ሉቃስ 16፡16-31

  1. ኢየሱስ በብሉይ ኪዳንና በፈሪሳያውን መካከል ስላለው ግንኙነት ያቀረበው ትምህርት (ሉቃስ 16፡16-18)

እዚህ ላይ ሉቃስ ኢየሱስ በተለያዩ ጊዜያት ያስተማራቸውን እውነቶች ጠቅለል አድርጎ የሚያቀርብ ይመስላል። አጠር ብለው ከመቅረባቸው የተነሣ አንዳንዶቹን ለመረዳት አስቸጋሪ ነው።

ሀ. ከሙሴ ዘመን ጀምሮ እስከ መጥምቁ ዮሐንስ ድረስ አይሁዶች ዘወትር ብሉይ ኪዳንን ሲማሩ ቆይተዋል። አሁን ኢየሱስ በመካከላቸው ተገኝቶ የእግዚአብሔርን መንግሥት የምሥራች እየነገራቸው ነበር። ነገር ግን ለመጥምቁ ዮሐንስም ሆነ ለኢየሱስ የተሰጡ ሁለት የተለያዩ ምላሾች ነበሩ። ፈሪሳውያን ብሉይ ኪዳንን እየታዘዝን ነው ብለው ቢያስቡም ይህንኑ እያደረጉ አልነበረም። (ለኢየሱስ ምን ዐይነት አመለካከት እንደ ነበራቸው በሉቃስ 16፡14 ላይ አንብብ።) መጥምቁ ዮሐንስም ሆነ ኢየሱስ ስለ እግዚአብሔር መንግሥት ያስተማሩትን መልካም የምሥራች ለመቀበል አልፈለጉም። ስለሆነም የእግዚአብሔርን በረከት ሊቀበሉ አልቻሉም። በሌላ በኩል ደግሞ ተራ አይሁዶችና የተናቁ ኃጢአተኞች የእግዚአብሔር መንግሥት አካል ለመሆን ይሽቀዳደሙ ነበር። እነዚህ ሰዎች በእግዚአብሔር መንግሥት ላይ ስላተኮሩ፣ የዮሐንስንም ሆነ የኢየሱስን ትምህርቶች ሰምተው ለመታዘዝ ከፍተኛ ጥረት ያደርጉ ነበር።

ለ. ምንም እንኳ ፈሪሳውያን ኢየሱስ የብሉይ ኪዳን ሕግ እንዳልጠበቀ በመግለጽ ቢከሱትም፣ እርሱ ግን ሕጉን እየጠበቀ ነበር። በኢየሱስ ምክንያት ከእግዚአብሔር ሕግ ውስጥ የሚፋቅ አንድም ሕግ የለም። አዲሱ ኪዳን አሮጌውን የብሉይ ኪዳን ሕግ ይፈጽመዋል እንጂ አይሽረውም።

ሐ. ፈሪሳውያን የብሉይ ኪዳን ሕግን እንዳላከበሩና ኢየሱስ ግን ይህንን ሕግ እንደፈጸመ ከምናስተውልበት መንገድ ውስጥ አንዱ በፍች ጉዳይ ላይ የቀረበው ትምህርት ነው። ፈሪሳውያኑ በሕጉ ዙሪያ ሰበብ በመፈለግ ፍችን ቀላል ለማድረግ ይጥሩ ነበር። ነገር ግን የእግዚአብሔርን ሕግ ለመፈጸም የፈለገው ኢየሱስ ፍችና ዳግም ጋብቻ በእግዚአብሔር ፊት ዝሙት መሆኑን በመግለጽ ተቃውሟል።

  1. የሀብታሙ ሰውዬና የአልዓዛር ታሪክ (ሉቃስ 16፡19-31)

ብዙውን ጊዜ ሕይወት በምድር ላይ ችግር የበዛበት ናት። ከእግዚአብሔር ልጆች አንዱ ለማኝ ሊሆንና ከሰይጣን ልጆች አንዱ ሀብታም ሊሆን ይችላል። ነገር ግን ከዚህ የሚበልጠው በዘላለማዊ መንግሥት የሚሆነው ነገር ነው። በዚያ ድሀ የነበረው የእግዚአብሔር ልጅ ሲያልፍለት፣ ሀብታም የነበረው የሰይጣን ልጅ የሥቃይ ሰው ይሆናል። በዚህ የሀብታሙ ሰውና የአልዓዛር ታሪክ፣ ኢየሱስ አይሁዶች አሁን የእግዚአብሔርን ቃል እንዲሰሙ ያስጠነቅቃቸዋል። ከሞት በኋላ ንስሐ ገብተው ሕይወታቸውን የሚለውጡበትን ዕድል አያገኙምና። ሉቃስ በተጨማሪም ስለ ገንዘብ ያለን አመለካከት መንፈሳዊ ሕይወታችን ምን እንደሚመስል ጥሩ አመልካች እንደሆነ እየገለጸ ነበር። በገንዘብ ጉዳይ ላይ ምሕረትን አለማሳየትና ንፉግ መሆን የእግዚአብሔር ተከታዮች አለመሆናችንን ያመለክታል።

የመጽሐፍ ቅዱስ ምሁራን ይህ ምሳሌ ነው ወይስ እውነተኛ ታሪክ በሚለው አሳብ ላይ ይከራከራሉ። ታሪኩ ምላሌ ከሆነ፣ ኢየሱስ የባለታሪኮቹን ስም ስለጠቀሰ ምሳሌ ነው ለማለት የሚቻል አይመስልም። ስለሆነም፣ ብዙ ምሑራን ታሪኩ እውነተኛ እንደሆነና ከሞት በኋላ የሚሆነውን የሚያውቀው ኢየሱስ በሀብታሙ ሰውና በድሀው ላይ የደረሰውን ያውቅ እንደነበር ይስማማሉ። (ይህ ኢየሱስ ከሞት ያስነሣው የማርያምና ማርታ ወንድም ታሪክ እንዳልሆነ አስተውል።) ይህ ምሳሌ ይሁን እውነተኛ ታሪክ በትክክል ስለማናውቅ፣ ከሞት በኋላ ስለሚሆነው ነገር እንደ ማብራሪያ ከመጠቀም መጠንቀቅ አለብን።

ኢየሱስ የሁለቱን ሰዎች ሕይወት አነጻጽሯል። አንደኛው ሀብታም ሲሆን፣ በአለባበሱ (ሐምራዊና የተልባ እግር በጥንቱ ዘመን በአብዛኛው ነገሥታት የሚለብሱት እጅግ ውድ ልብስ ነበር)፥ በአኗኗሩና በገንዘቡ ይደሰት ነበር። ይህ ሰው ገንዘቡን ሁሉ የሚጠቀመው ለራሱ ነበር። ሌላኛው ደግሞ ምንም የሌለውና ከውሾች በቀር ሰው የማይቀርበው ምስኪን ነበር። ሁለቱም ሰዎች ሞቱ። በዚህ ጊዜ ስፍራቸውን ተለዋወጡ። አልዓዛር ለጻድቃን ወደ ተዘጋጀውና «የአብርሃም እቅፍ» ወደሚባለው ስፍራ ተወሰደ። ሀብታሙ ሰውዩ ግን ለኃጢአተኞች ወደ ተዘጋጀውና ሲኦል በመባል ወደሚታወቀው ስፍራ ተወሰደ። ስለ አብርሃም እቅፍ የተነገረ ብዙ ነገር ባይኖርም፣ የበረከት ስፍራ እንደሆነ እናምናለን። ሲኦል ግን የእሳትና የሥቃይ ስፍራ እንደሆነ ተገልጾአል።

ሀብታሙ ሰውዬ አብርሃምና አልዓዛር የደስታ ሕይወት ሲኖሩ ቢመለከተም፥ ወደዚያ ግን መሄድ አይችልም ነበር። ስለሆነም አልዓዛር መጥቶ የተቃጠለ ምላሱን በውኃ ያረጥብለት ዘንድ አብርሃምን ለመነ፡፡ ነገር ግን አሁን መከራ የመቀበል ተራው እንደ ደረሰና ከሞት በኋላ ሰዎች ከአንዱ ወገን ወደ ሌላው ሊዛወሩ እንደማይችሉ ተገለጸለት። በዚህ ጊዜ ሰውዬው አልዓዛር ወደ ወንድሞቹ ተልኮ የሲኦልን አስከፊነት እንዲነግራቸውና ሕይወታቸውን ለውጠው ወደ ሲኦል ከመውረድ እንዲተርፉ እንዲያደርግ ለመነ አብርሃም ግን ይህንኑ እውነት ከብሉይ ኪዳን ሊማሩ እንደሚችሉና ይህንን ለማድረግ ካልፈቀዱ የአልዓዛር መሄድ ለውጥ እንደማያመጣ ተናገረ።

ከዚህ ታሪክ ምን ያህሉን ለመተርጎም እንደምንችል ለመገንዘብ አስቸጋሪ ቢሆንም፣ የሚከተሉትን እውነቶች መረዳቱ ተገቢ ይመስላል።

ሀ. ድሀ መሆን አንድን ሰው ወደ መንግሥተ ሰማይ እንደማያስገባው፣ ሀብታም መሆን ደግሞ አንድን ሰው ወደ ሲኦል እንደማያወርደው ከመጽሐፍ ቅዱስ እንገነዘባለን። መንግሥተ ሰማይ መግባትን አስመልክቶ፣ የአንድ ሰው ኢኮኖሚያዊ ሁኔታ የመንፈሳዊ ሕይወቱን ያህል አስፈላጊ አይደለም። ነገር ግን ሕይወታችን፣ በተለይም የገንዘብ አጠቃቀማችንና ለድሆች ምሕረትን ማሳየታችን ጥሩ የመንፈሳዊ ሕይወት ምልክት ነው።

ለ. ከሞትን በኋላ እምነታችንንና ተግባራችንን ልንለውጥ አንችልም። ዘላለማዊ ሁኔታችን ተወስኖ አልቋል። ከሞት በኋላ የምንሄድበትን የሚወስነው ዛሬ በሕይወት ሳለን የእግዚአብሔርን ቃል እውነት ከሕይወታችን ጋር ማዛመዳችን ነው።

ሐ. ሙታን ሁሉ የሚሄዱበት ሁለት ዐበይት ስፍራዎች አሉ። ከእነዚህ መካከል አንደኛው የበረከትና የክብር ስፍራ ሲሆን፣ ሌላኛው የቅጣትና የሥቃይ ስፍራ ነው። ሕይወት ከሞት በኋላ ምን እንደሚመስል ለመገንዘብ ይህን ምሳሌ ምን ያህል መጠቀም እንዳለብን አናውቅም። ወይም ደግሞ ምሳሌው የአዲስ ኪዳንን ሳይሆን የብሉይ ኪዳንን ዘመን ሁኔታ ብቻ የሚያመለክት እንደሆነም ግልጽ አይደለም። አንዳንድ ሰዎች ይህ ከኢየሱስ ሞትና ትንሣኤ በፊት የነበረውን የብሉይ ኪዳን ሁኔታ እንደሚያመለክት ይናገራሉ። በአንድ ሰፊ የሙታን ስፍራ ሁለት ክፍሎች ነበሩ። ከእነዚህም መካከል አንዱ የጻድቃን ነፍስ መኖሪያ ሲሆን፣ ሌላው ደግሞ የኃጢአተኞች ነፍስ መኖሪያ ነው። እነዚህ ሰዎች እንደሚያስቡት፣ ከኢየሱስ ትንሣኤ በኋላ የጻድቃን ነፍስ ወደ መንግሥተ ሰማይ ተወስደዋል። ለዚህም ነው ጳውሎስ ከሥጋ ውጭ መሆን ማለት ከኢየሱስ ጋር በሰማይ መሆን ማለት ነው የሚለው ሲሉ ያስተምራሉ (2ኛ ቆሮ. 5፡6-9)። የዕብራውያን ጸሐፊ የጻድቃን ነፍሳት ስላሉበት ሰማይ ጽፎአል (ዕብ 12፡22-24)። በመጨረሻው ዘመን የጻድቃን ነፍስ ሥጋ ከመቃብር የሚነሡ ሲሆን፣ አዲሱ አካላቸው ከነፍሳቸው ጋር ተዋሕዶ ለዘላለም በእግዚአብሔር መንግሥት ደስ ይሰኛሉ። የኃጢአተኞችም ነፍስ ተነሥተው ከነፍሳቸው ጋር በመዋሐድ ለዘላለም የእግዚአብሔርን ፍርድ ይቀበላሉ (ራእይ 20፡11-15)።

መ. ታሪኩ አይሁዶች ለማመን አለመፈለጋቸውን በጽኑ የሚያመለክት ይመስላል። ፈሪሳውያን እንደ ሀብታሙ ሰውዬ ነበሩ። እነዚህ ሰዎች ብሉይ ኪዳንን ለመረዳትና ለመታዘዝ ፈቃደኞች አልነበሩም። ኢየሱስ ቀደም ብሎ አንድ ሰው ከሞት አስነሥቷል። ከዚህ በኋላም አልዓዛር የተባለ ሌላ ሰው ከሞት ያስነሣ ነበር። ከዚያም ራሱ ኢየሱስ ከሞት ይነሣል። ነገር ግን ከእነዚህ ክስተቶች አንዱም የአብዛኞቹን አይሁዶች ልብ ሊለውጥና በኢየሱስ እንዲያምኑ ሊያደርግ አልቻለም።

የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) የሀብታሙ ሰውዬ ዕጣ እንዳይገጥመን፥ ሕይወታችንን እንድንመረምር ይህ ታሪክ ጠንካራ ማስጠንቀቂያ የሚሰጠን እንዴት ነው? ለ) የገንዘብ አያያዛችንና ድሆችን የምናስተናግድበት መንገድ መንፈሳዊ ሁኔታችንን ደህና አድርገው የሚያሳዩት እንዴት ነው? ሐ) በእነዚህ ሁለት ጉዳዮች ዙሪያ ሕይወትህን መርምር። በእነዚህ ሁለት ጉዳዮች ላይ ለኢየሱስ ክርስቶስ ትታዘዝ እንደሆነ መንፈስ ቅዱስ እንዲያሳይህ ጠይቅ።

(ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የአዲስ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)

Leave a Reply

Discover more from

Subscribe now to keep reading and get access to the full archive.

Continue reading