ማርቆስ 4፡1-41

ሀ. ክርስቶስ ስለ መንግሥቱ አስተማረ (ማር. 4፡1-34)። እንደ ማቴዎስ ሁሉ፥ ማርቆስም የክርስቶስን ምሳሌዎች በአንድ ክፍል ውስጥ አስቀምጧል። ይህ ማርቆስ ስለ ክርስቶስ ትምህርት ከገለጸባቸው ጥቂት አጋጣሚዎች አንዱ ነው። ክርስቶስ በእርሱ ላለማመን ልባቸውን ያደነደኑት አይሁዶች ፍርድን እንደሚቀበሉ ለማሳየት፥ በምሳሌ እንደሚናገር ለደቀ መዛሙርቱ ተናግሯል። ነገር ግን ለጥሪው ምላሽ ሰጥተው የተከተሉት የክርስቶስ ደቀ መዛሙርት፥ እውነትን የበለጠ እንዲረዱ በምሳሌ ያስተምራቸዋል። እነዚህ ምሳሌዎች እያንዳንዳቸው በክርስቶስ መንግሥት፣ ሕይወት ምን እንደሚመስል ያስተምራሉ።

1. የአራት ዓይነት መሬት ምሳሌ (ማር. 4፡1-20)። ደቀ መዛሙርቱ የክርስቶስን መልካም የምሥራች ካካፈሉ በኋላ ምን ሊጠብቁ ይገባል? ክርስቶስ ሰዎች በሦስት መንገዶች ምላሽ እንደሚሰጧቸው አስተምሯል። በመንገድ ላይ እንደወደቀው ዘር፥ ከመጀመሪያው ለመቀበል የማይፈልጉ ሰዎች ይኖራሉ። የሚያምኑ መስለው ከቀረቡ በኋላ ችግር ወይም ስደት በደረሰባቸው ጊዜ በጭንጫ መሬት ላይ እንደተዘራው ዘር የሚክዱም ይኖራሉ። አማኞች መስለው ከቀረቡ በኋላ ከደቀ መዝሙርነት ጎዳና ይልቅ የዓለምን መንገድ በመውደዳቸው ምክንያት፥ በእሾህ መካከል እንደተዘራው ዘር ወደ ኋላ የሚመለሱ ሰዎች ይኖራሉ። በአንጻሩ በመልካም መሬት ላይ እንደወደቀው ዘር እምነታቸውን በተለያዩ መንገዶች ሊገልጹ የሚችሉት ጥቂቶች ብቻ ናቸው።

የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) ሰዎች እነዚህን አራት ምላሾች ሲሰጡ ያየህባቸውን ሁኔታዎች በምሳሌዎች አብራራ። ለ) ለደቀ መዛሙርት እነዚህን አራት መንገዶች ማወቁ ለምን ያስፈልጋል?

2. የመቅረዝ ምሳሌ (ማር. 4፡21-25)። ክርስቶስን ለመከተል የሚፈልጉ ሰዎች የሮም ክርስቲያኖች የሚጋፈጡት ዓይነት ስደት ቢኖርም እንኳ፥ እምነታቸውን ከመደበቅ ይልቅ የእምነታቸው ብርሃን ለሁሉም እንዲያበራ ማድረግ እንዳለባቸው ሊያውቁ ይገባ ነበር። ከሰዎች የተሸሸጉ ምሥጢራዊ ማኅበረሰብ ከመሆን ይልቅ፥ በቃላቸው ብቻ ሳይሆን በሕይወታቸው ጭምር የክርስቶስ መንግሥት ተከታዮች መሆናቸውን ማሳየት ያስፈልጋቸው ነበር። የክርስቶስ ደቀ መዛሙርት መሆናቸውን ማሳየት ያስፈልጋቸው ነበር። ክርስቶስ ደቀ መዛሙርቱ እርሱን ለመስማትና በሕይወታቸው ውስጥ እውነቱን ተግባራዊ ለማድረግ ባይፈልጉ፥ ፍርድ እንደሚደርስባቸው አስጠንቅቋቸዋል። የክርስቶስን ትምህርት ይበልጥ ተግባራዊ ባደረጉ ቁጥር፥ ተጨማሪ መንፈሳዊ እውነቶችና ግንዛቤዎችን ይሰጧቸዋል። እኛም መንፈሳዊ እውነቶችን ተግባራዊ የማናደርግ ከሆነ፥ መንፈሳዊ እውነቶችን የመገንዘብ ችሎታችን ይቀንሳል።

የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) ይህ መንፈስ ቅዱስ የሚያስተምረንን ተግባራዊ ማድረግ እንዳለብን የሚያስጠነቅቀን እንዴት ነው? ለ) በቅርቡ መንፈስ ቅዱስ ያስተማረህን ሁለት እውነቶች ግለጽ። እንዴት ተግባራዊ እያደረግህ እንደሆነ አብራራ።

3. የአዳጊ ዘር ምሳሌ (ማር. 4፡26-29)። ይህ ምሳሌ የሚገኘው በማርቆስ ወንጌል ውስጥ ብቻ ነው። ክርስቶስ በዚህ ምሳሌ፥ መንግሥቱና ቤተ ክርስቲያኑ፥ እንደ ዘር በምሥጢራዊ መንገድ በራሷ የማደግ ኀይል እንዳላት አስተምሯል። ሰዎች ዕድገቱ እንዴት እንደሚካሄድ ለመገንዘብ ቢሞክሩም፥ ሁልጊዜም ምሥጢር ይሆናል።

4 የሰናፍጭ ቅንጣት ምሳሌ (ማር. 4፡30-34)። የኢየሱስ መንግሥት፥ ጅማሬዋ ልክ እንደ ኢየሱስና 12ቱ ሐዋርያት፥ አነስተኛ ይመስላል። ኃያል መንግሥት ባላቸው በሮማውያን ዓይን ፊት፥ በጣም አነስተኛና ምንም ያማያሳስብ ሆኖ ታያቸው። ነገር ግን ያቺ አነስተኛ መንግሥት በአስደናቂ መንገድ አድጋ፥ ታላቁ የሮም መንግሥት እንዲለወጥ ታደርጋለች። ቤተ ክርስቲያንም አድጋ፥ ከሮም መንግሥት በበለጠ መልኩ ዓለምን ታዳርሳለች።

ለ. ኢየሱስ በተፈጥሮ ላይ ኃይሉን አሳየ (ማር. 4፡35-41)። ኢየሱስ የእግዚአብሔር ልጅ ከሆነ፥ በፍጥረቱ ላይ ምን ኃይል አለው? ማርቆስ ይህን ታሪክ በመናገር፥ ክርስቶስ በፈጠራት ዓለም ላይ ሙሉ ሥልጣን እንዳለው አመልክቷል። ማዕበሎችና ነፋሳት ሁሉ ለክርስቶስ ቃል ታዝዘዋል። የክርስቶስ ጎይል በደቀ መዛሙርቱ ላይ ከፍተኛ ስሜት በማሳደሩ «ፈሩ»። በተጨማሪም እርሱ ከተራ ሰው የላቀ መሆኑን ስለ ተገነዘቡ፥ ትክክለኛ ማንነቱን ለመረዳት ተገድደው ነበር።

ነገር ግን ይህ ታሪክ እካላዊም ሆነ የስደት ማዕበል፥ በክርስቶስ ተከታዮች ላይ እንደሚደርስ ያሳያል። ከዚህ ማዕበል ማምለጥ አይቻልም። በዚህም ጊዜ በፍርሃት ልንኖር ወይም ክርስቶስ ከእኛ ጋር እንዳለ በመገንዘብ በእርሱና ማዕበሉን በመቆጣጠር ችሎታው ልንታመን እንችላለን።

የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) ስላጋጠመህ አንድ ማዕበል ግላጽ። በዚህ ጊዜ ከምን ዓይነት ልማቶች ጋር ታግለሃል። እምነት ነበረህ ወይስ አልነበረህም? ለ) ለማዕበሉች የምንሰጠው ምላሽ በክርስቶስ ላይ ያለንን የእምነት መጠን የሚያመለክተው እንዴት ነው?

(ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የአዲስ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)

Leave a Reply

%d