1. ኢየሱስ ስለ ጋብቻና ፍች አስተማረ (ማር. 10፡1-12)።
ፈሪሳውያን ክርስቶስን ለመፈተን በመፈለግ ስለ ፍች ጠየቁት። በዚህ ጊዜ እርሱም በፍች ላይ ያለውን የእግዚአብሔርን አመለካከት ገልጾላቸዋል። ፍች ሁልጊዜም የኀጢአትና በእግዚአብሔር ዓላማ ላይ የማመፅ ምልክት ነው። እግዚአብሔር ጋብቻን የወጠነው ባልና ሚስት በጣም በመቀራረብ በአሳብና በተግባር እንዲጣመሩ ነው። ፍችን ማበረታታት በእግዚአብሔር ፍላጎት ላይ ማመፅ ነው። ፍች የሚፈቀድበት ብቸኛው ጊዜ ግንኙነቱ በዝሙት የተበላሸ እንደሆነ ብቻ ነበር። ከተፋታ ሰው ጋር መጋባቱም በዝሙት ከመኖር እኩል ነው።
በምዕራቡ ዓለም፥ ክርስቲያኖች በእነዚህ ጥብቅ የጋብቻ ትእዛዝ ላይ ዓምፀዋል። ከዚህም የተነሣ፥ ፍች የዓለማውያንን ያህል በዝቷል። ይህ የክርስቶስ ትምህርት ሁሉንም ሁኔታዎች ላያካትት ይችላል። ለምሳሌ፥ አካላዊ ጥቃት በሚኖርበት ጊዜ ምን ማድረግ ይገባል?) ለተጨማሪ የፍች ሁኔታ 1ኛ ቆሮ.7፡15ን ይመልከቱ።) ነገር ግን ይህን ትምህርት በከፍተኛ አክብሮት መቀበል አለብን። ችግሮቹ ምንም ያህል ከባድ ቢሆኑም፥ በመንፈስ ቅዱስ እገዛ ክርስቲያኖች ሁሉንም አሸንፈው በአንድነት ሊኖሩ ይችላሉ።
ነገር ግን እግዚአብሔር ለጋብቻ የወጠነውን ፍጹማዊ ዕቅድ የምናፈርስበት ሌላ መንገድ አለ። ወንጌላውያንን ጨምሮ ብዙ ሰዎች ከትዳር ጓደኞቻቸው ተለይተው ለወራት ይቀመጣሉ። ብዙውን ጊዜ ባልና ሚስት በብዙ ኪሎ ሜትሮች ተራርቀው በተለያዩ ከተሞች ውስጥ ይቀመጣሉ። ስሦስት ወር ወይም በዓመት አንድ ጊዜ ይገናኛሉ። ይሄ እግዚአብሔር ያጣመረውን የምንለይበት ሌላው መንገድ አይሆንም? የእግዚአብሔር ፍላጎት የባልና ሚስት አብሮ መኖር ከሆነ፥ ከዚያ ውጭ የሆነው ሁሉ ኃጢአት አይደለምን? ተጨማሪ ገንዘብ ለማግኘት በምናደርገው ጥረት ቤተሰባችንን መለያየቱ የእግዚአብሔር ፈቃድ እንደሆነ እርግጠኞች ነን? ወይስ የገንዘብ ፍቅር እግዚአብሔርን ወደማናስከብርበት አቅጣጫ እየመራን ይሆን? የቤተሰብና የአካባቢ ሁኔታ ወንጌላውያንን ከሚስቶቻቸው ቢለያቸው፥ ቤተሰባቸውን ክርስቶስን ከመታዘዝ አላስበለጡም ወይ? ቤተሰብ የቤተ ክርስቲያን እጅግ ጠቃሚ ክፍል ከሆነ፥ አነስተኛ ገቢና ተጨማሪ ችግሮች ቢገጥሙንም እንኳ ቤተሰብን ልንንከባከብ ይገባል።
የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) ሰዎች በባልና ሚስት መካከል ሰለሚኖረው ግንኙነትና ስለ ጋብቻ ያላቸው የተሳሳቱ አመለካከቶች፥ እግዚአብሔር ለአእምር፥ ለልብና ለዓላማ አንድነት ያለውን ፍላጎት ሲያበላሹ የተመለከትህበትን ሁኔታ በምሳሌነት ጥቀስ። ለ) ብዙ ክርስቲያኖች በሥራ ምክንያት ከትዳራቸው ሲርቁ የተመለከትህበትን ሁኔታ አብራራ። ይህ በቤተ ክርስቲያንና በቤተሰብ ላይ ያስከተላቸው አሉታዊ ውጤቶች ምንድን ናቸው?
2. የእግዚአብሔር መንግሥት የተገነባችው እንደ ልጆች ባሉ ሰዎች ነው (ማር. 10፡13-16)።
ክርስቶስ ብዙ ጊዜ ደቀ መዛሙርቱን ባይቆጣም፥ አንዳንድ ጊዜ ግን ይህንኑ ሲያደርግ እንመለከታለን። ከእነዚህ ጥቂት ጊዜያት አንዱ፥ ልጆች አስቸጋሪዎች እንጂ በእግዚአብሔር ዓይኖች ብርቅ መሆናቸውን ያላጤኑት ደቀ መዛሙርት፥ ወደ ክርስቶስ እንዳይቀርቡ በተከላከሉበት ጊዜ የሰነዘረው ቁጣ ነበር። ክርስቶስ ቀን ለደቀ መዛሙርቱ ልጆች የእግዚአብሔር መንግሥት ሕይወት አርአያዎች እንደሆኑ ነገራቸው። ልጆች በወላጆቻቸው ላይ በፍጹም ልባቸው እንደሚተማመኑ ሁሉ፥ የእግዚአብሔርም ልጆች በፍጹም ልባቸው ሊተማመኑበት ይገባል።
3. ደቀ መዝሙርነት ማለት ኢየሱስን ከምንም ነገር በላይ መውደድ ማለት ነው (ማር. 10፡17-31)።
ክርስቶስ ግብረገባዊ ሕይወት ይመራ ለነበረው ሀብታም ወጣት ሹም፥ ደቀ መዝሙሩ ለመሆን ከፈለገ ገንዘቡን ሁሉ ለድሆች መስጠት እንዳለበት ሲናገር፥ ሹሙ ወደ ኋላ ተመለሰ። ለዓለም ነገሮች፥ በተለይም ለገንዘብ የነበረው ፍቅር ሁሉንም ነገር ትቶ ክርስቶስን የበለጠ መውደዱን እንዳያሳይ አገደው።
ደኅንነትና ክርስቶስን መከተል ቀላል አይደለም። እሑድ ቀን እጅን አንሥቶ ክርስቶስን እከተላለሁ ማለቱ ብቻ አይበቃም። ክርስቶስን መከተል ሕይወትን መስጠት ነው። ክርስቶስ በሕይወታችን ቀዳሚውን ስፍራ ሊይዝና ለክርስቶስ ያለንን ፍቅር የሚያደናቅፍ ነገር ሁሉ ሊወገድ ይገባል። ለዚህ ሰው መሰናክል የሆነው ገንዘብ ሲሆን፥ ለሌሎች ደግሞ ትምህርት ወይም የቤተሰብ ፍቅር ሊሆን ይችላል። ክርስቶስ ይህ ሰዎች በተፈጥሯዊ ብርታታቸው የሚያደርጉት ሳይሆን፥ በእግዚአብሔር ኀይል ለክርስቶስ ብለው ሁሉንም ነገር የሚተዉበት እንደሆነ ያውቅ ነበር። ነገር ግን አንድ ሰው ሁሉንም ነገር ለክርስቶስ በሚሰጥበት ጊዜ የበለጠ ዋጋ ያገኛል። በዓለም ፊት ቀዳሚውን ስፍራ ሊይዙ የሚፈልጉ ሀብታሞችና ዝነኞች፥ በዘላለሙ መንግሥት የመጨረሻውን ስፍራ ሲያገኙ ክርስቶስን በመከተላቸው ምክንያት ዓለም የናቀቻቸው በእግዚአብሔር መንግሥት ቀዳሚ ይሆናሉ።
4. ኢየሱስ እንደገና ስለ ሞቱ ተነበየ (ማር. 10፡32-34)።
ክርስቶስ የሚሞትበት ጊዜ እየቀረበ ሲመጣ፥ ስለ ሞቱ በበለጠ መናገሩን ቀጠል። ክርስቶስ ስለዚሁ ጉዳይ ለአራተኛ ጊዜ ሲተነብይ፥ ሞቶ እንደሚነሣ ተናግሯል። ክርስቶስ ከስደት ለመሸሽ ያልፈለገው፥ ይህ በግልጽ የእግዚአብሔር ፈቃድ ስለነበር ነው። ተከታዮቹም ተመሳሳይ አመለካከት ይኖራቸው ነበር።
5. መሪነት በኢየሱስ መንግሥት (ማር. 10፡35-45)
ክርስቶስ ወደ ምድር የመጣው ለምንድን ነው? በማርቆስ 10፡45 የተሰጠው ግልጽ ምሳሌ እንደሚያስረዳው ክርስቶስ የመጣው «ሰዎች እንዲያገለግሉት ሳይሆን፥ ሰዎችን ለማገልገልና ሕይወቱን ለብዙዎች ቤዛ አድርጎ ለመስጠት ነበር»። ክርስቶስ የመጣው ሌሎችን እንጂ ራሱን ለማገልገል አልነበረም። የመሥዋዕቱ ጥልቀት ሰዎችን ከኀጢአታቸው ነፃ ለማውጣት መሞቱን ያረጋግጣል።
ይሁንና፥ ክርስቶስ ጠቃሚ ትምህርት ለማስተማር ወደ ምድር መምጣቱን የሚያሳይ ግልጽ ብያኔ ሰጥቷል። ያዕቆብና ዮሐንስ በክርስቶስ መንግሥት ውስጥ ሹመት ለማግኘት ፈልገው ነበር። ይህ የሌሎችንም ደቀ መዛሙርት ፍላጎት ያንጸባርቅ ስለነበር፥ የእነዮሐንስ አነጋገር ሌሎቹን አስቆጣቸው። ክርስቶስ ተከታዮቹ በተለይም መሪዎች ከዓለማውያን የተለየ የአመራር አመለካከት ሊኖራቸው እንደሚገባ ተናግሯል። አመራር ራስን ለማገልገል፥ ክብርን፥ ሥልጣንንና ኀይልን ለማግኘት ተብሎ የሚገባበት ሳይሆን፥ ሌሎችን ለማገልገል የራስን ሕይወት የሚጠይቅ ነው። ማርቆስ፥ መሪዎች ሲባሉ የሌሎች ሰዎች «አገልጋዮች» እንደሚሆኑ ገልጾአል። ሌሎችን ከማገልገል ውጭ የሆነው ምክንያት ከዓለም የሚመጣ በመሆኑ፥ የእግዚአብሔርን ሕዝብ ክርስቶስ በሚፈልገው መንገድ ከመምራት ይልቅ፥ ወደ ጥፋት የሚያደርስ ይሆናል። ክርስቶስ ደቀ መዛሙርቱን ለመምራት ሕይወቱን ስለ ሰጠ፥ እኛም ለሌሎች ይህንኑ ልናደርግ ይገባል።
6. ኢየሱስ ዓይነ ስውሩን በርጤሜዎስ ፈወሰ (ማር 10፡46-52)
ክርስቶስ ሌሎችን ካገለገለባቸው ምሳሌዎች መካከል፥ ለመሞት ወደ ኢየሩሳሌም በሚሄድበት ጊዜ የለማኙን ጩኸት ሰምቶ የፈወሰበት አንዱ ነው።
(ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የአዲስ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)