ማርቆስ 5:1-20

የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) የሰይጣን ኀይል አይሎ ያየህበትን ጊዜ ግለጽ። ለ) የኢየሱስ ኀይል ሰይጣንን ሲያሸንፍ ያየህበትን ሁኔታ ዓለጽ፡፡ ይህ ስለ ኢየሱስ ምን ያስተምረናል? ሐ) ብዙ ክርስቲያኖች ሰይጣንን፡ ቡዳን፥ እርግማንን የመሳሰሉትን የሚፈሩት ለምንድን ነው? መ) መጽሐፍ ቅዱስ ስለዚህ ፍርሃት ምን ያስተምራል?

የግርማ አባት ጠንቋይ ነበሩ። እርሱ ከልጅነቱ ጀምሮ ለሰይጣን የተሰጠ በመሆኑ ብዙ ክፉ መናፍስት ሰፍረውበት ነበር። እያደገ ሲመጣ የሰይጣን ጭቆና በዛበት። አንድ ቀን ጭንቀቱን መቋቋም ተስኖት ራሱን ለማጥፋት ሞከረ። በዚህ ጊዜ አንድ ክርስቲያን ሕይወቱን አተረፈለት። ክርስቲያኑ በኢየሱስ ክርስቶስ ቢያምን ከሰይጣን ነፃ እንደሚወጣ ገለጸለት፡ ግርማም ምስክርነቱን ሰምቶ አመነ። ወዲያውኑ ክፉ መናፍስት ወደ መሬት ጣሉት። እዚያ ወድቆ ይንፈራፈርና ያጓራ ጀመር። ክርስቲያኑ ወዳጆቹን ሰብስቦ ብዙ ጸሎት ካደረገ በኋላ፥ መናፍስቱ ለቅቀውት ወጡ።

በቀጣዩ እሑድ ግርማ በአቅራቢያው ወደምትገኝ ቤተ ክርስቲያን ሄደ። በአምልኮው ጊዜ አንድ ሰው፥ ሰይጣን ታስሮ ወደ ጥልቁ እንዲወርድ እያዘዘ ሲጸልይ ሰማ። ሰዎች፥ «በኢየሱሱሱሱሱሱስ ስም?» እያሉ ይጮኹ ጀመር፡ «ሰዎች የኢየሱስን ስም እንዲህ የሚጠሩት ለምንድን ነው?» ሲል አሰበ። ክርስቲያኖቹ የግርማ አባት ኃይል አላቸው ብሎ የሚያምንባቸውን ቃላት በሚደጋግምበት መንገድ የኢየሱስ ስም ምትሐታዊ ኃይል አለው ብለው ስለሚያምኑ ይሆን?

በሌላ ስፍራ ከአንድ ጠንቋይ አጠገብ የመጽሐፍ ቅዱስ ትምህርት ቤት ተከፍቶ ነበር። አንዳንድ ጊዜ ጠንቋዩ ሌሊት ሌሊት ከበሮውን እየመታ በማጓራት ክርስቲያኖችን ይረግም ነበር። በዚህ ጊዜ የመጽሐፍ ቅዱስ ት/ቤት ተማሪዎች ይፈራሉ። ከመኝታ ክፍላቸው ተሯሩጠው በመውጣት፥ «በኢየሱሱሱሱስም ስም!» እያሉ ድምፃቸውን አጉልተው ይጮኻሉ፡፡

ኢየሱስ ከሰይጣን ጋር ምን ዓይነት ግንኙነት አለው? እኛ በሰይጣን ላይ ምን ሥልጣን አለን? የኢየሱስ «ስም» ከሥልጣናችን ጋር ምን ግንኙነት አለው? የኢየሱስን ስም እየደጋገሙ መጥራቱ ተጨማሪ ኃይል ይሰጠዋል?

ይሄ የሚያጠራጥር አይደለም። የምንፋጠጠው ከሰይጣን፥ ከትልቅ ጠላት ጋር ነው። መጽሐፍ ቅዱስ ሊውጠን ፈልጎ ከሚያገሳ አንበሳ ጋር ያነጻጽረዋል (1ኛ ጴጥ. 5፡8)። ጎይሉ ከፍተኛ ነው። ተአምራትን መሥራት ይችላል፥ ተፈጻሚነት የሚኖራቸውን እርግማኖችና ሌላም ሊያደርግ ይችላል። ነገር ግን ኢየሱስን በመታዘዝ ከሚመላለሱ ክርስቲያኖች ጋር ሲነጻጸር፥ ጎይሉ ምንድን ነው? ከዚህ በበለጠ ደግሞ ከኢየሱስ ጋር ሊነጻጸር፥ ኀይሉ ምንድን ነው? ለክርስቲያኖች መጽሐፍ ቅዱስ የሚያስተምረውን እውነት በግልጽ መረዳቱ አስፈላጊ ነው። ልናስወግዳቸው የሚገቡን ሁለት አክራሪ አቋሞች አሉ። ብዙ የተማሩ በተለይም በምዕራቡ ዓለም የሚገኙ ክርስቲያኖች ሰይጣንን ችላ ይላሉ። ሰይጣን መኖሩን ሊያምኑ ቢችሉም፥ ስለ እርሱ አያሳስባቸውም። ዛሬ እንደምንመለከተው ሰይጣን ብርቱ ጠላት ስለሆነ፥ እነዚህ ክርስቲያኖች በእርሱ ተሸንፈዋል። ሰይጣን ክርስቲያኖችን ለማሸነፍ የሚሠራባቸውን መንገዶች የማያውቁትን ክርስቲያኖች በቀላሉ ያጠቃቸዋል። ሌሎች ደግሞ ስለ ሰይጣን ሁልጊዜም ያስባሉ። በሚጸልዩበት ጊዜ ሁሉ ሰይጣን ወደ ጥልቁ እንዲጣል ያዝዛሉ። የሚደርሰው ጉዳት ሁሉ የሰይጣን ጥቃት እንደሆነ ያምናሉ። ብዙውን ጊዜ የሰይጣንን ኀይል ይፈራሉ። እርሱን እየፈሩ ስለሚኖሩ ሰይጣን እነርሱንም አሸንፎአቸዋል። ይህም መንፈሳዊ ሕይወታቸው ጠንካራና በድፍረት የተሞላ እንዳይሆን ያደርገዋል።

መጽሐፍ ቅዱስ ስለ ሰይጣን ብዙ ያስተምራል። አራት ዐበይት እውነቶችን ማስታወስ አለብን፡

ሀ. ሰይጣን ህልውናው የተረጋገጠ ኀይለኛ ጠላታችን ነው። የእግዚአብሔር መራራ ጠላት ሲሆን፥ ሰዎችን በራሱ የጨለማ መንግሥት ለማቆየት ወይም የእግዚአብሔር መንግሥት አካል የሆኑትን ወገኖች ውጤታማነት ለመቀነስ ተግቶ ይሠራል።

ለ. ኢየሱስ በሰይጣን ላይ ሙሉ ሥልጣንና ኀይል አለው። ሰይጣንና አጋንንት ኢየሱስ ማን እንደሆነ ስለሚያውቁ ይፈሩታል (ያዕ. 2፡19)። ይታዘዙታል። በአዲስ ኪዳን ውስጥ እንደተጻፈው ኢየሱስ ከሰይጣን ወይም ከአጋንንት ጋር ሲገናኝ፥ በአንዲት የትእዛዝ ቃል ያሸንፋቸው ነበር።

ሐ. ሰይጣን ተሸንፎአል። ኢየሱስ በመስቀል ላይ የኀጢአታችንን ዕዳ በመክፈል ሰይጣን የእግዚአብሔርን ልጆች ለመክሰስ የሚጠቀምበትን ሥልጣን አስወግዷል። በዚያም የፍጻሜያቸውን እርግጠኛነት በማሳየት ምርኮ ወስዷል (ቆላ. 2፡13-15)። በሰይጣን ላይ ዐቢዩን ድል ከተጎናጸፍን በኋላ፥ ሰይጣን የሽንፈት ጦርነት በሚያካሂድበት ዘመን ውስጥ እንኖራለን። ኢየሱስ በዳግም ምጽአቱ ሰይጣንና አጋንንቱን ወደ ሲኦል በመስደድ ሙሉ በሙሉ ያሸንፋቸዋል (ራእይ 20፡7-10)።

መ. ክርስቲያኖች “በክርስቶስ” ስለሆንን፥ ጥበቃውና ሥልጣኑ አይለየንም። መንፈሳዊ የጦር ዕቃዎቻችንን እስከ ለበስን ድረስ (አፌ. 6፡10-18 አንብብ)፥ የሰይጣንን ጥቃት መፍራት የለብንም። ሰይጣን አምልኳችንን እንዳይረብሽ ወይም በሕይወታችን ውስጥ ጣልቃ እንዳይገባ፥ እያሰርነው እንድንጸልይ የተሰጠ ትእዛዝ በአዲስ ኪዳን ውስጥ አይገኝም። ትኩረት የተሰጠው መንፈሳዊ የጦር ዕቃዎችን በመልበስ፥ ከሰይጣን ጥቃት የተጠበቅን መሆናችንን በማረጋገጡ ላይ ነው። በብቁ ሁኔታ የታጠቀ ሠራዊት የተሸነፈን ዓማፂ መፍራት የለበትም። እናም ሰይጣንን መፍራት የለብንም። በክርስቶስ ሥልጣን ሥር እስከ ተጠለልን ድረስ ሰይጣንን እናሸንፋለን። በራሳችን ኀይል ብንዋጋ ግን ምንጊዜም አናሸንፍም። “በኢየሱስ ስም” ከታገልነው በራሳችን ላይሆን፥ በክርስቶስ ኃይል እናሸንፋለን።

ይሁንና ብዙ ክርስቲያኖች በኢየሱስ ስም እየጸለዩ ሰይጣንን መዋጋት ማለት ምን ማለት እንደሆነ በትክክል አያውቁም። «በኢየሱሱሱሱስ. . . ስም» የሚሉት፥ ስሙን እየጠሩ የሚጮኹት፥ ወይም የኢየሱስን ስም ሦስት ጊዜ የሚጠሩት ለምንድን ነው? ይህ ሁሉ የመጣው መጽሐፍ ቅዱስ በኢየሱስ ስም ስላለን ሥልጣን የሚያስተምረውን ጠንቅቆ ካለማወቅ ነው። «በኢየሱስ ለም» መጸለይ ማለት ምን ማለት ነው? በመጀመሪያ፥ ኀይልን የምናገኘው በኢየሱስ ስም ብለን በመጮኻችን አይደለም። ስለሆነም «በኢየሱሱሉሱስ ስም» ማለቱም ሆነ መጮኹ ወይም ሦስት ጊዜ መደጋገሙ የሚጨምረው ነገር አይኖርም። ስለዚህ የኢየሱስን ስም እንደ ምትሐታዊ ቃል ከመጠቀም መጠንቀቅ አለብን። ይህን በማድረግ ክፉ መናፍስትን ለመቋቋም ክታቦችን ከሚያንጠለጥሉ ሰዎች ጋር እንዳንመሳሰል ልንጠነቀቅ ይገባል። ሁለተኛ፥ በራሳችን ኀይልና ሥልጣን እንደሌለን ለሰይጣን መናገራችን ነው። የጸሎታችንና የትእዛዛችን ሥልጣን ሁሉ የሚመጣው ከክርስቶስ ኀይል ነው። እኛ ያለን በውክልና የተሰጠን ኀይልና ሥልጣን ብቻ ነው። ስለዚህም፥ በኢየሱስ ክርስቶስ የምናምንና ሰይጣንን ለማሸነፍ፥ ከክርስቶስ ሥልጣን የተሰጠን ሰዎች በመሆናችን፥ ሰይጣንን እናዝዘዋለን። (ማስታወሻ፡- ይህ ጸሎታችንን “በኢየሱስ ስም” ብለን ከምንፈጽምበት ሁኔታ ጋር አንድ ዓይነት ፍች አለው። ይህን ስንል ወደ ሁሉን ቻይ አምላክ ለመምጣትና ከእርሱ ዘንድ መልስ ለመጠበቅ የቻልነው፥ ከክርስቶስ ጋር ባለን ግንኙነትና ወደ እግዚአብሔር እንድንመጣ በሰጠን ሥልጣን ምክንያት መሆኑን መግለጻችን ነው። ይህም በእግዚአብሔር ፊት የቀረብነው በራሳችን ጽድቅና የብቃት ስሜት እንዳልሆነ የምንገልጽበት ነው።)

የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) ሰዎች የኢየሱስን ስም ጮክ ብለው የሚጠሩት ወይም የሚደጋግሙት ለምንድን ነው? ለ) ከላይ ከቀረበው ትምህርት አንጻር፥ ጸሎታችን እንዴት ሊለወጥ ይገባል?

ኢየሱስ በሰይጣን ላይ ሙሉ ሥልጣን እንዳለው በግልጽ ከሚያሳዩት ነገሮች አንዱ፥ በጌርጌሴኖን አካባቢ በብዙ ክፉ መናፍስት የተያዘውን ግለሰብ ባዳነበት ሁኔታ ተገልጾአል። ቀደም ብለን እንደተመለከትነው፥ እነዚህ ክፉ መናፍስት ክርስቶስን ለይተው አውቀውታል። ስለዚህም፥ ኢየሱስ “የልዑል እግዚአብሔር ልጅ” እንደሆነ በግልጽ አውጀዋል። ይህም ኢየሱስ ራሱ አምላክ እንደሆነ የሚያመለክት ነበር። ኢየሱስ በእነርሱ ላይ ሙሉ ሥልጣን እንዳለውና እግዚአብሔር ለዘመናት የወጠነው ዕቅድ በሚፈጸምበት ጊዜ፥ ኢየሱስ ወደ ሥቃይ ስፍራ (ሲዖል) እንደሚልካቸው ያውቁ ነበር።

ይሁንና፥ የኢየሱስ ጎይል ከሰይጣን ጋር የሚነጻጸረው እንዴት ነው? ኢየሱስ ከሰይጣን የሚበልጠው ትንሽ ብቻ ነው? ማርቆስ የኢየሱስ ኀይል ፍጹማዊ እንደሆነና መጨረሻ በሌለው ሁኔታ ከሰይጣን ኀይል እንደሚለቅ አሳይቷል። በሮም ሠራዊት፥ አንድ ሌጌዎን (ጭፍራ) 6,000 ወታደሮችን ይይዛል። አጋንንት መንፈሳዊ ፍጥረታት ስለሆኑና አካላዊ ስፍራ ስለማይይዙ፥ በዚህ አንድ ግለሰብ ሰውነት ውስጥ 6,000 ክፉ መናፍስት ነበሩ። ነገር ግን ኢየሱስ ይህን የአጋንንት ሠራዊት ምን አደረገው? ፈራቸው? በፍጹም። አጋንንቱ እርሱን እንዳዩ በፍርሃት ተሸበሩ። ወደ ሥቃይ ስፍራ እንዳይልዳቸው ኢየሱስን ለመኑት። ቀላል ትእዛዙን ሰምተው ለመታዘዝ ተገደዱ። ክፋት በባሕርዩ ራሱ ያጠፋል። ይህንኑ ለማሳየት፥ ክፉ መናፍስት ወደ እሪያዎች ገብተው ገደሏቸው። ክፉ መናፍስቱ አልሞቱም ነበር። ነገር ግን የመኖሪያ ስፍራቸው ተወሰደባቸው።

በተጨማሪም፥ ማርቆስ ለዚህ የኢየሱስ ታላቅ ተግባር ሁለት የተለያዩ ምላሾችን ያነጻጽራል። አብዛኞቹ ሰዎች ለኢየሱስ ለመገዛትና እርሱን ለማክበር ስላልፈለጉ፥ ከአካባቢያቸው ለቅቆ እንዲሄድ ጠየቁት። በአጋንንት ተይዞ የነበረው ሰውዩ ግን ኢየሱስን ለመከተል ፈለገ። ኢየሱስ ግን ለዚህ ሰው የተሻለ አገልግሎት ሰጠው። ክርስቶስ ግለሰቡ ወደ ቤተሰቡ ተመልሶ እግዚአብሔር ስላደረገለት ምሕረት እንዲመሰክር ነገረው። ከደቀ መዛሙርት የሚጠበቀው ምንድን ነው? ማርቆስ ደቀ መዛሙርት ለሌሎች ስለ ክርስቶስ መመስከር እንዳለባቸው አመልክቷል። ነገር ግን የምስክርነታችን ዋና ነገር ምን መሆን አለበት? የተወሳሰበ ክርክር ወይም ሥነ መለኮታዊ እውነቶችን ማስተማር መሆን አለበት? አይደለም። ክርስቶስ ከሁሉም የሚበልጠውን ታላቅ ምስክርነት እኛን ለማዳን ያከናወነውንና አሁንም እኛን ለመርዳት እያከናወነ ያለውን ተግባር ለሌሎች ማካፈል እንደሆነ አሳይቷል። ብዙ ሰዎች ወደ ክርስቶስ የሚመለሱት ጥሩ በሚመስሉ ክርክሮች አማካኝነት ሳይሆን፥ በሚያውቋቸው ሰዎች ሕይወት ክርስቶስ የሚሠራውን በማየት ነው።

የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) በቅርቡ ኢየሱስ በሕይወትህ እየሠራ ያለው እንዴት ነው? ለ) ይህንን ለሦስት የማያምኑ ሰዎች አካፍልና ውጤቱን ለጥናት ቡድንህ ለማካፈል ተዘጋጅ።

(ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የአዲስ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)

Leave a Reply

%d bloggers like this: