- ኢየሱስ ለደቀ መዛሙርቱ ስለ እውነተኛ አሰጣጥ አስተማረ (ማር. 12፡41-44)።
በተፈጥሯዊ መንገድ የአንድን ለጦታ ታላቅነት ከምንለካባቸው መንገዶች አንዱ የስጦታውን መጠን መመልከት ነው። አንድ መቶ ብር ወይም ከዚያ የበለጠ ገንዘብ የሚከፍሉትን ሰዎች እያደነቅን፥ ዐሥር ሣንቲም ብቻ የሚሰጡትን ቸል እንላለን። ብዙ የሚሰጡትን እያከበርን፥ ጥቂት ብቻ የሚሰጡንን እንንቃለን። ክርስቶስ ግን እግዚአብሔር አንድን ስጦታ የሚለካው፥ ሰጭውን ምን ያህል እንደሚጎዳው በማገናዘብ መሆኑን ገልጾአል። ዐሥር ብር ብቻ ያላት ድሀ ሴት አምስት ብር በምትሰጥበት ጊዜ፥ አሥር ሺህ ብር ኖሮት አንድ መቶ ብር ከሚሰጠው ነጋዴ የበለጠ ሰጥታለች ማለት ነው። በተማሩትና በሀብታሞች ተማርከን፥ እግዚአብሔር ሰዎችን የሚመለከትበትን ሁኔታ እንዳንረሳ መጠንቀቅ አለብን።
የውይይት ጥያቀ:- ብዙ ገንዘብ የሚሰጡትን፥ የተማሩና ሀብታሞች የሚመስሉትን እያከበርን፥ ትንሽ ገንዘብ ብቻ የሚሰጡትን ድሆችና ያልተማሩ ሰዎች ቸል ልንል የምንችለው እንዴት ነው?
- ኢየሱስ ለደቀ መዛሙርቱ ስለ ዳግም ምጽአቱ ምልክቶች ነገራቸው (ማር. 13)።
የክርስቶስን ምጽአት የሚያሳዩ ምልክቶችና፥ ክርስቲያኖችም እንዴት ለምጽአቱ መዘጋጀት እንዳለባቸው ብዙ ማብራሪያ ከሰጠው ማቴዎስ በተቃራኒ፥ ማርቆስ በምልክቶች ላይ ብቻ ትኩረት አድርጓል። ከእነዚህ ምልክቶች አብዛኛዎቹ በማቴዎስ 24 ውስጥ ስለ ተጠቀሱ፥ በዚህ ክፍል ዝርዝራቸውን ከማቅረብ የበለጠ ተግባር አናከናውንም።
ሀ. ብዙ ሐሰተኛ መሲሖች ለሕዝቡ ችግሮች መፍትሔ እንደሚያመጡ ምርጥ የእግዚአብሔር መሪዎች አድርገው ራሳቸውን ያቀርባሉ። አንዳንዶች “ክርስቶስ” ተብለው በመጠራት ተአምራት ይሠራሉ።
ለ. ጦርነቶችና የጦርነት ወሬዎች ይሰማል።
ሐ. እንደ መሬት መንቀጥቀጥና ረሃብ ያሉ የተፈጥሮ አደጋዎች ይከሰታሉ፡፡
መ. በክርስቲያኖች ላይ ታላላቅ የስደት ጊዜያት ይደርሳሉ። የክርስቶስ ተከታዮች በአይሁድ ምኩራቦች)፥ እና በአሕዛብ (መንግሥታትና ነገሥታት) ፊት ቀርበው ለእምነታቸው መልስ ለመስጠት ይገደዳሉ። በዚህ ጊዜ ለመሪዎቹ ምላሽ ለመስጠት ከመፍራት ይልቅ፥ መንፈስ ቅዱስ የሚናገሩትን ቃል እንደሚሰጣቸው መተማመን ይኖርባቸዋል። እነዚህን ዕድሎች በመጠቀም ለመሪዎች መመስከር አለብን።
ሠ. ወንጌሉ በዓለም ሁሉ ለሁሉም የጎሳ ቡድኖች ይሰበካል።
ረ. ይህ ወንጌል በቤተሰቦች መካከል ከፍተኛ መለያየትን ስለሚያስከትል፥ የክርስቶስ ተከታዮች ይጠላሉ፤ ይሰደዳሉ። በዚህን ጊዜ ግን እኛ ለክርስቶስ ታማኞች ሆነን መጽናት አለብን።
ሰ. የጥፋት ርኩሰት ይከሰታል። (ማስታወሻ፡- ይህ ኢየሩሳሌም በሮማውያን መደምሰሷን ወይም በመጨረሻው ዘመን የሚከሰተውን ሌላ ድርጊት ስለ ማመልከቱ እርግጠኞች አይደለንም። ምናልባትም ሁለቱንም ያመለክት ይሆናል።) ዓለም ከዚህ በፊት አይታ የማታውቀው ከፍተኛና ፈጣን ጥፋት ይመጣል።
ሸ. ፀሐይን፥ ጨረቃንና ከዋክብቶችን የሚያጠቃ የህዋ አካላት ወይም ኮስሚክ (cosmic) ውድመት ይመጣል። (ይህ እግዚአብሔር በዓለም ላይ አስከፊ ፍርድ የሚያመጣበትን ሁኔታ የሚያሳይ የተለመደ አገላለጽ ነው። ኢሳ. 13፡10፥ ኢዩ 2፡10፥ 31፤ አሞጽ 8፡9)።
ቀ. ነገሮች እጅግ በሚከፉበት ሰዓት፥ ክርስቶስ ከመላእክቱ ጋር በመምጣት ልጆቹን (ምርጦቹን) ወደ ዘላለማዊ ፍርድ ከሚሄዱት ይለያቸዋል።
በ. ምንም እንኳ እነዚህ ምልክቶች የክርስቶስን ምጽአት ቢያሳዩም፡ (የበለስ ዛፍ የዓመቱን ወራት እንደምታሳይ ሁሉ)፥ ትክክለኛውን ቀን ወይም ዓመት ለይቶ ማወቅ አይቻልም።
ኀ. የክርስቶስ ተከታዮች የሆንን ሰዎች ምጽአቱን እየተጠባበቅን፥ በታማኝነት መመላለስ አለብን፡፡ ከተሰጡት ምልክቶች ሁሉ ባሻገር፥ ክርስቶስ ባልተጠበቀ ሰዓት ይመጣል። ክርስቶስ ቶሎ አይመጣም ብለን በመንፈሳዊ ሕይወታችን ሳንሰንፍ፥ ክርስቶስ ዛሬ ሊመጣ እንደሚችል በማሰብ ሕይወታችንን ማጥራት አለብን።
የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) ክርስቶስ ነገ እንደሚመጣ ብታውቅ ኖሮ ምን ታደርግ ነበር? ለ) እነዚህን ነገሮች አሁን የማታደርገው ለምንድን ነው?
(ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የአዲስ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)