- ማርያም ኢየሱስን ሽቶ ቀባችው (ዮሐ. 12፡1-11)
ኢየሱስ የሚሞትበት ጊዜ ደርሷል፤ የቀረው ስድስት ቀናት ብቻ ነው። ክርስቶስ ቢታንያ በሚገኘው የማርያም፥ የማርታና የአልዓዛር ቤት ተቀምጧል። ይህ ቤተሰብ ለክርስቶስ ያለው ፍቅር ጥልቅ በመሆኑ፥ ለክብሩ ትልቅ ግብዣ አዘጋጁለት። ሦስቱ የቤተሰቡ አባላት ፍቅራቸውን ለክርስቶስ ገለጹ። ምናልባትም ታላቅ እኅታቸው የነበረችው ማርታ ክርስቶስን ታስተናግድ ነበር። አልዓዛር ከክርስቶስ ጋር በማዕድ ተቀምጦ ይበላ ነበር። ማርያም የክርስቶስን እግር በውድ ሽቶ ትቀባ ነበር። የምታደርገው ነገር ሁሉ ለየት ያለ ነበር። ምንም ዓይነት የራስ ወዳድነት ስሜት ሳይታይባት ውድ ንብረቷን ሰጠችው። በሰው ፊት ጸጉሯን ፈትታ ለቀቀችው፤ ይህም የተከበሩ የአይሁድ ሴቶች የማያደርጉት ነገር ነው። ከዚያም እንደ አገልጋይ እግሩን አጠበች። (እግር ማጠብ የአገልጋዮች ተግባር ነበር።) ምናልባት ሽቶውን ያስቀመጠችው ለጋብቻዋ ቀን ይሆናል። ነገር ግን ለሌሎች ላናስብ ለእግዚአብሔር ያለንን የተለየ ፍቅር የምንገልጽበት ጊዜ ሊኖር ይገባል። ማርያም ፍቅሯን የገለጻችው በዚህ መንገድ ነበር።
ሌሎቹ ወንጌላት በሌሎቹ ደቀ መዛሙርት ምላሾች ላይ ሲያተኩሩ፥ ዮሐንስ ግን በይሁዳ ላይ አተኩሯል። ይሁዳ የኢየሱስንና የቡድኑን ገንዘብ የሚይዝ ሰው እንደ ነበር ዮሐንስ ገልጾአል። ነገር ግን ሁልጊዜ ከሚይዘው ገንዘብ እየሰረቀ ይወስድ ነበር። ገንዘቡን የፈለገው ለራሱ እንጂ ለድሆች አልነበረም። ይሁዳ ክርስቶስን አሳልፎ የሰጠው በድንገት አይደለም። ነገር ግን የገንዘብ ፍቅር በልቡ ውስጥ እንዲያድግ አድርጎ ነበር። ይህ የኃጢአት አረም በልቡ ውስጥ አደገ። ምንም እንኳ ክርስቶስ ስለ ገንዘብ ያስተማረውን ቢሰማም፥ ክርስቶስም ያደረጋቸውን ተአምራት ቢያይም፥ ይህ ኃጢአት በልቡ ውስጥ የሚያድገውን ክፋት እንዳያይ አሳወረው። በገንዘብ ረገድ ሰይጣን በሕይወቱ ውስጥ ስፍራ እንዲያገኝ ካደረገ፥ ሰይጣን በይሁዳ ሕይወት ውስጥ የፈለገውን ነገር ለመፈጸም ቀላል ይሆንለታል።
ይህ በሁላችንም ሕይወት ውስጥ እውነት ነው። ብዙ ጊዜ የሚያስቸግሩን ታላላቅ ኃጢአቶች አይደሉም። ትናንሽ የምንላቸው ኃጢአቶች ናቸው፥ ከምጽዋት የምትወሰደው ትንሿ ገንዘብና ትንሿ የዓይን አምሮት በጊዜ ካልተቀጩ፥ ሰይጣን ሕይወትህን ሊቆጣጠርና የኋላ ኋላም ሊያጠፋህ ይችላል።
ማንም ሰው ድንገት ዝሙት አይፈጽምም። የሚጀምረው በዚህ አሳብ ከተያዘ ሕሊና ነው። ግድያና ሌብነትም የሚጀምሩት ከክፉ ሃሳብና ቅናትና ምኞት ነው። አወዳደቃችን የይሁዳን ያህል የከፋ ላይሆን ይችላል፤ የማይታረሙ ትናንሽ ኃጢአቶች ወደ ትልቁ ያመራሉ፤ ይህም ሕይወታችንን፥ ምስክርነታችንን፥ ቤተሰባችንንና የኢየሱስን ስም የሚያጎድፍ ይሆናል።
የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) ስለ ትልልቅ ኃጢአቶች ብቻ ሳይሆን ስለ ትንንሾቹም ማሰብ እንዳለብን ይህ ትምህርት የሚያስጠነቅቀን እንዴት ነው? ለ) አንዳንድ ጊዜ አሳሳቢ አይደሉም ብለህ የናቅሃቸውን ኃጢአቶች በምሳሌነት ጥቀስ። እነዚህ ኃጢአቶች አድገው ሕይወትህን ሊገዙ የሚችሉት እንዴት ነው? ሐ) አሁን ጊዜ ወስደህ ሕይወትህን በጸሎት መርምር። መንፈስ ቅዱስ እንደ አረም ወደ ሕይወትህ ሊዘልቁና ሊያጠፉህ ብቅ የሚሉትን ትናንሽ ኃጢአቶች እንዲያሳይህ ተማጠነው። በሕይወትህ ስለምታያቸው ኃጢአቶች ንስሐ ግባ። ከዚያም በክርስቶስ አማካይነት ስላገኘኸው ድል እግዚአብሔርን አመስግን።
- ኢየሱስ ወደ ኢየሩሳሌም በድል ገባ (ዮሐ 12፡12-19)
ሐዋርያው ዮሐንስ ክርስቶስ በ”ሆሳዕና” ዝማሬ ታጅቦ ወደ ኢየሩሳሌም ሲገባ፥ ታሪኩን በገለጸበት በዚህ ክፍል የተለያዩ ቡድኖች በሰጡት ምላሾች ላይ ትኩረት አድርጓል። ክርስቶስ ኢየሱስ በአህያ ውርንጭላ ላይ ተቀምጦ ወደ ኢየሩሳሌም መግባቱ ምን ትርጉም እንዳለው ሕዝቡ ባይገነዘብም፥ በሁኔታው ግን ደስ ሳይሰኙ አይቀሩም። በወቅቱ ለኢየሱስ በተደረገው ታላቅ አቀባበል የተደነቁት ደቀ መዛሙርትም እስከ ትንሣኤው ድረስ ክርስቶስ የአይሁድ የሰላም ንጉሥ ሆኖ መምጣቱን አልተገነዘቡም ነበር። ለሌሎች ክርስቶስ ተአምራትን በማድረግና በማስተማር አስደናቂ ትእይንት እንደሚያሳይ ሰው ነበር። የሃይማኖት መሪዎች ደግሞ የተከታዮቹን ብዛት ሲመለከቱ ይበልጥ ቀኑበት።
(ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የአዲስ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)