ማርቆስ 7፡1-37

  1. ክርስቶስ ሰውን ስለሚያረክስ ነገር አስተማረ (ማር. 7፡1-23)

በማርቆስ ወንጌል ውስጥ ከቀረቡት ረዣዥም ታሪኮች አንዱ፥ ሰውን ስለሚያረከሱና ስለሚያነጹ ነገሮች የሚያስረዳው ነው። ይህ ቤተ ክርስቲያን ልትረዳው የሚገባት ጠቃሚ እውነት ነው። በቀድሞይቱ ቤተ ክርስቲያን ክርስቲያኖች ይጠይቋቸው ከነበሩት ዐበይት ጥያቄዎች አንዱ፥ «ሃይማኖታዊ ንጽሕናችንን ለማሳየት ልንጠብቃቸው የሚገቡ ትውፊቶች አሉ ወይ?» የሚል ነበር። ለብዙ ምእተ ዓመታት አይሁዶች የተወሰኑ ነገሮችን በማድረግ ውስጣዊ ሕይወትን በንጽሕና መጠበቅ እንደሚቻል ተምረው ነበር። ለምሳሌ፥ ንጽሕናን በተመለከተ አንዱ መንገድ የተወሰኑ የሥጋ ምግቦችን አለመመገብ ወይም ደሞ እጅን በተወሰነ መንገድ መታጠብ። ይህ ሥርዓት የእግዚአብሔር ፈቃድና ጠቃሚ መሆኑን ሲማሩ የነበሩት አይሁዶች፥ በክርስቶስ ባመኑበት ጊዜ፥ ክርስቲያኖችም ይህንኑ ማድረግ አለባቸው ብለው ያስቡ ነበር። አይሁዶች ብቻ ሳይሆኑ የአሕዛብ ክርስቲያኖችም እነዚህኑ ሥርዓቶች እንዲፈጽሙ ተነግሯቸዋል። ላይ ላዩን ሲታይ የተወሰኑ ምግቦችን መመገቡ ወይም እጅን መታጠቡ ብዙ ለውጥ ስለማያመጣ፥ ለአሕዛብ የአይሁድን የአኗኗር መንገዶች መከተሉ ከባድ አልነበረም። ነገር ግን በውስጡ አደገኛ የሆነ ትምህርት እንደነበረ ግልጽ ነው። ይህም የተወሰኑ ሃይማኖታዊ ሥርዓቶችን በምንፈጽምበት ጊዜ፥ እግዚአብሔር ደስ እንደሚሰኝብን፥ እንዲሁም ለእኛ የተስማማን ነገር ሁሉ ለሁሉም ሰዎች መልካም እንደሆነ አድርገን እንደምንገምት የሚያሳይ ነው። ስለሆነም፥ የኃጢአት ሥር የሚኖርበትን የልባችንን አመለካከት ትተን በሃይማኖታዊ ሥርዓት ላይ እናተኩራለን።

የሃይማኖት መሪዎች፥ ክርስቶስና ደቀ መዛሙርቱ በእግዚአብሔር ፊት ሰዎችን ንጹሕ ያደርጋሉ የሚሏቸውን አንዳንድ ሥርዓቶች አለመከተላቸውን በመግለጽ በወቀሱዋቸው ጊዜ፥ ክርስቶስ ሁለት ጠቃሚ ነገሮችን አስተማራቸው። በመጀመሪያ፥ በውጫዊ ልማዶችና ሥርዓቶች ላይ በማተኮር፥ ይበልጥ ጠቃሚ የሆነውን ነገር ላለማየት የመታወር አደጋ መኖሩን ገለጸ። ፈሪሳውያን እግዚአብሔርን በአፋቸው እያከበሩ፥ በሕግጋት ላይ ቢያተኩሩም፥ ልባቸው ወደ እግዚአብሔር ስለመቅረቡ ግድ የላቸውም ነበር፡፡ ሕግጋቱን በቀላሉ ወደሚፈጽሙበት አቅጣጫ ጠምዝዘዋቸው ነበር። ይህም እግዚአብሔር በሚፈልገው መንገድ እየኖርን ነው ብለው እንዲከራሩ አደረጋቸው። ብዙውን ጊዜ ግን እግዚአብሔር በማይፈልገው መንገድ ይመላለሱ ነበር። ስለዚህ አመለካከታቸው ከእግዚአብሔር ትእዛዛት «መንፈስ» የራቀ ነበር።

ሁለተኛ፣ ጌታችን የትኛውም ሰው ሠራሽ ውጫዊ ተግባር አንድን ሰው ንጹሕ ወይም ርኩስ ሊያደርግ እንደማይችል አስተማረ። መንፈሳዊ ንጽሕና ወይም ርኩሰት የሚመጣው ከልብ ነው። የሰው አመለካከቶች፥ አሳቦችና ፍላጎቶች የሚኖሩት በልብ ውስጥ ነው። ልብ የመልካም ነገሮች (እግዚአብሔርንና ባልንጀራን መውደድ) እና የመጥፎ ነገርች (ጥላቻ፥ ምኞት፥ ቁጣ) ምንጭ ነው። የክርስቶስ ተከታዮች በእነዚህ ነገሮች ላይ ማተኮር አለባቸው፡ ተግባራችን መልካምና እግዚአብሔርን የሚያስከብር ይሆን ዘንድ ከርኩስ ነገሮች መራቅ አለብን። እውነተኛ ሃይማኖት ሰዎች የሚያዩት ሳይሆን፥ በአማኙ ልብ ውስጥ ያለው ነው።

የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) ክርስቲያኖች ክርስቲያንነታቸውን የሚያሳዩባቸው፥ ጠቃሚና መልካም ተደርገው የሚወሰዱትን አንዳንድ ክርስቲያናዊ ልምምዶች ለምሳሌ፥ ዓይንን ጨፍኖ መጸለይ፥ በጌጣጌጥ አለመዋብ የመሰሉትን ዘርዝር። ለ) ክርስቶስ ባስተማረው መሠረት፥ ስለ እነዚህ ነገሮች ምን ዓይነት ግንዛቤ ሊኖርህ ይገባል?

ክርስቶስ ፈሪሳውያን ወይም ደቀ መዛሙርት እነዚህን ሰው ሠራሽ ልምምዶች እንዲያቆሙ አልተናገረም። ነገር ግን ስለ ደንቦች ትክክለኛ ጭብጥ ሊኖራቸው እንደሚገባ አስጠንቅቋቸዋል። ከጊዜ በኋላ ሁላችንም ትክክል ናቸው የምንላቸውን ውጫዊ ልምምዶች እናዳብራለን። ለምሳሌ፥ አልኮል አለመጠጣት ጥሩ ክርስቲያን መሆናችንን ያሳያል ብለን እናስባለን። (ማስታወሻ፡- በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ እንደ ኃጢአት የተጠቀሰው መስከር ብቻ ነው)። ዓይኖቻችንን ጨፍነንና እጆቻችንን አጣጥፈን መጸለይ እንዳለብን እናስባለን፤ ስንዘምርም ዓይኖቻችንን ጨፍነን ራሳችንን ወደ ሰማይ እናቀናለን። በዕልልታ ሃሌ ሉያ እያልን እንጮኻለን። እነዚህ ድርጊቶች ስሕተት ባይሆኑም፥ እንድናደርጋቸው እግዚአብሔር ያዘዘን አይደሉም። መንፈሳዊ ሕይወታችን ምን እንደሚመስል እነዚህ ነገሮች አያሳዩም። ጫማ ሳያወልቁም ሆነ፥ አውልቆ በቤተ ክርስቲያን ውስጥ ማምለክ ይቻላል። ዓይንን ጨፍኖ ወይም ሳይጨፍኑ መጸለይ ይቻላል። በዝማሬ ጊዜ ዓይንን መጨፈን ወይም አለመጨፈን እጅን ማንሳት ወይም ማውረድ፥ ማጨብጨብ ወይም አለማጨብጨብ ይቻላል። በአምልኮ ውስጥ እነዚህ ውጫዊ ተግባራት ትክክል ወይም ስሕተት የሚባሉ አይደሉም። ዋናው የልባችን ሁኔታ ነው።

  1. ታላቅ እምነት ያላት አሕዛብ (ማር 7፡24-30)

ክርስቶስ ጎሰኛ ነበር? የገዛ ወገኖቹ ለነበሩት ለአይሁዶች ብቻ ይጨነቅ ነበር? ወይስ ለአሕዛብም ያስብ ነበር? ለሮማውያን አንባቢዎች እነዚህ ጥያቄዎች አስፈላጊዎች ነበሩ። ስለሆነም፥ ማርቆስ ክርስቶስ ወደ ሶርያና ፊንቂ ተጉዞ አሕዛብ የነበረች ሴት እንዳገኘ አብራርቷል። ክርስቶስ በእግዚአብሔር ዕቅድ መሠረት አይሁዶችን በመጀመሪያ ለማገልገል መጠራቱን ተናግሯል። ስለዚህ በብሉይ ኪዳን ዘመን የእግዚአብሔር ልጆች የነበሩትን አይሁዶች መግቦ ገና አልረካም ነበር። እግዚአብሔር፥ ክርስቶስና ደቀ መዛሙርቱ ወደ አሕዛብ እንዲሄዱ ገና አላዘዛቸውም ነበር። ይህን ማለት ግን ክርስቶስ ስለ አሕዛቡ ሕዝብ አያስብም ማለት አይደለም። ሴቲቱ ክርስቶስ አጋንንትን ለማውጣት እንደሚችል በመግለጽ እምነቷን ስታሳይና እግዚአብሔር በረከቶቹን ለአሕዛብ የማዳረስ ባሕርይ እንዳለው ስታመለክት፥ ክርስቶስ ልጇን ፈወሰላት፡፡ የሚገርመው የእግዚአብሔር ልጆች የነበሩት አይሁዶች፥ “ውሾች” ናቸው ከሚሏቸው ከአሕዛብ ያነሰ እምነት ነበራቸው።

  1. ኢየሱስ በአጋንንት የተያዘ ደንቆሮና ዲዳ ሰው ፈወሰ (ማር. 7፡31-37)

የክርስቶስ ፈውስ በአንድ መንገድ ብቻ አልነበረም። አንዳንድ ጊዜ በቃሉ በመናገር፥ ሌላ ጊዜ በእጁ በመዳሰስ ሰዎችን ይፈውስ ነበር። በዚህ ስፍራ ክርስቶስ ሰውዬውን እንትፍ ብሎ በመዳሰስ ፈውሶታል። ይህም የደነቆሩትን ጆሮዎች ነካ፥ መናገር በተሳነው ምላስ ላይ እንትፍ አለ፥ ከዚያም በጸሎት ወደ ሰማይ ተመለከተ። እግዚአብሔር በተለያዩ መንገዶች ለጸሎት መልስ ስለሚሰጥ ሁልጊዜም አንድ ዓይነት ስልት ላይከተል ይችላል። ምሥጢሩና ኀይሉ የሚመጣው ከክርስቶስ ማንነት ነው። ሰዎች መንፈሳዊ ውጤት የሚያመጡት በተወሰነ መንገድ በመሄዳቸው፥ ወይም በመስበካቸው እንደሆነ በማሰብ እንዳንሳሳት መጠንቀቅ አለብን። ውጤቶችን የሚያመጣው የአሠራር መንገድ ሳይሆን፥ እዚአብሔር ራሱ የሚፈጽመው ተግባር ስለሆነ፥ እንዲህ ዓይነቱ አስተሳሰብ ከእውነት የራቀ ሊሆን ይችላል። እግዚአብሔር አህያን ለማናገር ከቻለ (ዘኁል. 22፡28) ማንንም ሰው ሊያናገር ወይም የፈለገውን መንገድ ለክብሩ ሊጠቀም ይችላል።

ሰዎችን ያስደነቀው የክርስቶስ መፈወስ ብቻ ሳይሆን፥ ሁሉንም በሚገባ መፈጸሙ ነበር። ነገሮችን የምናከናውንበት መንገድ ነገሮችን ከማከናወን እኩል አስፈላጊ ነው። ያለ መልካም ዝግጅት የይድረስ ይድረስ ተግባር ብናከናውን ድርጊቱ ግምት ላይ ይጥለናል። ይህን ብናደርግ ለእግዚአብሔር ክብር ሳናስብ የራሳችንን ፍላጎት የምንፈጽም መሆናችንን ያሳያል። ዓለምን የፈጠረውና ሁሉም «መልካም ነው» ያለው እግዚአብሔር፥ ሁሉንም ነገር በጥንቃቄ እንድናከናውን ይፈልጋል። ከሥራ ላለመባረር፥ በትምህርት ቤት ከክፍል ወደ ክፍል ለማለፍ ወይም መንፈሳዊ ለመምሰል ላይ ላዩን ከመጣር ይልቅ፥ ፍሬ ያለው ሥራ ከልባችን ለመሥራት መትጋት አለብን፡፡

የውይይት ጥያቄ ሀ) በግማሽ ልብ የተሠሩ ነገሮች በከፍተኛ ጥንቃቄ ከተሠሩት እንዴት ይነጻጸራሉ? ይህ ምን ልዩነት ያስከትላል? ) ሥራችን ባሕርያችንንና ከእግዚአብሔር ጋር ያለንን ግንኙነት የሚያሳየው እንዴት ነው? ሐ) ይህ ትምህርት የማስተማርንና የስብከት አገልግሎታችንን እንዴት ሊለውጠው ይገባል?

(ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የአዲስ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)

Leave a Reply

Discover more from

Subscribe now to keep reading and get access to the full archive.

Continue reading