ማርቆስ 9፡1-50

  1. ኢየሱስ ሰማያዊ ክብሩን ገለጸ (ማር. 9፡1-3)።

ኢየሱስ ከደቀ መዛሙርቱ አንዳንዶቹ ከመሞታቸው በፊት ክብሩን እንደሚያዩ ከተናገረ በኋላ፥ ጴጥሮስን፥ ዮሐንስንና ያዕቆብን ይዞ ወደ ተራራ ወጣ። በዚያም መለኮታዊ ክብሩን ገለጸ። በዚያም ሕግን የወከለው ሙሴና ነቢያትን የወከለው ኤልያስ ቀርበው ከኢየሱስ ጋር ተነጋገሩ። ለሁለተኛ ጊዜ ደቀ መዛሙርቱ ኢየሱስ እግዚአብሔር የሚወደው ልዩ ልጁ እንደሆነ ሰሙ። ሦስቱ ደቀ መዛሙርት ምን ያህል እንደ ተደሰቱ አስቡ። ወዲያው ግን ኢየሱስ አምላክ ቢሆንም እንኳ፥ መከራን እንደሚቀበልና በሕዝቡ ዘንድ ተቀባይነትን እንደሚያጣ በመግለጽ ደቀ መዛሙርቱን አስደነገጠ። ያዩትን ሁሉ ለሌሎች አለመናገሩ ሳይከብዳቸው አልቀረም።

  1. ኢየሱስ ከአንድ ልጅ አጋንንትን አስወጣ (ማር. 9፡14-32)።

ደቀ መዛሙርቱ ከተራራው ሲወርዱም እንደገና ደነገጡ። ከልጁ አጋንንት ለማውጣት ባለመቻላቸው ወደ ተራራው ያልመጡት ደቀ መዛሙርት፥ ተጨንቀውና አፍረው ቆመው ነበር፡፡ ቀደም ሲል ክርስቶስ ለአገልግሎት በላካቸው ጊዜ ያከናወኑት አጋንንትን የማስወጣት ተግባር፥ ለምን እንደ ተሳናቸው ሊገባቸው አልቻለም ነበር።

ክርስቶስ ይህንን ጊዜ ለደቀ መዛሙርቱ ስለ እምነት ለማስተማር ተጠቀመበት፡፡ በመጀመሪያ፡ ለልጁ አባት፥ ለሚያምን ሁሉም እንደሚቻል ገለጸለት (ማር. 9፡23)። ስለ እምነት ልናስታውሳቸው የሚገቡን ሁለት ነገሮች አሉ። ታላላቅ ነገሮችን የሚሠራው ራሱ እምነታችን ሳይሆን፥ የምናምንበት አካል ነው። ስለሆነም በጣዖታት ላይ ከፍተኛ እምነት ያለው ሰው ታላላቅ ነገሮችን ሊያሳካ አይችልም። ነገር ግን በታላቁ አምላክ ላይ አነስተኛ እምነት ያለው ሰው እግዚአብሔር ታላላቅ ተአምራትን ሲሠራ ሊመለከት ይችላል። በተገላቢጦሹ እምነት በማይኖርበት ጊዜ ወይም ሰዎች ለማመን ሳይፈልጉ ሊቀሩ፣ እግዚአብሔር ተአምራትን ለመሥራት አለመቻሉ ሳይሆን፥ ነገር ግን ሰዎች እርሱን ወይም ችሉታውን በሚጠራጠሩበት ጊዜ ለመሥራት አለመምረጡ ነው።

ሁለተኛ፣ ክርስቶስ በእግዚአብሔር ዕቅድ ውስጥ ሥራዎችን ለማከናወን በእምነት መጽናት አስፈላጊ የሚሆንበት ጊዜ እንዳለ ተናግሯል። ደቀ መዛሙርቱን ያጋጠቸው ችግር ክርስቶስ በተአምር ለመፈወስ ኃይልን ማጣቱ አልነበረም። ክርስቶስ በአንድ የትእዛዝ ቃል ነበር አጋንንቱን ሁሉ ያስወጣው። ተግቶ የማይሠራ ሰው ጠንካራ ጡንቻ ሊኖረው አይችልም። በተመሳሳይ ሁኔታ በጸሎት ጽኑ ትግል የማያደርግና በጾም በእግዚአብሔር ላይ ጥገኛ መሆኑን የማያሳይ ክርስቲያን መንፈሳዊ ጡንቻ ሊኖረው አይችልም፡፡ ስለሆነም፥ እግዚአብሔር ቀደም ሲል እኛን ለመርዳት ቢሠራም እንኳ፥ ጥያቄዎቻችንን በፍጥነት የማይመልስባቸው ጊዜያት አሉ። እምነታችንን የሚፈታተን ሁኔታ ሁሉ አዲስ ሁኔታ ነው። በቀድሞው ስኬት ወይም ብርታት ላይ ሳንመሠረት፥ እንደገና በእግዚአብሔር ላይ ጥገኝነታችንን ማኖር አለብን።

የውይይት ጥያቄ- ሀ) ብዙውን ጊዜ አንድ ነገር ከተሳካልን በኋላ፥ በእግዚአብሔር ላይ መደገፋችንን የምናቋርጠው እንዴት ነው? ለ) እግዚአብሔር ለጸሎትህ ፈጣን ምላሽ ባለመስጠቱ ምክንያት መንፈሳዊ ብርታትህ የጨመረባቸውን መንገዶች የሚያሳዩ ምሳሌያችን ስጥ።

ማርቆስ ክርስቶስ ለሦስተኛ ጊዜ ስለ መጭው ሞቱ፥ ቀብሩና ትንሣኤው መግለጹን ዘግቧል።

  1. ኢየሱስ በመንግሥቱ ውስጥ አመራር ምን እንደሚመስል አስተማረ (ማር. 9፡33-50)

የተሳሳቱ አመለካከቶችን ማስወገዱ ቀላል አይደለም። እጅግ ከተሳሳቱ እመለካከቶች አንዱ ሥልጣንና የመሪነት ስፍራ ለማግኘት የሚደረግ ጥረት ነው። በዓለም ሁሉ ያለው ባሕል በራስ ጥቅም ላይ ያተኩራል። ሰዎች መሪ ከሚሆኑባቸው ዋንኛ ምክንያቶች አንዱ ሥልጣን፥ ሀብትና ኀይል ለማግኘት ነው። ይህ አመለካከት ካልተወገደ በስተቀር ቤተ ክርስቲያንን እግዚአብሔር በሚፈልገው መንገድ መምራት አይቻልም። ይህ የኀይልና የክብር ፍላጎት ደቀ መዛሙርቱን ይፈታተናቸው ስለ ነበር፥ ክርስቶስ የመንግሥቱ አመራር በአምስት መንገዶች እንደሚለይ አስተምሯል።

ሀ. በክርስቶስ መንግሥት አመራር ከዓለም የተለየ ነው። ታላቅነት የሚለካው አንድ መሪ ራሱን ዝቅ አድርጎ ከራስ ወዳድነት በጠራ መንፈስ ሌሎችን ለማገልገል በመቻሉ ነው፡፡ እንደ ትልልቅ ሰዎች በችሎታችንና በታላቅነታችን ከመመካት ይልቅ፥ እንደ ልጆች በእግዚአብሔር አብ ላይ ጥገኞች ልንሆን ይገባል።

ለ. በክርስቶስ መንግሥት አመራር የሚያከብረው ታላላቆች ናቸው የተባሉትን ሳይሆን፥ ዝቅተኛ ግምት የሚሰጣቸውን ሰዎች ነው። ጠቃሚዎች ናቸው የምንላቸውን ሰዎች (ሀብታሞች፥ ነጋዴዎች፥ ምሁራን) እየወደድን፥ ጠቃሚዎች አይደሉም የምንላቸውን ሰዎች (ልጆች፥ ሴቶች፥ ድሆች፥ መሃይማንን) እንንቃለን። በክርስቶስ መንግሥት ለዓለም የማይጠቅሙ የሚመስሉ ሰዎች አስፈላጊዎች ናቸው።

ሐ የእግዚአብሔር መሪዎች ሌሎች ስኬታማ ሲሆኑና እግዚአብሔር ባልተጠበቁ መንገዶች ሲሠራ በሚመለከቱበት ጊዜ አይቀኑም። አሥራ ሁለቱ ደቀ መዛሙርት ሌላ አማኝ ክርስቶስን ሳያስፈቅድ አጋንንት ሊያወጣ በማየታቸው ቀንተው ክርስቶስ እንዲከለክለው ነገሩት። ክርስቶስ ግን የአመራር ሚና ሰዎችን ማበረታታት እንጂ መቆጣጠር እንዳልሆነ አስተማራቸው። ለእግዚአብሔር ክብርን የሚያመጣ ማንኛውም ነገር በሚከሰትበት ጊዜ መደሰት አለብን። ይህ የግድ «በእኛ» መሪዎች ወይም በምንጠብቃቸው ሰዎች መከናወን የለበትም። ምክንያቱም ለክርስቶስ ክብር የሚሠራ ሰው፥ ወዲያውኑ ተመልሶ የክርስቶስ ጠላት ሊሆን ስለማይችል ነው።

መ. አገልግሎት የሚለካው በምናከናውናቸው ተግባራት ታላቅነት ሳይሆን፥ በታማኝነትና በጥሩ አመለካከት በማገልገላችን ነው። የግድ ታላላቅ ሰባኪያን ወይም አስተማሪዎች መሆን የለብንም። የባሪያን በሚመስል አመለካከት የተሰጠ አንድ ኩባያ ቀዝቃዛ ውኃ ዋጋ አለው።

ሠ. መሪዎችና በሌሎች ላይ ኃላፊነት ያላቸው ሰዎች፥ (ለምሳሌ፥ ወላጆች) በተግባራቸውና በአመለካከታቸው ትንንሽ ልጆችንና የቤተ ክርስቲያን ምእመናንን ወደ ኀጢአት እንዳይገፉ መጠንቀቅ አለባቸው። ክርስቶስ ሌሎችን በኀጢአት ለማሰናከል የተጋነነ ቋንቋ በመጠቀም አንድን ሰው ከማሰናከል ይልቅ፥ የግል አካላዊ ጉዳትን መቀበል እንደሚሻል ተናግሯል። ሌሎችን የሚያሰናክሉ ሰዎች እውነተኛ የክርስቶስ ደቀ ዛሙርት ባለመሆናቸው፥ ከፍተኛ ቅጣት ይደርስባቸዋል። ተግባሮቻችንና አመለካከቶቻችን እንደ ብርሃን እያንጸባረቁ ሰዎችን ወደ ክርስቶስ መምራት ይኖርባቸዋል። መንፈሳዊ ባሕርይን በመላበስ (በነፍሳችሁ ጨው ይኑርባችሁ)፥ እርስ በርሳችን በሰላም እንኖራለን።

የውይይት ጥያቄ፦ ሀ) ክርስቶስ ስለ መሪነት ያስተማረውን በቤተ ክርስቲያን ውስጥ ካለው ሁኔታ ጋር እነጻጽር፡፡ ለ) አመራርን ይበልጥ ክርስቶስ ባየበት ዓይን ለመመመልከት፥ ከተግባራችንና ከእመለካከታችን ሊለወጡ የሚገባቸው ነገሮች ምን ምንድን ናቸው?

(ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የአዲስ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)

 

Leave a Reply

Discover more from

Subscribe now to keep reading and get access to the full archive.

Continue reading