እንዲገልጽ ነው። እርሱም ከሁሉ በላይ የላቀ ጌታና የመንግሥቱም ገዥ ነው። ይህ ገለጻ ንጉሠ ነገሥቱ መለኮታዊም ነው የሚል ትርጉምም ያዘለ ነው። ብዙዎቹ ነገሥታትና አፄዎች ከሞቱ በኋላ እንደ አማልክት ይቆጠሩ ነበር። በሕይወትም በነበሩ ጊዜ ሕዝቦቻቸው ወደ አማልክትነት ይለወጣሉ ብለው ያስቡ ነበር። ነገሥታቱና አፄዎቹም ቢሆኑ በበኩላቸው ሕዝቡ እንደ መለኮታውያን አድርጎ እንዲመለከታቸው ያበረታቱ ነበር። ይህንንም ያደርጉ የነበሩት ድርጊቱ ታላቅነታቸውን በማጉላት ሕዝብ እንዲያመልካቸው ከማድረጉም በላይ መንግሥታቸውንም እንደሚያስተ ባብርላቸው በማመን ነበር። ስለዚህ ኩሪዮስ የሚለው ቃል በሕዝቡ ላይ ፍጹም የሆነ ሥልጣንና ኃይል የነበራቸውንና እንዲሁም መለኮታውያን ነን የሚሉትን የግሪክ ነገሥታትንና አፄዎችን ማንነት ለመግለጽ አገልግሎት ላይ የዋለ ቃል ነበር። 

ነገር ግን የአዲስ ኪዳን ደራሲያን ኢየሱስን፥ «ጌታ» ሲሉት ምን ማለታቸው ነው? 

2. ኢየሱስ እንደ «ጌታ» 

2.1 ጌታ ኢየሱስ መምህር ነው። 

ጥያቄ፡- ሉቃስ 9፡59-60 አንብቡ። በዚህ ክፍል ስሙ ያልተጠቀለው ደቀ መዝሙር ኢየሱስን «ጌታ ሆይ» ብሎ ሲጠራው ምን ማለቱ ይመስላችኋል? 

በወንጌሎች ውስጥ ሰዎች ብዙ ጊዜ ኢየሱስን «ጌታ» ብለው በሚጠሩበት ጊዜ «መምህር» ብለው መጥራታቸው ነው። በሌላ አነጋገር፥ አዶናይ ወይም ያህዌ ማለታቸው አይደለም። ነገር ግን እርሱ መምህራቸውና መሪያቸው ስለሆነ የሚታዘዙለትና የሚነግራቸውን ሁሉ የሚፈጽሙለት መሆናቸውን መናገራቸው ነው። አንዳንድ ጊዜ መምህር ብለው በመጥራት ፈንታ ጌታ (የአክብሮት መግለጫ ብቻ) ብለው ይጠሩታል። በማቴዎስ 8፡21 ኢየሱስን እንደ መምህሩ ሳይቆጥረው «ጌታ» ብቻ ብሎ የጠራው ሰው ለዚህ ጥሩ ምሳሌ ነው። ይህ ሰው በመጀመሪያ ወደ ኢየሱስ በመጣ ጊዜ፥ ኢየሱስ መምህሩ እንደሆነ አስቦ ይሆናል፥ ነገር ግን ሊታዘዘው ፈቃደኛ አልነበረም። ስለዚህ ኢየሱስን ኩሪዮላ (kurios) ብሎ ሲጠራው፥ ምናልባት «ጌታ» ብሎ በአክብሮት ብቻ መጥራቱ ሳይሆን አይቀርም። 

2.2 ጌታ ኢየሱስ የዓለም ገዥና፥ የፍጥረታት ሁሉ ፈራጅ (ዳኛ) ነው። 

ነገር ግን ኢየሱስ ከሙታን ከተነሣ በኋላ፥ ደቀ መዛሙርቱ እርሱ ከሰብአዊ ጌታ በላይ መሆኑ ገብቶአቸው ነበር። በተቀሩት የአዲስ ኪዳን ክፍሎች ውስጥ ያለው ትምህርት ግልጽ እንደሚያደርገው፥ ሐዋርያት ኢየሱስን «ጌታ» ብለው ሲጠሩት፥ ለማለት የፈለጉት እርሱ የሰዎች ሁሉ የበላይ ገዥና አንድ ቀን በፍጥረታት ላይ የሚፈርድ ያህዌ እግዚአብሔር መሆኑን ነበር። 

ጥያቄ፡- የሐዋርያት ሥራ 2፡34-36 አንብቡ። ሀ) በሐዋ. ሥራ 2፡34-35 ውስጥ ጴጥሮስ የትኛውን ቁጥር ጠቀሰ? ለ) ጴጥሮስ ሊናገር፥ ከትንሣኤና ከመንፈስ ቅዱስ መውረድ የተነሣ ለእስራኤል ምን ይረጋገጥለታል አለ? 

እንደምታስታውሱት በትምህርት ስድስት ላይ መዝሙር 119ን በጥንቃቄ አጥንተን ነበር። በዚያ ክፍል የሚመጣው መሢሕ ታላቅ ኃይልና ሥልጣን እንደሚኖረው ገልቱ የሚናገር ትንቢት መሆኑን ተመልክተናል። የአዲስ ኪዳን ጸሐፊዎች ኢየሱስ እንደ እግዚአብሔር መሢሕ ኃይልና ሥልጣን ያለው መሆኑን ለመግለጽ መዝሙር 110ን ብዙ ጊዜ ይጠቅሱታል። አንዱም ምሳሌ፥ በሐዋ. 2፡34-36 የሰፈረው ነው። ሐዋርያው ጴጥሮስ በጴንጤቆስጤ ቀን ባደረገው ንግግር ማጠቃለያ ላይ መዝሙር 10ን በመጥቀስ ሊናገር፥ የኢየሱስ ትንሣኤና የመንፈስ ቅዱስ መውረድ፥ እርሱ ተስፋ የተሰጠበት መሢሕና ጌታ መሆኑን እንደሚያረጋግጥ ገልጾአል። በትምህርት ስድስት ውስጥ በንጉሥ ቀኝ እንዲቀመጥ የሚፈቀድለት ሰው፥ እርሱ ራሱ እንደ ንጉሥ ኃይልና ሥልጣን ሁሉ እንዳለው ተመልክተናል። ስለሆነም፥ የኢየሱስ ከሙታን መነሣትና መንፈስ ቅዱስን መላክ፥ እርሱ ከዚህ ጊዜ ጀምሮ ሙሉ ኃይልና ሥልጣን ተቀዳጅቶ በመዝሙር 110 ላይ በተሰጠው ተስፋ መሠረት ከሁሉ በላይ የሆነ ጌታ ሆኖ እየገዛ መሆኑን እንደሚያረጋግጥ ተከታትለናል። 

ጥያቄ ፊልጵስዩስ 2፡9-11 አንብቡ። ሀ) እግዚአብሔር ኢየሱስን ወደ ምን ስፍራ ከፍ ከፍ አደረገው? ለ) እግዚአብሔር ለኢየሱስ ምንን ሰጠ? ሐ) በኢየሱስ ፊትስ ማን ይሰገዳል? መ) መላስ ሁሉ ምንን ይመሰክራል? 

ፊልጵስዩስ 2፡6-11 ጳውሎስ ስለ ኢየሱስ ተሠገዎና ከዚያም በኋላ ከፍ ከፍ ስለ ማለቱ የገለጸበት ክፍል ነው። በሦስተኛው ሳምንት ክፍለ ትምህርት ላይ ከቁጥር 6=8፥ ስለ ኢየሱስ ተሠገራና ራሱንም ዝቅ ስለ ማድረጉ የተጻፈውን በጥንቃቄ አጥንተናል። ኢየሱስ ራሱን ዝቅ አድርጎ ስለ ኃጢአት ለመሞት የተሰጠ ሰው ከመሆኑ የተነሣ «እግዚአብሔር ከሁሉ በላይ ወዳለው የክብር ስፍራ ከፍ አደረገው፥ ከስምም ሁሉ የሚበልጥ ስም ሰጠው፡፡» እንዲህ ማለት እግዚአብሔር ኢየሱስን የፍጥረታት ሁሉ የበላይ ገዥ አደረገው ማለት ነው። ወደፊት ደግሞ ሰው ሁሉ በኢየሱስ ፊት በስግደት ራሱን ዝቅ አድርጎ እርሱ ገዢው መሆኑን ይገልጻል። ወደፊት ሰው ሁሉ ኢየሱስ ጌታው መሆኑን ይመሰክራል። በፊልጵስዩስ 2፡11 ላይ ሐዋርያው ጳውሎስ ኢየሱስን «ጌታ» ብሎ ሲጠራው፥ እርሱ የፍጥረታት ሁሉ፥ ከዚህ ቀደም የኖረው የእያንዳንዱ ሰውና ወደፊትም የሚኖረው ሰው ሁሉ ገዥና ጌታ ነው ማለቱ ነው። 

2.3 ጌታ ኢየሱስ ከእግዚአብሔር አብ ጋር እኩል ነው። 

ጥያቄ፡- 1ኛ ቆሮንቶስ 8:5-6 አንብቡ። ሀ) ክርስቲያኖች ስንት አምላኮች አሉዋቸው? ለ) ክርስቲያኖች ስንት ሴቶች አሉዋቸው? 

ሐዋርያው ጳውሎስ በ1ኛ ቆሮንቶስ 8 ውስጥ አንድ እግዚአብሔር እንዳለና ለጣዖታት ሁሉ የተሠዋ በፍጹም ለእግዚአብሔር የተሠዋ አለመሆኑን ያስተምራል፥ ምንም እንኳን የሚያምኑ ሰዎች ብዙ አማልክትና ብዙ ጌቶች እንዳሉ ቢያምኑም፥ እውነቱ ግን አንድ እግዚአብሔርና አንድ ጌታ ብቻ ነው ይላል። አንዱ ጌታም ኢየሱስ ክርስቶስ ሲሆን፥ ጳውሎስ እርሱን ከእግዚአብሔር አብ እኩል ያስቀምጠዋል። እርሱም፥ «ሁሉ ነገር በእርሱ የተፈጠረና እኛም በእርሱ የምንኖር ነን።» ይህ ማለትም ኢየሱስ የሕይወት ፈጣሪና ተንከባካቢ ነው ማለት ነው። ጳውሎስ በ1ኛ ቆሮንቶስ 8፡6 ውስጥ ኢየሱስን «አንድ ጌታ» ብሎ ሲጠራው፥ ኢየሱስ ከእግዚአብሔር አብ ጋር እኩል አድርጎ ይመለከተዋል። 

2.4 ከፍርድ የሚያድነን ጌታ ኢየሱስ ብቻ ነው። 

ጥያቄ፡- ሮሜ 10፡9-13 አንብቡ። ሀ) እንደ ቁጥር 9-10 ሰው ለመዳን ምን ማድረግ፥ ደግሞስ ምንን ማመን አለበት? ለ) እንደ ቁጥር 11 ሰዎች በኀፍረት ላይ እንደማይወድቁ እንዴት እርግጠኞች ሊሆኑ ይችላሉ? ሐ) እንደ ቁጥር 12 ኢየሱስ የማን ጌታ ነው? 

ጥያቄ፡- ኢዩኤል 2፡30-2 አንብቡ። ሀ) እንደ ቁጥር 30-31 የጌታ ቀን ምን ይወመስላል? ለ) እንደ ቁጥር 32 በዚህ ቀን ግን ይድናል? ሐ) ሐዋርያው ጳውሎስ በሮሜ 10፡13 ውስጥ፥ ኢዩኤል 2፡32ን ይጠቅሳል። ሰኢዩኤል 22 በተጠቀሰው ዐውድ መሠረት ጳውሎስ «የጌታን ስም የሚጠራ ሁሉ ይድናል» ሲል ምን ማለቱ ይመስላችኋል? 

በኢዩኤል 2፡28-32 ነቢዩ ስለ መጨረሻው ቀን ይናገራል። በመጀመሪያ፥ በመጨረሻው ቀን ስለሚመጣው የመንፈስ ቅዱስ በረከት ይናገራል (ኢዩኤል 2፡28-29)። ይህ እንግዲህ ክርስቲያኖች የተቀበሉትን በረከት የሚያመለክት ነው። ነቢዩ በሁለተኛ ደረጃ ፥ እግዚአብሔር ወደፊት በዓለም ላይ የሚፈርድ መሆኑን ይናገራል። ይህ ጊዜ ፀሐይ የምትጨልምበት ጨረቃም እንደ ደም የምትቀላበት በጣም አስፈሪ ጊዜ ይሆናል። በዚህ አስፈሪ የፍርድ ጊዜ፥ የእግዚአብሔርን ስም የሚጠሩት ብቻ ይድናሉ። በእግዚአብሔር ብቻ የሚያምኑትና እግዚአብሔር ብቻ እንደሚያድናቸው የሚተማመኑ ብቻ ከሚመጣው ከእግዚአብሔር ፍርድ ይድናሉ። 

በኢዩኤል 2 ውስጥ ከተገለጸው ፍርድ ለመዳን እያንዳንዱ ሰው የሚፈጽመው ኃላፊነት እንዳለበት ጳውሎስ በሮሜ 10 ውስጥ ያብራራል። ይህ ኃላፊነትም «ኢየሱስ ጌታ መሆኑን መመስከርና እግዚአብሔር ከሞት እንዳስነሣው ማመን ነው?» በዚህ ሁኔታ ኢየሱስ ጌታ መሆኑን የሚያምኑ ሁሉ፥ እግዚአብሔር በሚፈርድባቸው ቀን እንደማያፍሩና ደግሞም እንደማይኮነኑ እርግጠኞች ሊሆኑ ይችላሉ። ኢየሱስ የአይሁድና የአሕዛብ፥ የሁለቱም ጌታ ስለሆነ ሁለቱም የእግዚአብሔርን ደኅንነት ስለማግኘታቸው እርግጠኞች ሊሆኑ የሚችሉት፥ እርሱ ጌታቸው መሆኑን አምነው ሊቀበሉ ብቻ ነው። ከዚያም ጳውሎስ ለማጠቃለል ኢዩኤል 2፡32ን በመጥቀለ እንዲህ ይላል፥ «የጌታን ስም የሚጠራ ሁሉ ይድናል»። ስለሆነም በኢዩኤል 2 ውስጥ ሊመጣ ካለው ፍርድ ለመዳን የብሔር ልዩነት ሳይኖር ሁሉም ሰው የጌታን ስም መጥራት አለበት። ኢየሱስ ጌታ መሆኑንም መመስከር አለባቸው። 

ነገር ግን ኢየሱስ ጌታ ነው ብሎ መመስከር ሊባል ምን ማለት ነው? ደግሞም የጌታን ስም መጥራት ሲባልስ? ጳውሎስ ስለ ኢየሱስ የተናገረው፥ በኢዩኤል ምዕራፍ 2 እንደተጠቀሰው እንደ እውነተኛው አንድ አምላክ ያህዌ ኢየሱስም የፍርድና የደኅንነት ጌታ መሆኑን ነው። «የጌታን ስም መጥራት» ማለት ኢየሱስ ያህዌ መሆኑንና በሰዎች ሁሉ ላይ ሊፈርድ የሚመጣና ሰዎችንም ሁሉ የማዳን ሥልጣን ያለው እርሱ ብቻ መሆኑን አምኖ በይፋ መመስከር ነው። ስለሆነም ሰዎች ሊድኑ የሚችሉት ኢየሱስ ፈራጅና አዳኝ መሆኑን ሊያምኑ ብቻ ነው። ሰዎች ሁሉ እይሁድም ሆኑ አሕዛብ የእግዚአብሔርን የተትረፈረፈ የደኅንነት በረከትን ሊያገኙ የሚችሉት እግዚአብሔር በራሱ መንገድ አማካኝነት እንዲያድናቸው ስሙን በመጥራት ነው። 

«ኢየሱስ ጌታ ነው» ማለት እርሱ ጌታችን ነው እንታዘዘዋለን ከማለት የበለጠ ነው። ስለዚህ፥ «ኢየሱስ ጌታ ነው» ማለት እርሱ መለኮታዊ ፈራጃችንና መለኮታዊ አዳኛችን ስለሆነ እንደ አንድ እውነተኛ አምላክ አድርገን በእርሱ እናምናለን ማለት ነው። «ኢየሱስ ጌታ ነው» ማለት እርሱ ብቻ ሊያድነን የሚችል መሆኑን ማመን ማለት ነው። በዚህ አነጋገር ኢየሱስን ጌታ ማድረግ ማለት ጳውሎስ እንደተናገረው፥ ለእኛ ለክርስቲያኖች ማንነታችንን የምናስመሰክርበትና መለያችን የሆነ ምልክታችን ነው። 57ኛ ጥያቄ፡- 1ኛ ቆሮንቶስ 2፡3 አንብቡ። «ኢየሱስ ጌታ ነው» የሚለው አነጋገር ምንን ያመለክታል? 

ጳውሎስ በ1ኛ ቆሮንቶስ 12፡3 ውስጥ የክርስቲያን አንዱ መታወቂያ፥ «ኢየሱስ ጌታ ነው» ብሎ መመስከር ነው ይላል። እንዲህ ማለትም አንድ ሰው በአፉ ብቻ ይህን ቃል ያነበንባል ማለት አይደለም። እንዲህ ማለት ኢየሱስ አንድ ቀን በፍጥረታት ሁሉ ላይ እንደሚፈርድ ማመን ማለት ነው። እንዲህ ማለትም አንድ ሰው ኢየሱስ ከሚመጣው ፍርድ እንደሚያድነው አምኖ እንደ ግል መድኃኒቱ ይቀበለዋል ማለት ነው። ማንም ይህንን የመሰለ የምስክርነት ቃል የሚሰጥ መንፈስ ቅዱስም በውስጡ ይኖራል። እርሱም እውነተኛ በክርስቶስ አማኝ ለመሆኑ ምልክት ይታይበታል። 

የጥንት ክርስቲያኖች ኢየሱስ ጌታ ነው በሚሉበት ጊዜ፥ ስለ ብዙ ነገር መናገራቸው ነበር። ትንሣኤው እርሱ በእግዚአብሔር የተመረጠ መሢሕ መሆኑን ያረጋግጣል ማለታቸው ነበር። እንዲሁም በእግዚአብሔር የተመረጠ መሢሕ እንደ መሆኑ፥ እርሱ ከሁሉ በላይ የሆነ የፍጥረታት ሁሉ ገዥ ነው ማለታቸው ነበር። እርሱ የፍጥረታት ሁሉ ጌታ ብቻ ሳይሆን የግላቸውም ጌታ ነው። ይታዘዙታል፥ ትእዛዙንም ሁሉ ይፈጽማሉ። መንግሥታቸውንና ምድራዊ ሥልጣንን ቢያከብሩ እንኳ (1ኛ ጴጥሮስ 2፡13-17፥ የመጨረሻውና ከሁሉ በላይ የሆነ ጌታቸው ኢየሱስ ክርስቶስ መሆኑን ያስታውሳሉ። ነገር ግን፥ «ኢየሱስ ጌታ ነው» በሚሉበት ጊዜ ኢየሱስ የበላይ ነው ከማለት ያለፈ ነው። ይህን በሚሉበት ጊዜ ኢየሱስ ከእግዚአብሔር አብ ጋር እኩል 

መሆኑን ይመሰክራሉ። እርሱ ራሱ ያህዌ ስለሆነ አንድ ቀን በሰዎች ሁሉ ላይ ይፈርዳል። ስለሆነም ወደ ደኅንነት ለመድረስ ያለው ብቸኛው መንገድ በእርሱ ማመን ነው። 

3. ኢየሱስ የሕይወታችን ጌታ የመሆኑ አስፈላጊነት 

ጥያቄ፡- ሀ) ኢየሱስ ጌታ ነው! እንዲህ ማለት እርሱን ስለ መታዘዛችሁ ምን ያመላክታል? ለ) ኢየሱስ ጌታ ነው! እንዲህ ማለት ለሌሎች ስለምትሰጡት ምስክርነት ምን ያመለክታል? 

ብዙ ክርስቲያኖች፥ በአፋቸው «ኢየሱስ ጌታ ነው» ለማለት ይፈጥናሉ። ነገር ግን በሕይወታቸው አይገልጹትም። «ኢየሱስ ጌታ ነው» ማለት አስቸጋሪ በሆነበት ጊዜ እንኳን ለእርሱ እንታዘዛለን ማለት ነው። እርሱ ፍጹም የሆነ ጌታችን በመሆኑ፥ ምን ጊዜም ፈቃዱን ለመፈጸም እንሻለን ማለት ነው። ኢየሱስ በሕይወታችን ላይ ፍጹም ሥልጣንና ቁጥጥር አለው ማለት ነው። ነገር ግን «ኢየሱስ ጌታ ነው» ስንል እኛ ለሌሎች ያለንን ምስክርነትም ይመለከታል። ኢየሱስን እንደ ጌታቸው አድርገው የማይመለከቱ ሰዎች በሚያጋጥሙን ጊዜ፥ ኢየሱስ አንድ ቀን በፍጥረታት ሁሉ ላይ እንደሚፈርድ ልናስታውሳቸው ይገባል። አንድ ቀን ኢየሱስ በእነርሱም ላይ ይፈርዳል። እና ከሚመጣው የፍርድ ቀን መዳን የምንችለው፥ ዛሬ ኢየሱስ ያህዌ እግዚአብሔር መሆኑን በመመስከርና እንደ ግል መድኃኒታችን አድርገን እርሱን በመቀበል ብቻ ነው። 

ጥያቄ፡- ሀ) በሕይወታችሁ ውስጥ ኢየሱስን እንደ ጌታችሁ አድርጋችሁ ያላሰባችሁበትን ጊዜ፥ ነገር ግን በዚህ ሳምንት ውስጥ የምትታዘዙበትን ሁኔታ ጻፉ። ለ) ኢየሱስ የሚመጣው ጌታና ፈራጅ መሆኑን ለመመስከር የሚፈልጉና እርሱን እንደ ግል መድኃኒታቸው አድርገው በማመን የሚቀበሉ ሰዎችን ስም ጻፉ። ሐ) የኢየሱስ ጌትነት፥ በቤተ ክርስቲያኖቻችሁ በአካባቢአችሁ ኅብረተሰብና አስተዳደር ላይ ማሳደር ስለሚገባው አዎንታዊ ተጽዕኖ አንዱን አቅጣጫ በመጥቀስ ጻፉ። 

ምንጭ፡- “አስተምህሮ ክርስቶስና ደኅንነት”፤ ጽሑፍ፣ በዶ/ር ስቲቭ ስራውስ፤ ትርጉም በኃይሉ ልመንህ

Exit mobile version