ማርቆስ ስለ ክርስቶስ ትንሣኤ ያቀረበው ዘገባ ከሁሉም ወንጌላት አጠር ያለ ነው። ይህም በተለይ ብዙ ምሑራን እንደሚሉት፥ ምዕራፍ 16 ቁጥር 8 ላይ የሚያበቃ ከሆነ እውነት ነው ማለት ይቻላል። የክርስቶስን መቀበር የተመለከቱት ሦስት ሴቶች ወደ መቃብሩ ተመለሱ። በዚህ ጊዜ የተመለከቷቸው መላእክት ክርስቶስ ከሞት እንደ ተነሣና ወደ ገሊላ እንደ ሄደ ነገሯቸው። ደቀ መዛሙርቱ በዚያ ከእርሱ ጋር ተገኝተዋል።
ማርቆስ ወንጌሉን የፈጸመው በሴቶቹ ፍርሃትና ግራ መጋባት ነው። ለምን እንዲህ መጽሐፉን ድንገት ጨረሰው? አንዳንድ ምሑራን ማርቆስ መጽሐፉን ቁጥር 8 ላይ የጨረሰው አንባቢያኑ ስለ ትንሣኤ እንዲያስቡ ለማድረግ እንደሆነ ያስባሉ። ክርስቲያኖች ከሞት የተነሣውን ክርስቶስን ማምለካቸው፥ ደቀ መዛሙርቱ ወደ ገሊላ ሄደው ከክርስቶስ ጋር እንደ ተገናኙ ያረጋግጣል። በዚህ ጊዜ ሕይወታቸው ሙሉ በሙሉ ተለወጠ። ቤተ ክርስቲያን የተመሠረተችው በዚያ ነበር። ሰዎች በክርስቶስ የሕይወት ታሪክ ግራ ተጋብተው ለመኖር ወይም በክርስቶስ አምነው ግራ መጋባታችውን ለማስወገድ ምርጫ ነበራቸው።
ሌሎች ምሑራን የማርቆስ የመጀመሪያው መደምደሚያ እንደ ጠፋ ያለባሉ። ለዚህም ነው የቀድሞዎቹ ጸሐፊዎች አብዛኞቹ የማርቆስ ወንጌል የመጀመሪያ ቅጂ እካል አይደለም የሚሉትን ማርቆስ 16፡9-20 ላለመጨመር የተገደዱት፡፡
ማርቆስ 16፡9-20 በሌሎች ወንጌላትና የሐዋርያት ሥራ ውስጥ የሚገኙትን አንዳንድ ታሪኮች ጠቅለል አድርጎ ያቀርባል። የማቴዎስ ወንጌል ጋር በመስማማት፥ መግደላዊት ማርያም መጀመሪያ ክርስቶስን ያገኘችው እንደ ነበረች ያስረዳል። እንደ ሉቃስ፥ ሁለት ሰዎች በኤማሁስ መንገድ ከክርስቶስ ጋር እንደ ተገናኙ ያስረዳል። እንደ ዮሐንስ፡ ክርስቶስ ከአሥራ አንዱ ጋር እንደ ተገናኘና አንዳንዶች እንደ ቶማስ እንደተጠራጠሩት ይገልጻል።
ስለ ታላቁ ተልእኮ የሚናገረውም የማርቆስ ምንባብ በሌሎች ወንጌላት ውስጥ የተጠቀሱት እውነቶች ውህደት ይመስላል። ክርስቶስ ደቀ መዛሙርቱ በዓለም ሁሉ ወንጌልን እንዲሰብኩ አዝዟቸዋል። በክርስቶስ ያመኑ ደኅንነትን ሲያገኙ፥ ለማመን ያልፈለጉት ግን ተፈርዶባቸዋል።
ጸሐፊው በተጨማሪም ወንጌሉ በሚስፋፋበት ጊዜ ተአምራት (ምልክቶች) እንደሚታዩ ገልጾአል። (ማስታወሻ፡- ይህ እያንዳንዱ ክርስቲያን ይህንን ሁሉ እንደሚያደርግ ሳይሆን፥ ምልክቶቹ በቤተ ክርስቲያን ውስጥ እንደሚፈጸሙ የሚያሳይ መሆኑን አስተውል።)
ሀ. በክርስቶስ ስም አጋንንትን ማስወጣት
ሊ በአዲስ ልሳናት መናገር
ሐ እባቦችን መያዝ። (ምናልባትም ይህ ጳውሎስ እባብን ከያዘበት ታሪክ የተወሰደ ይሆናል። የሐዋ. 28፡)
መ መርዝ ጠጥቶ አለመሞት። ይህንን በተመለከተ በአዲስ ኪዳን ውስጥ ምንም መረጃ የለም።
ሠ. በበሽተኞች ላይ እጅ በመጫን መፈወስ።
በእነዚህ ጥቅሶች ላይ ብቻ ተመርኩዘን እምነታችንን እንዳንመሠርት መጠንቀቅ አለብን። ከእነዚህ ነገሮች ውስጥ አብዛኞቹ በቀድሞዪቱ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ የተፈጸሙ ሲሆን፥ ዛሬም እንኳ እየተፈጸሙ ነው። ነገር ግን ይህ ጥቅስ በራሱ ሁሉም ክርስቲያኖች በልሳን ይናገራሉ ብሎ ለማስተማር ጥቅም ላይ መዋል የለበትም፡፡ እባብን ስለመያዝና መርዝ ለለመጠጣት የቀረበው ትምህርት በሌላ ቦታ ስላልተደገመ፥ ክርስቲያኖች መንፈሳዊነታቸውን ለማሳየት መርዛማ እባቦችን እንዲይዙ ወይም መርዛማ መጠጥ እንዲጠጡ ማበረታታት ጥበብ የጎደለው ድርጊት ነው። በአገልግሎታቸው እነዚህን ድርጊቶች የሚፈጽሙ ጥቂት ክርስቲያኖች አሉ፡ ከዚህም የተነሣ ብዙ ሰዎች ይሞታሉ።
ጸሐፊው ሌሎች የአዲስ ኪዳን ትምህርቶችንም እንደ ማጠቃለያ አድርጎ ያቀርባል። ኢየሱስ ወደ ሰማይ ባረገ ጊዜ፥ በእግዚአብሔር አብ ቀኝ ወዳለ ከፍ ያለ የክብርና የሥልጣን ስፍራ ሄደ። የሐዋርያት ሥራ መጽሐፍ እንደሚያሳየው፥ ሐዋርያት የኢየሱስን ታሪክ ለሌሎች ነገሩ፥ የኢየሱስንም አገልግሎት በሽተኞችን በመፈወስ፥ አጋንንትን በማውጣት፥ ወዘተ… ቀጠሉ።
(ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የአዲስ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)
Thanks bless u
Thank u for your honers blessed