- ኢየሱስ እንደ ሰላም ንጉሥ ወደ ኢየሩሳሌም በድል ገባ (ማር.11፡1-11)።
አሁን ማርቆስ የክርስቶስን ታሪክ የሚናገርበት መንገድ ተቀይሯል። በፊት ማርቆስ የጊዜ ቅደም ተከተልን ጠቅሶ የዕለት ተዕለት ሁኔታዎችን ካስረዳ በኋላ፥ «ወዲያውኑ» በሚሉ ዓይነት ቃላት ታሪኩን በፍጥነት ይተርክ ነበር፡ አሁን ማርቆስ የዕለት ተዕለት ክስተቶችን ይዘረዝራል። አሁን ቀስበቀስ የታሪኩን ፍጻሜ (የክርስቶስን ሞትና ትንሣኤ) ይገልጻል። በተለይም በስቅለት ዕለት ማርቆስ ክስተቶችን ከሰዓት ሰዓት እየዘረዘረ የታሪኩን ፍጥነት ዝግ አድርጎታል። በማርቆስ ወንጌል ውስጥ የተገለጹትን የነገሮች ቅደም ተከተል ከዚህ በታች ይመልከቱ፡
ሀ. እሑድ፡- ኢየሱስ በድል ወደ ኢየሩሳሌም ገባ (ማር 11፡1-11)።
ለ. ሰኞ፡- ኢየሱስ በለሷን ረገመ ቤተ መቅደሱን አነጻ (ማር 11፡12-19)።
ሐ. ማክሰኞ፡- ከሃይማኖት መሪዎች ጋር ተጋፈጠ፥ የተለያዩ ትምህርቶችን ሰጠ (ማር 11፡20-13-37)።
መ. ረቡዕ፡- ኢየሱስ ሽቶ ተቀባ፥ ይሁዳ አሳልፎ ሊሰጠው ተስማማ (ማር. 14፡1-11)።
ሠ. ሐሙስ፡- ቅዱስ ቁርባንና የኢየሱስ መያዝ (ማር. 14፡12-72)።
ረ ዓረብ፦ ኢየሱስ በጲላጦስ ተመረመረ፥ ተሰቀለ፥ ሞተ፥ ተቀበረ (ማር. 15)።
ሰ. ቅዳሜ፦ ኢየሱስ ተቀበረ።
ሸ. እሑድ፡- ኢየሱስ ከመቃብር ተነሣ (ማር. 16፡1-8)።
ሮማውያን ትልቅ ጦርነት ካሸነፉ በኋላ፥ ለጦር ጄኔራሎቻቸው ከፍተኛ የአቀባበል ሥነ ሥርዓት የማዘጋጀት ባሕል ነበራቸው። የሮም ጄኔራል በትልቅ ፈረስ ላይ ተቀምጦ ፊት ፊት ሲሄድ፥ ወታደሮች ከኋላ ይከተሉታል። ምርኮኞችና ባሮች ደግሞ ከወታደሮቹ ኋላ ይከተላሉ። ክርስቶስ በድልነሺነቱ በሁሉም መንገድ የተለየ ነበር። ክርስቶስ የተቀመጠው በተናቀ የአህያ ውርንጭላ ላይ ሲሆን፥ ሰዎችም እርሱን ሳይሆን እግዚአብሔርን እያመሰኑ ይዘምሩ ነበር። ነገር ግን በዚህ ጊዜም ቢሆን አይሁዶች ስለ ንጉሣቸው የተሳሳተ አሳብ ይዘው ነበር፤ እርሱ የመጣው የዳዊትን መንግሥት ለመጀመር ሳይሆን ለመሞት ነበርና።
- ኢየሱስ ነጋዴዎችን ከቤተ መቅደስ አስወጣ (ማር. 11፡12-19)።
ክርስቶስ ወደ ቤተ መቅደሱ በደረሰ ጊዜ ወዲያውኑ በቁጣ ተሞላ። ሰዎች የአምልኮን ስፍራ ለሌላ ዓላማ ሲጠቀሙ በመመልከቱ፥ በአሕዛብ አደባባይ (አሕዛብ የሚያመልኩበት) እንስሳትን ይሸጡ የነበሩትን ነጋዴዎች አባረረ። ክርስቶስ ለምን ተቆጣ? ማቴዎስ የነጋዴዎችን ሌላ ምክንያት ጠቁሟል። በአሕዛብ አደባባይ ውስጥ መገበያየቱ አሕዛብን ከአምልኮ ማደናቀፍ ነበር። ኢሳይያስ 56፡7 አሕዛብ ከአይሁዶች ጎን እግዚአብሔርን ሊያመልኩ እንደሚችሉ ቢገልጽም አይሁዶች ግን ለአሕዛብ በነበራቸው ጥላቻ ምክንያት ወደ እግዚአብሔር እንዳይቀርቡ እየከለከሏቸው ነበር። ማርቆስ የሃይማኖት መሪዎች ክርስቶስን ለመግደል ከፈለጉባቸው ምክንያቶች አንዱ ይሄ እንደሆነ ገልጾአል።
የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) ክርስቲያኖች ኃጢአትን ሳይፈጽሙ ሊቆጡ የሚችሉባቸው አንዳንድ መንገዶች ምን ምንድን ናቸው? ለ) ብዙውን ጊዜ ክርስቲያኖች የሚቆጡባቸው ነገሮች ምንድን ናቸው? ሐ) ብዙውን ጊዜ የእኛ ቁጣ ከክርስቶስ ቁጣ የሚለየው እንዴት ነው?
- ኢየሱስ የበለስን ዛፍ ረገመ (ማር. 11፡12-14፥ 20-26)።
ቀደም ባለው ቀን ክርስቶስ ፍሬ ያላት የምትመስል (ነገር ግን የሌላታን) የበለስ ዛፍ አይቶ ነበር። ይህችን በለስ በፍርድ ረገማት። በቀጣዩ ዕለት ወደ ኢየሩሳሌም በሚሄዱበት ጊዜ በለሲቱ ጠውልጋ በማየታቸው ደቀ መዛሙርቱ ተደነቁ። ክርስቶስ ይህንን የእምነት ትምህርት አድርጎ ተጠቅሟል። እግዚአብሔር ታላቅ አምላክ ስለሆነ፥ የሚነግረን ነገር ሁሉ ይፈጸማል። እንደ ተራራ የገዘፉ የሚመስሉ ነገሮች ሳይቀር በጸሎታችን ተግባራዊ ይሆናል። እምነት እንደ መክፈቻ ቁልፍ ነች። ቁልፉ በሚዘጋበት ጊዜ የእዚአብሔር ኃይል ወደ ሕይወታችን ሊፈስ አይችልም። እምነት በሚኖርበት ጊዜ ግን ቁልፉ ክፍት ስለሆነ፥ የእግዚአብሔር ኃይል በነጻነት እየፈሰሰ ተአምራትን ያደርጋል። ይህም አይሁዶች እግዚአብሔር የሚፈልግባቸውን የጽድቅ ፍሬ ባለማፍራታቸው ምክንያት ፍርድ እንደሚመጣባቸው የሚያሳይ ስውር ታሪክ ነበር።
(ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የአዲስ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)