የሮም ግዛተ ዐፄና የሄሮድስ አገዛዝ

ኢየሱስ በጳለስቲና በተወለደበት ወቅት በተለያዩ ቡድኖች መካከል ፖለቲካዊ ትግልና ሽኩቻ ነበር። ለሥልጣን ሲባል በቤተ ሰብ አባላት መካከል እንኳ እርስ በርስ መገዳደል ይፈጸም ነበር። ይህ ሁሉ ትግል በተራው ኅብረተሰቡ ላይ የሚያስከትለው የኑሮ ጫና ቀላል አልነበረም። የተለያዩ ቡድኖች በሥልጣን ላይ ካሉትና ከሮማውያን ጋር ለሚያካሂዱት ትግል የተራውን ሕዝብ ድጋፍ ይፈልጉ ነበር። ግብር እየጨመረ ሲሄድ፥ የኑሮ ውድነቱም እንደዚያው ይከፋ ጀመር። ሰላምና መረጋጋት ታጣ። ከአሕዛብም አገዛዝ ነፃ ለመውጣት አልተቻለም።

የውይይት ጥያቄ፡- ክርስቶስ የኖረበት ዘመን ከእኛ ዘመን ጋር የሚመሳሰለው ወይም የሚለያየው እንዴት ነው?

«ንጉሣችን የታለ? ነፃ አውጪያችን የት አለ? መሢሑስ?» የሚሉ ጥያቄዎች ለ400 ዓመታት ያህል ሲነሡ ቆይተዋል። አይሁዶች በመቃብያን አማካኝነት ለአጭር ጊዜ ነጻነታቸውን ካገኙና መልሰውም ከተነጠቁ በኋላ፥ ከፍተኛ የነጻነት ጥማት አደረባቸው። በኢየሩሳሌም ከተማ የተለያዩ ቡድኖችና መሪዎች የሚያካሂዷቸው ትግሎች፥ እንዲሁም በአገሪቱ ውስጥ የፍትሕና ቅድስና አለመኖር የሕዝቡን ሕይወት ለምሬት ዳረገው።

እርስ በርሳቸው፥ «እግዚኣብሔር ተስፋ የሰጠን የሰላምና የጽድቅ አገዛዝ የታለ?» እያሉ ይጠያየቁ ነበር። ሕዝቡ ለዚህ ጥያቄ መልስ ለማግኘት የሚፈልጉት ከፖለቲካዊ መሢሕ ነበር። ነገር ግን የነገሥታት ንጉሥ በመካከላቸው ተገኝቶ የውስጥ ሰላምና ጽድቅ ያለበትን መንፈሳዊ መንግሥት በሰበከላቸው ጊዜ ሊቀበሉ አልፈለጉም። ሕዝቡ የሚፈልጉትን ፖለቲካዊ መልስ ሊሰጣቸው ስላልቻለ መሢሑን አንቀበልህም አሉት።

የውይይት ጥያቄ፡- እግዚአብሔር ብዙውን ጊዜ የምንጠብቃቸውን መልሶች ባለመስጠቱ ምክንያት ለችግሮቻችን የሚያቀርባቸውን መፍትሔዎች የምንቀበለው እንዴት ነው?

የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) ማቴ. 2፡7-18 አንብብ። ስለ ሄሮድስ ባሕርይ የቀረበው ገለጻ ምንድን ነው? ) ከመጽሐፍ ቅዱስ መዝገበ ቃላት ስለ ሄሮድስ እንብብና ስለ ሕይወቱና አገዛዙ አጭር ነገር ጻፍ።

ታላቁ ሄሮድስ (37-4 ዓ.ዓ.)

ምንም እንኳ መጽሐፍ ቅዱስ ሄሮድስ ክፉ ሰው እንደነበረ ቢገልጽም፥ የዓለም ታሪክ ከይሁዳ ታላላቅ መሪዎች እንደ አንዱ ይዘክረዋል። ሄሮድስ በአንድ ወቅት ንጉሥ ዳዊትና ሰሎሞን የያዙትን የጳለስቲና ግዛት በቁጥጥሩ ሥር ለማድረግ የቻለ ንጉሥ ነበር። ሄሮድስ በአገሪቱ ሁሉ አምባዎችን የገነባ ታላቅ ወታደራዊ መሪ ነበር። ይህ ሰው ራሱን ችሎ እንደሚገዛ ንጉሥ ይሁዳን እያስተዳደረ ከሮም ጋር ሰላማዊ ግንኙነቶችን ለመመሥረት የቻለ ብልህ ፖለቲካዊ መሪ ነበር፡፡ ሄሮድስ በይሁዳ ብቻ ሳይሆን፥ በሌሎች የዓለም ክፍሎችም በገነባቸው ሕንፃዎች፥ በጥንቱ ዓለም ውስጥ የታወቀ ሰው ነው። ከታላላቅ ሥራዎቹ መካከል አሻሽሎ ያሠራው የኢየሩሳሌም ቤተ መቅደስ ኣንዱ ነው። በ19 ዓ.ዓ የተጀመረው ይህ ሥራ እስከ 63 ዓ.ም ድረስ ሙሉ በሙሉ አልተጠናቀቀም ነበር። የኢየሩሳሌሙ ቤተ መቅደስ በጥንቱ ዘመን ከሚገኙ ሕንፃዎች መካከል እጅግ ውብ ሕንፃ ነበር። ስለሆነም ሕዝቡ፥ ንጉሥ ሄሮድስን እንደ ታላቅ መሪ ይመለከቱት ነበር።

ይህም ሆኖ፥ አይሁዶች ስለ ሄሮድስ ፍጹም የተለየ አመለካከት ነበራቸው። አንደኛው፥ ሄሮድስ ንጹሕ አይሁዳዊ ሳይሆን፥ ከፊል ኢዱሚያዊ (የአይሁዶች የረዥም ጊዜ ጠላት ከነበሩት ኤዶማውያን ትውልድ) እና ከፊል አይሁዳዊ መሆኑ ነበር። ስለሆነም፥ በጳለስቲና የሚኖሩ አይሁዶች ሙሉ በሙሉ አልተቀበሉትም ነበር። ሁለተኛው፥ ከዳዊትም ሆነ ከሃስሞኒያን የዘር ሐረግ ባለመምጣቱ፥ ሕጋዊ ገዥ ነው ብለው አያምኑም ነበር። እንዲያውም ሄሮድስ በሥልጣን ወንበር ላይ የተቀመጠው የሃስሞኒያኖችን ዘሮች በመጨረሱ ነበር። ሦስተኛው፥ የሮማውያን ወዳጅ ነበር። አይሁዶች ሙሉ ነጻነታቸውን ይፈልጉ ስለ ነበር፥ በአገራቸው ላይ የሚደርሰውን የአሕዛብ ተጽዕኖ አጥብቀው ይጠሉ ነበር። ምንም እንኳ ሄሮድስ የአይሁድ ሃይማኖት ተከታይ ቢሆንም፥ ሮማውያንን ይደግፍና ለፖለቲካው አስፈላጊ በሚሆንበት ጊዜ የአሕዛብ ጣዖትን ለማምለክ ፈቃደኛ ነበር።

ከፍተኛ የአስተዳደር ችሎታ ቢኖረውም፥ ሄሮድስ አንድ ሰው እርሱን ገድሎ ዙፋኑን እንዳይወስድበት ይሰጋ ነበር። ምክንያቱም በሃስሞኒያኖች ታሪክ ብዙውን ጊዜ ወንድም ወንድሙን ገልብጦና ገድሎ ስፍራውን ይወስድ ነበር። ሄሮድስ ይህ አደጋ በእርሱ ላይ እንዳይደርስ ፈራ። አጥብቆ ይፈራ የነበረው ደግሞ ቤተሰቡን ነበር። ስለሆነም ያሤሩብኛል ብሎ በመፍራቱ አጎቱን፥ ሚስቱንና ብዙ ልጆቹን አስገድሏል።

የክርስቶስ ታሪክ የሚጀምረው ከሄሮድስ የአገዛዝ ዘመን ነው። ክርስቶስ ወደ ምድር በመጣበት የመጀመሪያ ዓመት፥ ሄሮድስ ንጉሥ ነበር። እውነተኛ የአይሁድ ንጉሥ በቤተልሔም እንደተወለደ ሲነገር የሰጠው ምላሽ ሄሮድስ አንድ ሰው እርሱን ገድሎ ፖለቲካዊ ሥልጣኑን እንዳይወስድሰት መስጋቱን ያሳያል። ሄሮድስ ክርስቶስ መሢሕ ነው ብሎ ባያምንም፥ ማንም ሰው የኢየሩሳሌሙን ዙፋን እንዳይቀናቀንበት ፈራ።

ሰብአ ሰገል ከኢየሩሳሌም ወጣ ብላ በምትገኘው አነስተኛ የቤተልሔም ከተማ የአይሁድ ንጉሥ እንደ ተወለደ በነገሩት ጊዜ፥ ንጉሥ ሄሮድስ በከተማይቱ ውስጥ በቅርብ ጊዜ የተወለዱትን ወንድ ልጆች በሙሉ አስገደለ። እግዚአብሔር ግን ሄሮድስ ሕፃኑን ክርስቶስን እንዳያገኘው ከዮሴፍና ከማርያም ጋር ወደ ግብፅ አገር ላከው። ሄሮድስ ከ30 ዓመት በላይ ከገዛ በኋላ ክርስቶስ እንደ ተወለደ ብዙም ሳይቆይ ሞተ።

ይህም ክርስቶስ ከ6-4 ባለው ዓ.ዓ መካከል እንደተወለደ ይጠቁማል። ምሁራን ክርስቶስ የተወለደበትን ትክክለኛ ዓመት ባያውቁም፥ ሄሮድስ በሞተበት ከ4 ዓ.ዓ. በፊት መሆኑ ይገመታል። የዓለም የቀን መቁጠሪያ በሁለት ዐበይት የዘመናት ቀመር ተከፍሏል። አንደኛው ከክርስቶስ ልደት በፊት የነበረው ዘመን ሲሆን ዓ.ዓ. (ዓመተ ዓለም) ሲባል፥ ሁለተኛው ከክርስቶስ ልደት በኋላ ያለው ዘመን ዓ.ም. (ዓመተ ምሕረት) ተብሎ ይታወቃል። ዓመተ ምሕረት ክርስቶስ ለተወለደበት የዘመን ቀመር የተሰጠ መጠሪያ ነው። ይህ ዘመናዊ የቀን መቁጠሪያ በክርስቶስ መምጣት ምክንያት በዓለም ታሪክ ዘንድ ፍጹም ኣዲስ ምዕራፍ እንደ ተጀመረ የሚያበሥርና የክርስቲያኖችን እምነት የሚያንጸባርቅ ነው።

እንግዲህ በቀን መቁጠሪያችንና በትክክል በተፈጸመው ነገር መካከል ልዩነት የሚታየው ለምንድን ነው? በኢትዮጵያና በአውሮፓ የቀን መቁጠሪያ መካከል ልዩነት የሚታየው ለምንድ ነው? ምንም እንኳ ምክንያቶቹን በሙሉ ባናውቅም፥ የቤተ ክርስቲያን ታሪክ የሚሰጠን መልስ አለ። ይህም ከክርስቶስ ሞት በኋላ ለ500 ዓመታት ያህል እያንዳንዱ አገር የየራሱ የቀን መቁጠሪያ ነበረው። አይሁዶች ዓለም የተፈጠረችበት ዘመን እንደሆነ ከሚያምኑበት ጊዜ የሚነሣ የቀን መቁጠሪያ ነበራቸው። የሮማውያን የቀን መቁጠሪያ ደግሞ የሮም ከተማ ከተመሠረተችበት ጊዜ የሚጀምር ነበር። ግሪኮች፥ ቻይናውያንና ሌሎችም አገሮች ከተለያዩ አጋጣሚዎች የሚነሡ የቀን መቁጠሪያዎች ነበሯቸው።

በመካከለኛው ዘመን ግን ክርስትና እየተስፋፋና ታላቅ እምነት እየሆነ ሲሄድ፥ ከክርስቶስ ልደት የሚጀምር የቀን መቁጠሪያ መጠቀሙ አስፈላጊ ሆኖ ተገኘ። ይህ ሲሆን፥ ብዙ ዘመን አልፎ ነበር። በ525 ዓ.ም አንድ ካህን ኢየሱስ የተወለደበትን ዘመን ለመወሰን ፈልጎ ታሪክን መከለስ ጀመረ። ስለሆነም ከክርስቶስ ልደት በፊት የነበሩትን ዓመታት “ክርስቶስ በፊት”፥ ከዚያ በኋላ ያሉትን ደግሞ “የምሕረት ዘመን” ብለው ለመጥራት ወሰኑ። አብዛኞቹ ምሑራን ክርስቶስ ከ4-6 ዓ.ዓ ባለው ጊዜ እንደተወለደ ያምናሉ።

በምዕራባውያንና በኢትዮጵያ የቀን መቁጠሪያ መካከል የ7(8) ዓመት ልዩነት የሚታየውስ ለምንድን ነው? ለዚህ ምክንያቱን መናገር አስቸጋሪ ቢሆንም፥ ሁለት አማራጭ መልሶች አሉ። አንደኛው፥ የኢትዮጵያ የቀን መቁጠሪያ የፀሐይን ሳይሆን የጨረቃን ዑደት ይከተል እንደ ነበር የሚያመለክቱ ጽሑፎች በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ አሉ። የጨረቃ ዑደት ከፀሐይ ስለሚያጥር፥ ይህን የጊዜ ለውጥ ሊያስከትል ይችላል። ሁለተኛው፥ ከጁሊያን ወደ ግሪጎሪያን የቀን መቁጠሪያ በተደረገው ለውጥ የተከሰተ ለውጥ አለ። ከ46 እስከ 1582 ዓ.ም. ድረስ በሮም ግዛት ውስጥ የሚኖሩ «የጁሊያን ቀን መቁጠሪያ» በመባል የሚታወቀውን የጊዜ መቁጠሪያ ይከተሉ ነበር። ይህ የቀን መቁጠሪያ የፀሐይን ዑደት የሚከተልና አንድን ዓመት ለ365 1/4ኛ ቀናት የሚከፍል ነበር። ይህም በየአራት ዓመቱ 366 ቀናት እንደሚኖሩ ያመለክት ነበር። ዛሬ በኢትዮጵያ ውስጥ የምንከተለው የቀን መቁጠሪያ ይሄ ነው።

ነገር ግን ጳጳስ ግሪጎሪ በ82 ዓ.ም አብዛኞቹ የክርስቲያኖች በዓላት በትክክለኛው ቀን አይከበሩም በማለት የተሰማቸውን ኀዘን አስታወቁ። የፀሐይ ዓመት ከጁሊያን ዓመት 11 ደቂቃ ከ14 ሰኮንዶች ስለሚረዝም፥ ቀስ በቀስ የጁሊያን ቀን መቁጠሪያ ወደኋላ በመቅረት ላይ ነበር። ስለሆነም ከቀን መቁጠሪያው ላይ 10 ቀናትን አነሡ። በ1752 ዓ.ም ደግሞ ተጨማሪ ማሻሻያ ተደርጎ በምዕራቡ ዓለም የቀን መቁጠሪያ ላይ 11 ቀናት ተጨመሩ።

ከግሪክ ኦርቶዶክስ ጋር የሚዛመዱ እንደ ኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ያሉ አብያተ ክርስቲያናት በጁሊያን የቀን መቁጠሪያ ላይ ምንም ማስተካከያ ሳያደርጉ በመገልገል ላይ ይገኛሉ።

እንግዲህ የክርስቶስን የልደት ዘመን በመገመቱ ረገድ ትክክለኛው ማን ነው? ምሑራን ሁለቱም የቀን መቁጠሪያዎች ትክክል እንዳልሆኑ ያስባሉ። የምራባውያኑ የቀን መቁጠሪያ አራት ወይም አምስት ዓመቶችን እንደሚያጎድልና፥ የኢትዮጵያ የቀን መቁጠሪያ ደግሞ ሁለት ወይም ሦስት ዓመቶችን እንደሚያጎድል ይገምታሉ።

መጽሐፍ ቅዱስ ብዙውን ጊዜ የሄሮድስን ልጆች «ሄሮድስ» እያለ ስለሚጠራ ስለየትኛው ሄሮድስ እንደሚናገር በጥንቃቄ ማስተዋል ይኖርብናል። ከማቴዎስ ምዕራፍ 2 በስተቀር፥ በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ «ሄሮድስ» የሚለው ስም የመጀመሪያውን ንጉሥ ትውልዶች የሚያሳይ ነው።

ታላቁ ሄሮድስ ለ30 ዓመት ያህል የተረጋጋ መንግሥት ሲያስተዳድር ቆይቶ ሲሞት፥ ሮም ይሁዳን እስከ ተቆጣጠረችበት ጊዜ ድረስ አለመረጋጋት ሰፈነ። ሄሮድስ መንግሥቱን ለሦስት ቦታ ከፋፍሎ ለአርኬላዎስ፥ ለሄሮድስ አንቲጳስና ለሄሮድስ ፊልጶስ ሰጠ። ዋናው ግን ሮም መንግሥቱን ማን እንዲያስተዳድር የመወሰኗ ጉዳይ ነበር። ስለሆነም፥ የሄሮድስ መንግሥት ሕጋዊ ወራሾች ሆነው ለመሾም እያንዳንዳቸው የሄሮድስ ትውልዶች ወደ ሮም ተጓዙ። አይሁዶችም ይህን አጋጣሚ ተጠቅመው አርኬላዎስ በግዛታቸው እንዳይነግሥ የሮም ባለሥልጣናትን ጠየቁ። የሮም መንግሥት ግን አርኬላዎስ ይሁዳንና ሰማርያን፥ አንቲጳስ ገሊላንና ጳራያን፣ ፊልጶስ ደግሞ የገሊላን ባሕር ሰሜን – ምዕራባዊ አካባቢዎች እንዲያስተዳድሩ ወሰነ። የሮም መንግሥት ለማናቸውም የንግሥና ሥልጣን ሳይሰጥ እነዚህን አካባቢዎች እንዲያስተዳድሩ ሾማቸው። የሄሮድስ ዋንኛ ወራሽ የሆነው አርኬላዎስ ከሁለቱ የበለጠ ሹመት ነበር የተሰጠው። ሮማውያን ይህንን ያደረጉት ለአሠራራቸው የሚያመች ሰው ሆኖ ከተገኘ ንጉሥ አድርጎ ለመሰየምና ከዚህ በፊት አባቱ ይገዛው የነበረውን ግዛት ሁሉ ለመስጠት አስበው ነበር።

የአርኬላዎስ አገዛዝ (4 ዓ.ዓ. – 6 ዓ.ም) እና የሮም ገዥዎች (6-41ዓ.ም፥ 44-70 ዓ.ም)

በዚህ ጊዜ በኢየሩሳሌም ሰላም ጠፍቶ የማያቋርጥ ሁከትና ዐመፅ ነበር። ይህ ሁኔታ እየተባባሰ በመሄዱ ሮማውያን ከአንጾኪያ ወታደሮችን ለማስመጣት ተገደዱ። ለሌሎች ማስጠንቀቂያ እንዲሆን በማለት አንድ የሮም ጄኔራል 2000 አይሁዶችን በዋና ዋና መንገዶች ላይ አሰቅሏል።

በአርኬላዎስ ዘመን በይሁዳ ውስጥ የተረጋጋ ሁኔታ አልነበረም። ኣርኬላዎስ በነገሠባቸው ሦስት ዓመታት ውስጥ (ከ4ዓ.ዓ – 6ዓ.ም) ሕዝቡን ይቀሰቅሉብኛል በሚል ፍርሃት ሊቀ ካህናትን ሦስት ጊዜ ቀይሯል። ምንም እንኳ ኣርኬላዎስ የአባቱን የሕንጻ ፕሮጀክቶች ለመቀጠል ቢፈልግም፥ አይሁዶች አጥብቀው ስለ ጠሉት የሳምራውያንና የአይሁዳውያን መሪዎች ወደ ሮም አንድ መልእክተኛ ልከው በአገዛዙ ላይ የነበራቸውን ቅሬታ ገለጹ። ይህም አርኬላዎስ ከሥልጣን እንዲባረር አደረገ። በዚህ ጊዜ ሮማውያን የራሳቸውን ገዥዎች በይሁዳ ላይ ለመሾምና የይሁዳ ኣውራጃ ለማድረግ በመፈለጋቸው፥ ከብዙ መቶ ዓመታት በኋላ አሕዛብ በኢየሩሳሌም ላይ ነገሡ።

የይሁዲነት ማዕከል በሆነችው በይሁዳ ላይ የተካሄደው የሮማውያን አገዛዝ የኢየሩሳሌምን አቋም ለወጠው። ከዚያን ጊዜ አንሥቶ የኢየሩሳሌም ከፊል ነጻነትና ሉዓላዊነት አበቃ። ነገር ግን ኢየሩሳሌም የሮም አውራጃ በመሆኗ፥ ንጉሡ የራሱን አስተዳዳሪ ይሾምባት ጀመር። ሰላም ለማስጠበቅና ሕዝቡ ለሮም ሥልጣን እንዲገዙ ለማስገደድ ንጉሡ የሮምን አስተዳዳሪና ወታደሮች የግሪክ ከተማ በሆነችው ቂሣሪያ አሰፈረ። የሮም አስተዳዳሪ ብዙውን ጊዜ በአይሁዶች ጉዳይ በቀጥታ ጣልቃ አይገባም ነበር። የአይሁዶችን ጉዳይ በማስተዳደሩ በኩል ሊቀ ካህናቱን የአይሁድ ሸንጎ (የኣይሁድ ገዥ ጉባዔ) ዋንኛውን ተግባር እንዲያከናውን ያደርግ ነበር።

አይሁዶች ቀደም ሲል ይሰበስቡት የነበረውን ግብር እዚያው ይጠቀሙበት ነበር፤ አሁን ግን በቀጥታ ወደ ሮም እንዲልኩ ተደረገ። አይሁዶች ከሮም ግዛት ሥር መሆናቸውን የሚያመለክተውን ይህን ግልጽ ተግባር አጥብቀው ይጠሉት ነበር። የግብር አሰባሰቡን ለማገዝ የሚሾሙ ቀራጮች የይሁዲነት ጠላት ተደርገው ታሰቡ። ሮማውያን አይሁዶች ሊከፍሉ የሚገባቸውን የቀረጥ መጠን ለመወሰን የሕዝብ አስተያየት በሚሰበስቡበት ወቅት ይሁዳ በተባለ የገሊላ ሰው የተመራ ዐመፅ ተካሄደ (የሐዋ. 5፡7 አንብብ።) አንድ ታማኝ አይሁዳዊ ከእግዚአብሔር በተጨማሪ ለሮማውያን ቀረጥ መክፈል አለበት ወይስ የለበትም? የሚለው አከራካሪ ጉዳይ ሆነ፡፡ ብዙ አይሁዶች ለሮማውያን ቀረጥ ኣንከፍልም በማለት የአሕዛብን አገዛዝ መቃወማቸውን ገለጹ።

የውይይት ጥያቄ፡- ማቴ. 22፡15-21 ኣንብብ። ሀ) ግብር ስለ መክፈል የቀረበው ጥያቄ ክርስቶስን ለማጥመድ ያገለገለው እንዴት ነው? ለ) ክርስቶስ በጥበብ ባይመልስ ኖሮ ከአይሁዶች ወይም ከሮማውያን ዘንድ ምን ዐይነት ችግር ይገጥመው ነበር።

በተለይ በገሊላ ሮማውያን የአይሁዶችን ሉዓላዊነት መጋፋታቸውን በመቃወም የተጀመረው እንቅስቃሴ ለእናት ኣገራቸውና ለነጻነታቸው ቀናኢ የሆኑ አይሁዶች ቡድን እንዲመሠረት አደረገ። ይህ ቡድን ይበጀኛል በሚለው መንገድ ሁሉ የሮምን አገዛዝ ለማስወገድ ይጥር ነበር (ማቴ. 10፡4)።

ምናልባትም ይሁዳ ክርስቶስን አሳልፎ ከሰጠባቸው ምክንያቶች አንዱ፥ ክርስቶስ በሮማውያን ላይ አብዮት እንዲያካሂድ ለማስገደድ ሳይሆን አይቀርም። የዚህ ቡድን ተቃውሞ እየተካረረ በመሄዱ፥ በ66 ዓ.ም የትጥቅ ትግልን ኣስከትሏል። ይህም ሮማውያን የኢየሩሳሌምን ከተማና ቤተ መቅደስ በማፈራረስ የአይሁድን ሕዝብ እንዲደመስሱ አድርጓል።

ሮማውያን የይሁዳን ሕዝብ ለመቆጣጠር ከሚጠቀሙባቸው መንገዶች ውስጥ አንዱ ሊቀ ካህናትን መሾምና መሻር ነበር። ብዙውን ጊዜ ሊቀ ካህናት የሚመረጡት ለሮማውያን ያላቸውን ታማኝነት ያሳዩ እንደ ሆነ ወይም ጉቦ ሲሰጡ ነበር። ሮማውያን የሾሙት የመጀመሪያው ሊቀ ካህናት ለሮም መንግሥት ታማኝና ከሰዱቃውያን ወገን የነበረው ሐናንያ ነበር። ሐናንያ ከዘጠኝ ዓመት በኋላ በሮማውያን ቢሻርም፥ ለብዙ ዓመታት ከሊቃነ ካህናቱ በስተጀርባ ሆኖ ሲሠራ ቆይቷል። ከእርሱ በኋላ የተሾሙት ሊቃነ ካህናት በአመዛኙ አንድም የእርሱ ልጆች፥ አልያም በጋብቻ የሚዛመዱት ነበሩ። ሐናንያ ኢየሱስ በሚመረመርበት ጊዜ ሕጋዊ ሊቀ ካህን ባይሆንም፥ የመስቀል ሞት ፍርድ ሊፈረድበት ምርመራውን ተከታትሏል (ዮሐ 18፡1214)። ሮማውያን ብዙ የተለያዩ ሊቃነ ካህናት ከሾሙ በኋላ፥ የሐናንያ አማች የነበረውን ቀያፋን መረጡ። ቀያፋ በክርስቶስ ምድራዊ የአገልግሎት ዘመን ሁሉ ሕጋዊ ሊቀ ካህናት የነበረ ሲሆን፥ ክርስቶስ እንዲሰቀል የወሰነው እርሱ ነበር (ማቴ. 26፡3-4)።

የይሁዳ አገር በኋላ ቀርነቷና በዐመፀኛነቷ የምትታወቅ የሮም ግዛት ነበረች። ምንም እንኳ ብዙ የሮም ኣስተዳዳሪዎች ይሁዳን ያስተዳደሩ ቢሆንም፥ እጅግ የሚታወቀው ግን ጴንጤናዊው ጲላጦስ ነበር። ጲላጦስ ከ26 እስከ 36 ዓ.ም ድረስ ለ10 ዓመት ይሁዳን ገዝቷል። ጲላጦስ ልበ ደንዳናና ጨካኝ መሪ የነበረ ሲሆን፥ በኣገዛዝ ዘመኑ ብዙ ችግሮች ተከስተዋል። ኃይሉን ለማሳየት ሲል፥ የሮም ወታደራዊ ሰንደቅ ዓላማ በኢየሩሳሌም እንዲውለበለብ አድርጓል። ይህ ለአይሁዶች ትልቅ ስድብ በመሆኑ ባንዲራው ካልወረደ እንደሚያምፁ ገለጹ። በሌላ ጊዜ ለከተማይቱና ለቤተ መቅደሱ ውኃ ለማስመጣት የቤተ መቅደሱን ገንዘብ ለመጠቀም ሲሞክር፥ ተመሳሳይ የዐመፅ እንቅስቃሴ ተጀመረ። ጲላጦስ በተደጋጋሚ የዚህ ዓይነት በደል ይፈጽምባቸው ስለ ነበረ፥ አይሁዶችም ለሮማው ቄሣር አቤቱታ ያቀርቡ ነበር። ክርስቶስ የሚሰቀልበት ጊዜ ሲደርስ፥ የአይሁድ መሪዎች አሁንም ለቄሣር ጉዳዩን እንደሚያሳውቁ በመግለጽ ጲላጦስ እነርሱ የሚፈልጉትን እንዲያደርግ ጫና አሳደሩበት። ጲላጦስ የክርስቶስን ንጽሕና እያወቀ አይሁድን በመፍራትና ለፖለቲካዊ ሹመቱ በመስጋት አሳልፎ ሰጠው (ዮሐ. 19፡4-16)።

የሄሮድስ ፊልጶስ አገዛዝ (4 ዓ.ዓ34 ዓም) እና ሄሮድስ አንቲጳስ (4 ዓ.ዓ–39 ዓ.ም)

ሄሮድስ ፊልጶስ መልካም አስተዳዳሪ ነበር። የአገዛዝ ክልሉ የወንጌል ታሪክ ከተፈጸመበት ውጭ በመሆኑና ጭፍሮቹም አሕዛብ በመሆናቸው፥ በአዲስ ኪዳን ውስጥ ብዙም ትኩረት አልተሰጠውም። አብዛኛው የክርስቶስ አገልግሎት በእርሱ ክልል ውስጥ በመሆኑ፥ የገሊላ ገዥ የነበረው ሄሮድስ አንቲጳስ በወንጌላቱ ውስጥ በተደጋጋሚ ተጠቅሷል። ከታሪክ አንጻር፥ ሄሮድስ አንቲጳስ እንደ አባቱ ታላቅ መሪ ነበር። በገሊላ ባሕር ዳር የገነባትን ጥብርያዶስ የመሰሉ አዳዲስ ከተሞችን ኣንጾአል። የመከላከያ አምባዎችንም ገንብቷል። የናባጢያን 4ኛ ንጉሥን ልጅ አግብቶ ከእርሱም ጋር ቃል ኪዳን መሥርቷል። ነገር ግን ይህቺን የንጉሥ ልጅ ፈትቶ የወንድሙን የሄሮድስ ፊልጶስን ሚስት አገባ። ይህ የብሉይ ኪዳንን ሕግ የሚሽር ቀጥተኛ በደል ስለነበር መጥምቁ ዮሐንስ ድርጊቱን አውግዞታል። (አንዳንድ ምሑራን ክርስቶስ በማቴዎስ 5፡31-32 አንድ ሰው ሚስቱን ፈትቶ ሌላይቱን ቢያገባ አመንዝራ ይሆናል በማለት የገለጸው ይህንኑ የሄሮድስን ተግባር እያሰበ መሆኑን ያምናሉ)። በኋላ ሄሮድስ አንቲጳስ ሚስቱንና ልጇን ለማስደሰት ሲል፥ የመጥምቁ ዮሐንስ አንገት እንዲሰየፍ አድርጓል። ክርስቶስ ቀርቦ የተመረመረው በዚሁ በሄሮድስ አንቲጳስ ፊት ነበር (ሉቃስ 23፡7-15)። የናባጢያኑ ንጉሥ አሬታስ 4ኛ፥ ሄሮድስ አንቲጳስ ልጁን ፈትቶ ሌላ ስላገባ በዚህም እጅግ በመቀየሙ ውጊያ ከፍቶ አሸንፎታል።

የሄሮድስ አግሪጳ አገዛዝ (37–44 ዓ.ም)

ታላቁ ሄሮድስ ያምፁብኛል ብሎ ከገደላቸው ልጆቹ መካከል አሪስቶቡሉስ የሚባለው ኣንዱ ነበር። አሪስቶቡሉስ ሄሮድስ አግሪጳ የሚባል ልጅ ነበረው። ሄሮድስ አግሪጳ አባቱ ከተገደለ በኋላ፥ ከእናቱ ጋር ወደ ሮም ሽሽቶ በዚያ ከንጉሣውያን ቤተ ሰቦች ጋር ተወዳጀ። የሮም ንጉሥ የሆነው ጋይዮስ ካሊጉላ (37-41 ዓ.ም.) ወደ ሥልጣን ሲወጣ፥ አግሪጳን በሄሮድስ ፊልጶስ ግዛት ላይ ሾመው። ይህን የሰማው የገሊላው ገዥ ሄሮድስ አንቲጳስ ወደ ሮም ሄዶ የንግሥና ማዕረግ እንዲሰጠው ጠየቀ። ነገር ግን ንጉሥ ሄሮድስ አግሪጳ ተጨማሪ ግዛት ስለ ፈለገ፥ እጎቱ አግሪጳ አንቲጳስ በሮም ላይ ለማመፅ እንዳቀደ ለሮሙ ንጉሥ ገለጸለት። ከአግሪጳ ጋር ወዳጅ የነበረው ካሊጉላ የተነገረውን አምኖ በመቀበል ሄሮድስ አንቲጳስን ወደ ምርኮ ሰደደው። በአንቲጳስ ሥር የነበሩትን የገሊላና የጴሪያ ግዛቶችም ለአግሪጳ ሰጠው።

በንጉሥ ካሊጉላ ዘመን፥ አይሁዶች በተደጋጋሚ ብርቱ ችግር ገጥሞአቸዋል። በመጀመሪያ አይሁዶች ከሮም ባለሥልጣናት ልዩ ድጋፍ በሚያገኙበት በእስክንድርያ ከተማ በአይሁዶች ላይ ሁከት ተነሣ። የእስክንድርያ ሰዎች ለሮም ባቀረቡት አቤቱታ፥ አይሁዶች ካሊጉላን እንደ አምላክ እንደማያመልኩትና መሥዋዕትም እንደማያቀርቡለት አስረዱ። ይህም ካሊጉላን አስቆጣው። ከይሁዳ ውጭ በምትገኝ አንዲት አውራጃ ውስጥ የሚኖሩ አሕዛብ ለካሊጉላ መሠዊያ ሠርተው መሥዋዕት ማቅረባቸው ደግሞ ችግሩን አባባሰው። በአካባቢው የነበሩት አይሁዶች በሁኔታው ተቆጥተው መሠዊያውን ኣፈራረሱት። ካሊጉላ ይህን በሰማ ጊዜ እጅግ ተቆጣ። ከዚህም የተነሣ በቤተ መቅደሱ አካባቢ ለራሱ መሠዊያ ለማሠራትና መሥዋዕቶች እንዲቀርቡለት ለማድረግ ቆረጠ። ይህ አይሁዶችን እንደሚያስቆጣ ስለሚያውቅ፥ የጦር ሠራዊት ወደ ኢየሩሳሌም ላከ። የአይሁድ መሪዎች ሰአንቲዮከስ ኤፕፋነስ ዘመን የተከሰተውን የእርስ በርስ ጦርነትና እልቂት በማስታወስ፥ የተቆጣው የሠራዊቱ ጄኔራል ወደ ኢየሩሳሌም ከተማ ከመግባቱ በፊት ጄኔራሉ ይህን ተግባር እንዳይፈጽም ተማጸኑት። ጄኔራሉ ሊነሣ የሚችለውን ጦርነት ለማስቀረት ሲል የንጉሡን ትእዛዝ ቀስ በቀስ ለመፈጸም ወሰነ። (አንዳንድ ምሑራን ጳውሎስ በ2ኛ ተሰሎንቄ 28 ስለ ዐመፅ ሰው የጻፈው፥ ይህንን ሁኔታ እያስታወሰ ነው ብለው ያምናሉ።) በዚህ ጊዜ፥ ሄሮድስ አግሪጳ ወደ ሮም ሄዶ ንጉሡ ትእዛዙን እንዲለውጥ ተማጠነው። ብዙም ሳይቆይ ንጉሡን በጭካኔው የተበሳጩበት ሮማውያን ገደሉት።

ሄሮድስ አግሪጳ የተተኪው ንጉሥ ቀላውዴዎስ ወዳጅ ነበር። ቀላውዴዎስ በእስክንድርያ የተካሄደውን የፀረ-አይሁዳውያን ዓመፅ ከመግታቱም በላይ፥ ይሁዳንና ሰማርያን በመስጠት የአግሪጳን ግዛት አስፍቶላታል። ይህም ንጉሥ ኣግሪጳ የአያቱን የታላቁ ሄሮድስን አብዛኛውን ግዛት እንዲይዝ አድርጎታል።

የውይይት ጥያቄ፡- የሐዋ. 12፡1-23 አንብብ። ሀ) ንጉሥ አግሪጳ ለክርስቲያኖች ምን ፈጸመ? ለ) እግዚኣብሔር ጴጥርስን ለማዳን ምን አደረገ? ሐ) እግዚአብሔር ሄርድስ አግሪጳን የቀጣው በምን መንገድ ነበር? መ) እግዚአብሔር በገዥዎች ላይ ስለሚያመጣው ፍርድ ከዚህ ታሪክ ምን እንማራለን? ይህን ሁኔታ የተመለከትህባቸውን አንዳንድ ምሳሌዎች ዘርዝር።

ሄሮድስ አግሪጳ በአዲሱ የይሁዳ ግዛቱ አይሁዶችን ደስ ለማሰኘት ስለፈለገ፥ በክርስቲያኖች ላይ የሚያደርሱትን ስደት ይደግፍ ጀመር። ሐዋርያው ያዕቆብን ካስገደለ በኋላ፥ ሐዋርያው ጴጥሮስንም ሊጨምር ሲል የእግዚአብሔር መልአክ አዳነው። ኣግሪጳ በኢየሩሳሌም ዙሪያ ሦስተኛ የንብ በማሠራት አይሁዶችን ለማስደሰት ቢፈልግም፥ ቀላውዴዎስ ወደፊት አይሁዶች ዐመፅ ቢያስነሡ ይህ ለሮም አስቸጋሪ ሁኔታ እንደሚያስከትል ስለተገነዘበ ፈቃድ ሊሰጠው አልፈለገም። አግሪጳ በ44 ዓ.ም በቂሣርያ ከፍተኛ በዓል ከተከበረ በኋላ በድንገት ሞተ። ክርስቲያኖች ይህ ቀጥተኛ የእግዚአብሔር ፍርድ እንደሆነ ተመለከቱ። ፍርዱም የደረሰበት ያዕቆብን ስላስገደለ ብቻ ሳይሆን፥ ለእግዚአብሔር ብቻ የሚገባውን አምልኮና ክብር ስለተቀበለ ጭምር ነበር።

ሄሮድስ አግሪጳ ዳግማዊ (50-75 ዓም)

ምንም እንኳ ቀላውዴዎስ የሄሮድስ አግሪጳን ልጅ ለማንገሥ ቢፈልግም፥ የሮም መማክርት ጉባዔ ለዚህ ትልቅ ኃላፊነት ዕድሜው እንደማይፈቅድለት ወሰነ። ስለሆነም ቀላውዴዎስ ለአግሪጳ ዳግማዊ በሊባኖስ ትንሽ ግዛት ሰጠው። አግሪጳ ዳግማዊ በኋላ ያንን ግዛት እስከ ጳለስቲና ድንበር ድረስ ሊያሰፋው ችሏል። ከዚያም ኔሮ ከገሊላ አጠገብ የነበረውን ተጨማሪ መሬት ሰጥቶታል።

በዚህ ጊዜ ይሁዳ በሮም ባለሥልጣናት አገዛዝ ሥር ወደቀች፡፡ አይሁዶች በሄሮድስ አግሪጳ ዘመን ሰላማዊ ሕይወት ለመኖር ቢችሉም፥ ከ44 እስከ 66 ዓ.ም ድረስ ሮማውያን በአይሁዶች ላይ ተቃውሟቸውን እያጠናከሩ መጡ። በዚህ ጊዜ አይሁዶችን ከፖለቲካዊ ባርነት እናወጣለን የሚሉ ብዙ “መሢሖች” ብቅ ብቅ ማለት ጀምረው ነበር። እውነተኛውን መሢሕ አንቀበልም ያሉት አይሁዶች መሢሕ መጥቶ ነፃ እንዲያወጣቸው ይፈልጉ ነበር። የሮም መሪዎች እነዚህን መሢሖችና መሪዎቻቸውን በፍጥነት ይገድሉ ነበር። በይሁዳ የሚካሄደው ተከታታይ ዐመፅ ሰላም ስለነሣቸው የሮም ነገሥታት አይሁዶች ለብዙ ዓመታት የተሰጣቸውን መብት ነፈጓቸው። የይሁዳ መቃቢያውያንን ዘመን በማስታወስ አይሁዶች ነፃ የሚያወጧቸውን ወታደራዊ መሪዎች ተመኙ። ሕዝቡ ለነጻነቱ ተዋግቶ ለመሞት ፈቃደኛ ነበር።

አንዳንድ ምሑራን ይህ ታላቅ ዐመፅና የብሔርተኝነት ስሜት፥ በቤተ ክርስቲያን ውስጥ በአይሁድና አሕዛብ ክርስቲያኖች መካከል ለተከሰተው ትግል መንሥዔ እንደሆነ ይናገራሉ። የብሔራዊ ነጻነት ፍላጎት የተስፋፋው በኢየሩሳሌምና በጳለስቲና ብቻ አልነበረም። በዓለም ሁሉ ተበትነው የሚገኙ አይሁዶች ለነጻነት የሚደረገውን ትግል ለመደገፍ በመቁረጣቸው፥ በአይሁድና በአሕዛብ መካከል የነበረው ልዩነት በአዲስ መልክ አገረሸ። ምሑራን በዚህ ጊዜ ክርስቲያን አይሁዶች አንዱን አቅጣጫ ለመምረጥ ተገድደው እንደነበረ ያስባሉ። ለአይሁዶች ያላቸውን ታማኝነት በማሳየት አሕዛብን መጥላትና ምንም ዓይነት ግንኙነት አለማድረግን፥ ለጳለስቲና ነጻነት በመዋጋት የእንስሳት መሥዋዕትና የአባቶች ትውፊት እንደገና እንዲቀጥል፥ የኣምልኮውም ሥርዐት እንዲመለስ ማድረግ? ወይስ ከአሕዛብ አማኞች ጋር መወገን? እዚህ ላይ አንዳንድ የአይሁድ ክርስቲያኖች ክርስትናቸውን ደብቀው እንደ አይሁዶች በማምለክ ከዚህ አጣብቂኝ ለመውጣት ሞክረዋል። ከአሕዛብ ክርስቲያኖች ጋር የነበራቸውን ግንኙነት ለማቋረጥ ስላልፈለጉ ኣሕዛብም እንደ እነርሱ እንዲገረዙ ጠየቁ። ይህ አሕዛብን ወደ ይሁዲነት መለወጥ አብረዋቸው ለማምለክ እንዲችሉና ታማኝ አይሁዶች ብቻ ሳይሆኑ ጀግናም እንደሆኑ እንዲሰማቸው አደረጋቸው። ወይም ደግሞ ከአሕዛብ ጋር ማንኛውንም ዐይነት ኅብረት ላለማድረግ ይወስኑ ነበር። ይህም በብሔርተኝነት ላይ የተመሠረቱ ሁለት አብያተ ክርስቲያናት እንዲመሠረቱ አደረጉ ምንም እንኳ ይህ ትምህርት አይሁድ ክርስቲያኖች በሌሎች አይሁዶች እንዳይሰደዱ ለመከላከል ቢያስችልም፥ እንዲህ ዓይነቱ ጥያቄ አሕዛብ በክርስቶስ እንዳያምኑ ያደርግ ነበር። ይህ ደኅንነትን እነርሱ የሚፈጽሙት «ተግባር» ከማድረጉም በላይ፥ የክርስቶስን የአካል አንድነት ያናጋል። የአሕዛብ ሐዋርያ የነበረው ጳውሎስ ይህን ትምህርት በብርቱ ተቃውሟል፤ እንደ ጳውሎስ እምነት አንድ አዲስ አካል አለ፤ በዚህም አካል ውስጥ መንፈሳዊ ዝምድና እንጂ ሥጋዊ ዝምድና ስፍራ የለውም (ቆላ. 3፡1)። በዚህ አዲስ አካል ውስጥ የሚደረግ ማንኛውም ዐይነት መከፋፈል ክርስቶስ የሞተለትን እውነት ይጎዳዋል። ከዚህም በተጨማሪ ደኅንነትና በእግዚአብሔር ዘንድ ተቀባይነትን ማግኘት ሁልጊዜ የእምነት እንጂ ባህልን የመለወጥ ወይም አንድን ተግባር የመፈጸም ጉዳይ አይደለም። የዕብራውያን ጸሐፊ የብሉይ ኪዳን የአምልኮ ሥርዐት በእግዚአብሔር ዕቅድ ውስጥ ጊዜያዊ በመሆኑ መወገዱ እንደማይቀር ገልጾአል (ዕብ 8፡13)። የአይሁዶችን ስደት ፈርቶ እምነትን መደበቅ፥ በእግዚአብሔር ፊት ዐመፅ ስለሆነ፥ ፍርድን ያስከትላል (ዕብ 10፡15-39)።

የውይይት ጥያቄ፡ ሀ) ከራሳችን ጎሳ ወይም ቤተ ሰብ እባላት በላይ ክርስቲያኖችን መደገፍ ለምን እንደሚከብድ ግለጽ። ለ) የቤተ ክርስቲያን ምእመናን ጎሰኝነት ተጠናውቷቸው፥ እንደ ክርስቲያን ግን መንፈሳዊ ቤተ ሰባቸው የበለጠ ኣስፈላጊ መሆኑን የዘነጉበትን አጋጣሚ የሚያሳዩ ምሳሌዎችን አቅርብ። ከዚህ የተነሣ በቤተ ክርስቲያን ውስጥ የታዘብካቸው ችግሮች ምን ምንድን ናቸው?

ምንም እንኳ አብዛኞቹ የአይሁድ ክርስቲያኖች በእምነታቸው ለመጽናት ቢወስኑም፥ አንዳንዶች ከአሕዛብ ጋር የነበራቸውን ግንኙነት ማቋረጣቸው ግልጽ ነው። የአይሁድ ክርስቲያኖች ከአሮጌው አምልኳቸው ጋር እንዴት እንደሚዛመዱና የአይሁድን ሕዝብ እንዴት እንደሚደግፉ ለማወቅ ተቸግረው ነበር። በሐዋርያት ሥራ 21፡17-24 ላይ የአይሁድ ክርስቲያኖች ጳውሎስ መሥዋዕት በማቅረብ ለብሉይ ኪዳን አምልኮ ሥርዐት ያለውን ታማኝነት እንዲያሳይ ጠይቀውታል። ጳውሎስም አይሁዶችን በመፍራት ሳይሆን፥ ክርስቲያን በሆኑትና ባልሆኑ አይሁዶች መካከል የነበረውን የተቃውሞና የጥርጣሬ ግድግዳ ለማፍረስ ሊል የጠየቁትን ፈጽሟል። በእርሱ ዘንድ አንድ ሰው የሚያመልክበት ሁኔታ ትልቅ ለውጥ የለውም። ከመልእክቶቹ እንደምንረዳው ጳውሎስ ያድናቸው ዘንድ ከአይሁዳውያን ጋር አይሁዳዊ፥ ከአሕዛብም ጋር አሕዛብ ሆኖ አገልግሏል (1ኛ ቆሮ. 9፡20)። ይህ ተግባሩ በኢየሩሳሌምና በሮም ለአራት ዓመት እንዲታሰር አድርጎታል።

ምንም እንኳ ከአይሁድ መሪዎች ስደት ቢኖርም፥ በቤተ ክርስቲያን ታሪክ ውስጥ እስከዚህ ጊዜ ድረስ ብዙ አይሁዶች በአይሁድ ክርስቲያኖች መንፈሳዊ ሕይወት ተስበው በክርስቶስ ሊያምኑ ችለዋል። ነገር ግን የአይሁዶች ብሔርተኝነት እየጠነከረ በመሄዱና በአይሁዶችና በአሕዛብ መካከል ያለውም ልዩነት እየሰፋ ስለመጣ፥ የኣይሁድ ክርስቲያኖች ክርስቶስን በመከተል ከሕዝባቸው ወይም ከትውፊታዊው ይሁዲነት የመገንጠሉን ከባድ ምርጫ ለማድረግ ተገደዱ። የአሕዛብ ክርስቲያኖች በቁጥር እየበዙ ሲሄዱ ደግሞ በቤተ ክርስቲያን ውስጥ የነበራቸውን ኃይል ያጡ ጀመር። ይህም ብዙ ኣይሁዶች ክርስቶስን እንዳይከተሉ አድርጓቸዋል። ብዙዎቹ እምነታቸውን ትተው ወደ ይሁዲነት ለመመለስና ከስደት ነፃ ለመሆን ወሰኑ። የዕብራውያን ጸሐፊ እነዚህ አይሁዶች ወደ ይሁዲነት ቢመለሱ ከዚያ በኋላ ደኅንነትን ለማግኘት እንደማይችሉና ይልቁንም የእግዚአብሔርን ፍርድ እንደሚቀበሉ በመግለጽ አስጠንቅቋቸዋል (ዕብ. 10፡15-39)።

የውይይት ጥያቄ:- ቤተ ክርስቲያንህ፥ ቤተ ሰቦቻቸው ወይም የጎሳ አባሎቻቸው ከባህላዊ ሃይማኖታቸው እንዳይወጡ ለሚከለክሏቸው ሰዎች፥ የደኅንነት ተስፋ በክርስቶስ ብቻ እንደሚገኝና በቤተ ክርስቲያን የጎሳ ልዩነት ሳይደረግ ሰዎች ሁሉ ኣንድ ቤተ ሰብ መሆናቸውን በግልጽ ለማስተማር ምን እያደረገች ነው?

የሮም ቀንደኛ ደጋፊ የነበረው ዳግማዊ አግሪጳ ብዙውን ጊዜ በሃይማኖታዊ ጉዳዮች ላይ የሮም ገዥና አማካሪ ሆኖ ይሠራ ነበር (የሐዋ. 26፡24-32)። በ62 ዓ.ም. ፊስጦስ ከሞተ በኋላ ለሦስት ዓመት ያህል የሮም ገዥ አልተተካም ነበር። ዳግማዊ ሐናንያ የሚባል ሊቀ ካህናት ይህን አጋጣሚ በመጠቀም፥ ለክርስቲያኖች የነበረውን ጥላቻ ማንጸባረቅ ጀመረ። ምንም እንኳ የክርስቶስ ወንድም የነበረው ያዕቆብ በቤተ መቅደሱ ውስጥ የሚያመልክና ለመንፈሳዊነቱም በአይሁዶች የተከበረ ቢሆንም፥ ሐናንያ የኢየሩሳሌም ቤተ ክርስቲያን መሪ የነበረውን ያዕቆብን አስገደለው።

ሁከትና ብጥብጥ በኢየሩሳሌም ለሚኖሩ አይሁዶች የዕለት ተዕለት ክስተት ሆነ፡፡ እያንዳንዱ ተተኪ የሮም ገዥ አይሁዶችን ደስ ማሰኘት አልቻለም። እነዚህ የሮም ገዥዎች ብዙውን ጊዜ ለዐመፅ ኃይልን የሚጠቀሙ ጨካኞች ነበሩ፡፡ በሮም ላይ የሚያምፁ ሰዎች በተገደሉ ቁጥር፥ የአይሁዶች ቁጣ እየጨመረ ይሄድ ጀመር። የሮም ባለሥልጣናት በበኩላቸው ከሰዎች ገንዘብ ለመሰብሰብ ይስገበገቡ ነበር። አይሁዶች በሃስሞኒያን አገዛዝ ዘመን ነጻነትን ይፈልጉ ነበር። አንድ ሰው ከዳዊት የዘር ሐረግ ተነሥቶ የአይሁድ ጠላቶችን በመደምሰስና ሰላማዊ መንግሥት በመመሥረት የብሉይ ኪዳንን ትንቢት እንዲፈጽም ይናፍቁ ነበር። በመጨረሻም በ66 ዓም. ይህ በሮማውያን ላይ የነበረው ቁጣ ገንፍሎ ጦርነትን ቀሰቀሰ።

የመጨረሻው የሮም ገዥ ፍሎረስ የተዋጣለት የአስተዳደር ችሎታ ያልነበረውና በይሁዳም ውስጥ ለሚቀሰቀሉት ዐመፆች ግድ ያልነበረው ሰው ነበር። ይህ ሰው አሕዛብ በአይሁዶችና በሃይማኖታቸው ላይ እንዲያላግጡ አድርጓል። የቤተ መቅደስ ሀብት የነበረ ብዙ ገንዘብ ከመውሰዱም በላይ፥ ስለተቃወሙት ብቻ ብዙ ሰዎችን አስገድሏል። በርካታ ሀብታም ነጋዴዎችና ዳግማዊ ኣግሪጳ ሕዝቡ እንዳያምፁ ቢለምኗቸውም ሊሰሟቸው ግን ፈቃደኞች አልነበሩም። ስለሆነም በአንድ ካህን እየተመሩ በመዋጋት፥ በኢየሩሳሌም የነበረውን የሮማውያን ሰፈር ወረሩ። ለአገራቸውና ለነጻነታቸው ቀናኢዎች የነበሩ የእንቅስቃሴው አባላት ወዲያውኑ ከዚህ ቡድን ጋር በመቀላቀል ሌላውን የሮም ሰፈር ያዙ። ከዚያም የኢየሩሳሌምን ከተማ ወረሩ። አለመታደል ሆነና፥ ቀደም ሲል ቤተ መቅደሱን የተቆጣጠረው ቡድን የቀናኢውን ቡድን በስግደት ላይ እያለ ተኩሰው በመግደላቸው፥ የእርስ በርስ ውጊያ ገጠሙ። ሮማውያን ዐመፁን ለማስቆም ከሶርያ የላኩት ሠራዊት በቁጥሩ አነስተኛ በመሆኑ፥ ብዙ ወታደሮች ከሞቱበት በኋላ አፈገፈገ። ይህ የሮም ሠራዊት መሸነፍ ታላቅ ተስፋ በማስገኘቱ፥ ሌሎችም አገሮች በውጊያው ተባበሩ።

ሮም በጳለስቲና የተቀሰቀሰውን ዐመፅ ለመቆጣጠር ቁርጥ ውሳኔ ስላደረገች፥ ምርጥ ተዋጊ እንደሆነ የሚነገርለትን ቪስፓሲያን የተባለ ጄነራሏንና 60,000 ወታደሮች እንደገና ላከች። ከሰሜን የመጡት እነዚህ ወታደሮች ብዙም ሳይቆዩ ገሊላንና የኢየሩሳሌምን አካባቢዎች ተቆጣጠሩ። ወደ ኢየሩሳሌም ከተማ በቀረቡ ጊዜ ንጉሥ ኔሮ ራሱን በመግደሉ፥ በሮም የእርስ በርስ ጦርንት ተቀሰቀሰ፡ ቪስፓሲያን በኢየሩሳሌም ላይ ለመክፈት ያሰበውን ጦርነት ለጊዜው ገትቶ የሚሆነውን ይጠባበቅ ጀመር። አይሁዶች ይህ ሁኔታ እግዚአብሔር ለእነርሱ የመዋጋቱ ምልክት እንደሆነ በማሰብ፥ ሮም በእርስ በርስ ውጊያ እንደምትወድም ገመቱ። ከአንድ ዓመት በኋላ ግን ነገሮች በመለወጣቸው ቬስጋሲያን ወጊያውን ቀጥሎ፥ ከኢየሩሳሌምና ከሌሎች ሦስት ሰፈሮች በስተቀር አገሩን ሁሉ በፍጥነት ተቆጣጠረ። ብዙም ሳይቆይ ቬስፓልያን የንጉሠ ነገሥትነቱን ሥልጣን ስላገኘ፥ ልጁ ቲቶ ውጊያውን እንዲያጠናቅቅ ሾመው።

በዚህ ጊዜ ግንባር ፈጥረው የጋራ ጠላታቸውን መውጋት ሲገባቸው፥ የተለያዩ የአይሁድ መሪዎች፥ ኢየሩሳሌምን ለመቆጣጠር እርስ በርሳቸው ይዋጉ ነበር። በሺዎች የሚቆጠሩ ምእመናን በዓለ ኀምሳን ለማክበር ወደ ኢየሩሳሌም ከተማ መጥተው ስለነበር የምግብና የውኃ እጥረት ሆነ። ሰዎች ሰዎችን ለመብላት ተገደዱ። ከብዙ ወራት በኋላ ነሐሴ 27 ቀን 70 ዓ.ም. ባቢሎናውያን የሰሎሞንን ቤተ መቅደስ በደመሰሱበት ቀን ሮማውያንም ቤተ መቀደሱን ደመሰሱ። በዚህ ውጊያ ከሮማውያን ጋር የተባበረው ዳግማዊ አግሪጳ፣ ምናልባትም ከቲቶ ፍላጎት ውጭ ከወታደሮቹ ጋር በመሆን ያንን ታላቅ ቤተ መቅደስ እሳት ለኩሰው አነደዱት። ቤተ መቅደሱን፤ የኢየሩሳሌምን ቅጥርና በከተማይቱ ውስጥ የነበሩትን ቤቶች ሁሉ አፈራረሱ። ብዙ ምሑራን ይህ ክርስቶስ ስለ «ጥፋት ርኩሰት» የተናገረው ትንቢት ፍጻሜ እንደሆነ ይናገራሉ (ማቴ. 24፡15)። በብዙ ሺዎች የሚቆጠሩ አይሁዶች ሲገደሉ፥ ሌሎቹ ለባርነት ተዳርገዋል። ከዚህ በኋላ፥ በጳለስቲና የሚኖሩ አይሁዶች ኃይል ተዳከመ። የዕብራውያን መልእክት ጸሐፊ እንደተናገረው ብሉይ ኪዳን ከእንስሳቱ መሥዋዕት ጋር ተፈጸመ (ዕብ. 8፡13)። ከዚህ በኋላ አይሁዶች ለ2000 ዓመታት ያህል ቤተ መቅደስም ሆነ የእንስሳት መሥዋዕት ለማቅረብ ዕድል አልነበራቸውም። አሁን ግን የአይሁድ መሪዎች ቤተ መቅደሱን እንደገና ለመሥራትና መሥዋቶችን ለማቅረብ እያቀዱ ናቸው።

የውይይት ጥያቄ፡- በጳለስቲና እገር የምትኖር አይሁዳዊ ክርስቲያን ብትሆን ኖሮ፥ ሕዝብህና ከተማህ ሲወድሙ መመልከት ምን ዓይነት ስሜት ያሳድርብህ ነበር?

ምንም እንኳ ብዙ አይሁዶች ቢገደሉና ለባርነት ሲሸጡም፥ ጥቂት አይሁዶች በፈራረሰችው ኢየሩሳሌም ውስጥ ቤቶቻቸውን መልሰው ይገነቡ ጀመር። ከኢየሩሳሌም ውጭ ሌሎች ሦስት ሰፈሮችን የተቆጣጠሩት የአገርና የነጻነት ቀናኢ ቡድኖች ለሦስት ዓመት ያህል መዋጋታቸውን ቀጠሉ። እነዚህ ቡድኖች ለሮማውያን እጅ ከመስጠት ይልቅ፥ ራሳቸውን በራሳቸው አጠፉ። በ135 ዓ.ም አይሁዶች በሮም ላይ እንደገና ዐምፀው በግብፅና በቀሬና ላይ ጥቃት ሰነዘሩ። ሮማውያን ይህን ዐመፅ በፍጥነት ከተቆጣጠሩ በኋላ እንድም አይሁዳዊ ወደ ኢየሩሳሌም እንዳይገባ ከለከሉ። ቤተ መቅደሱ በነበረበት ስፍራ ለሮም ጣዖት ቤተ መቅደስ በመሥራት አረማዊ መሥዋዕቶችን ያቀርቡ ጀመር። በ70 ዓ.ም ኢየሩሳሌም ስትፈራርስ ከሰዱቃውያን ኣብዛኞቹ ተገድለዋል። ፈሪሳውያንና ብዙ የአይሁድ ክርስቲያኖች ጃምኒያ ወደተባለች ከተማ ፈልሰው ያለ ቤተ መቅደስና መሥዋዕት ሃይማኖታቸውን መከተል ጀመሩ።

በዚህ ጊዜ ክርስቲያኖች ምን ሆኑ? ሮማውያን ከተማይቱን ከመደምሰሳቸው በፊት አብዛኞቹ ክርስቲያኖች ለቅቀው ሳይወጡ እንዳልቀሩ ይገመታል። በጃምኒያ ከተማ ሳይሰፍሩ አልቀሩም። ነገር ግን ጊዜው እያለፈ ሲሄድ ቁጥራቸው እየተመናመነ ስለመጣ፥ በመጀመሪያው ምእተ ዓመት መጨረሻ ላይ በስፍራው የቀሩት አይሁዳውያን ክርስቲያኖች ቁጥር አነስተኛ ነበር።

(ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የአዲስ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ ስለዚህ አስደናቂ አገልግሎታቸው እግዚአብሔር ይባርካቸው፡፡)

2 thoughts on “የሮም ግዛተ ዐፄና የሄሮድስ አገዛዝ”

  1. ስለ ሁሉም መልካም ልፋታችዉ ጌታ ይበርካችዉ
    #ፈተነዉን ጨርሼ sumit አድርጌዉ ነበረ ግን በ email አልመጣልኝም።

    1. ሰላም ደስታ፣

      ጥያቄዎቹን መልስክ ከጨረስክና ከላክ በኋላ ውጤቱ በኢሜይ አድራሻህ እንዳልደረሰክ ገልጽክ የጻፍክልኝ ደርሶኛል፡፡ በመጀመሪያ ስለገጠመክ ሁኔታ አዝናለው፡፡ ይሄ ኢሜይ ደርሶህ ማንበብ ከቻልክ ችግሩ ከኢሜይል አድራሻክ ጋር የተያያዛ ይደለም ማለት ነው፡፡ መልስህ እኔም ጋር ስላልደረሰ፣ ምናልባት የላክ መስሎህ ሳትልክ ቀርተህ ሊሆን ስለሚችል ደግመህ ላክና ውጤቱን እይ፡፡

      ተባረክ!

Leave a Reply

Discover more from

Subscribe now to keep reading and get access to the full archive.

Continue reading