የዮሐንስ ወንጌል የጥናት መምሪያና ማብራሪያ
ምልከታ
በማግስቱ ወደ በዓሉ የመጣው ብዙ ሕዝብ ኢየሱስ ወደ ኢየሩሳሌም እንደሚመጣ በሰሙ ጊዜ የዘንባባ ዝንጣፊ ይዘው ሊቀበሉት ወጡ። “ሆሣዕና በጌታ ስም የሚመጣ የእስራኤል ንጉሥ የተባረከ ነው” እያሉም በታላቅ ድምፅ ጮኹ። ኢየሱስም ትንቢቱ ይፈጸም ዘንድ በአህያ ውርንጭላ ላይ ተቀምጦ ገባ። መጀመሪያ ላይ ደቀ መዛሙርቱ ይህን ባይረዱትም ጌታ ከከበረ በኋላ ግን ይህ ስለ እርሱ የተጻፈ መሆኑንና እነርሱም እንዳደረጉለት አሰቡ። በዚያም መካከል ወደ በዓሉ ለስግደት መጥተው የነበሩ አንዳንዴ ግሪካውያን ፊልጶስን “ጌታ ሆይ ኢየሱስን ልናይ እንወዳለን” ብለው ለመኑት። ኢየሱስም የሰው ልጅ ይከብር ዘንድ ሰዓቱ ደርሷል በማለት መለሰላቸው። የስንዴ ቅንጣት በምድር ወድቃ ካልሞተች ብቻዋን ትቀራለች፤ ብትሞት ግን ብዙ ፍሬ ታፈራለች በማለት ስለ ሞቱና ስለሚገኘው ፍሬ አስተማረ። ነፍሱን የሚወድ ያጠፋታል፤ ነፍሱንም በዚህ ዓለም የሚጠላ ለዘላለም ሕይወት ይጠብቃታል በማለት እውነተኛ ደቀ መዝሙርነትን ገለጠ።
ትርጓሜ
የሕዝቡ የዘንባባ ዝንጣፊ መያዝና “ሆሣዕና” ማለታቸው ኢየሱስን እንደ መሲሐዊ ንጉሥ መቀበላቸውን ያሳያል። ሆኖም እርሱ በአህያ ላይ መቀመጡ ምድራዊና በጦርነት የሚያሸንፍ ንጉሥ ሳይሆን የሰላምና የትሕትና ንጉሥ መሆኑን ያመለክታል። ግሪካውያን እርሱን ለመፈለግ መምጣታቸው ወንጌል ከአይሁድ አልፎ ለዓለም ሁሉ እንደሚሆን ምልክት ነው። ኢየሱስ ስለ ስንዴ ቅንጣት የተናገረው ምሳሌ የእርሱን የመስቀል ሞት አስፈላጊነት የሚያስረዳ ነው። እርሱ በመስቀል ላይ ካልሞተ የሰው ልጅ ድኅነት ሊገኝ እንደማይችልና መንፈሳዊ ፍሬ ሊፈራ እንደማይችል ገልጿል። እውነተኛ ደቀ መዝሙርነትም ራስን ከመውደድና ከዓለማዊ ምቾት ወጥቶ ለጌታ በመኖርና በመከተል የሚገኝ መሆኑን ያስተምረናል። ክብር የሚገኘው በትሕትናና በመሥዋዕትነት መንገድ እንደሆነ ጌታ በተግባር አሳይቶናል።
💬 ለአነስተኛ ቡድን ውይይት የሚሆኑ ጥያቄዎች
👉 ጌታ ኢየሱስን በሕይወትህ ንጉሥ አድርገህ ስትቀበለው እንደ አይሁድ ለምድራዊ ጥቅም ነው ወይስ ለዘላለም ድኅነት?
👉 እንደ ግሪካውያኑ “ኢየሱስን ልናይ እንወዳለን” የሚል ጥልቅ ናፍቆትና ፍለጋ በዕለት ተዕለት ሕይወትህ አለ?
👉 በሕይወትህ ፍሬ ለማፍራት እንደ ስንዴ ቅንጣት የገዛ ራስህን ፍላጎትና ስሜት ለጌታ ፈቃድ አሳልፈህ የመስጠት ዝግጁነት አለህ?
👉 ነፍስን መውደድ ማለት ለዚህ ዓለም ጊዜያዊ ደስታ መኖር እንደሆነና ይህ ደግሞ ኪሳራ እንደሆነ ስታስብ ምን ይሰማሃል?
👉 ጌታን መከተል ማለት እርሱ በሄደበት የትሕትናና የመሥዋዕትነት መንገድ መጓዝ መሆኑን በተግባር እንዴት ትገልጸዋለህ?
👉 ጌታን በሚያገለግልበት ስፍራ አብ እንደሚያከብረው የገባው ቃል በአገልግሎትህ እንድትበረታ ያደርግሃል?
👉 በሕይወትህ የሚገጥሙህ ፈተናዎችና “ሞቶች” ለበለጠ መንፈሳዊ ፍሬ መሆኑን አምነህ የመቀበል ትዕግሥት አለህ?
