ኢየሱስ የእግዚአብሔር ልጅ ስለመሆኑ ከአይሁድ መሪዎች ጋር ተከራከረ (ዮሐ. 10፡22-42)

ከብዙ ጊዜ በኋላ የመታደስ በዓል ሲከበር ክርስቶስ አሁንም በቤተ መቅደስ ተገኝቶ ነበር። ይህ የመታደስ በዓል የሚከበረው በታኅሣሥ 165 ዓ.ዓ ሲሆን፥ በአንቲኮስ ኤጲፋነስ የረከሰውን ቤተ መቅደስ ይሁጻ መቃብያን መልሶ አደሰው። በዓሉ አይሁዶች ለመጨረሻ ጊዜ የተቀዳጁትን ድል ያመለከታል።

ክርስቶስ በሃይማኖት መሪዎች ለሚመሩ አይሁዶች መሢሕነቱን ደጋግሞ ገልጾአል። የፈጸማቸው ተአምሮችና «ምልክቶች» መሢሕ መሆኑን ይመሰክራሉ። ይሁንና አይሁዶች እስከ አሁን ድረስ በመሢሕነቱ አያምኑም። ምክንያቱም ኢየሱስ አይሁድ ይጠብቁት የነበረው ፖለቲካዊ መሪ ስላልነበረ ነው። ከሁለት መቶ ዓመታት በፊት አይሁዶችን ነፃ እንዳወጣው እንደ ይሁዳ መቃብያን አልነበረም። ክርስቶስ እነርሱን ደስ ለማሰኘት ተጨማሪ ተአምራትን ለማድረግ አልፈለገም። ቀደም ሲል ብዙ ምልክቶችን ሰጥቷቸዋል፤ ስለሆነም አይሁዶች አሁን ከውሳኔ ላይ መድረስ አለባቸው። ስለዚህ ኢየሱስ ለማያምኑት አይሁድ የሚከተለውን ተናገረ፡-

ሀ. ቀደም ሲል መሢሕ መሆኑንና ያደረጋቸውም ተአምራት ይህንኑ እንደሚያረጋግጡ ነገራቸው።

ለ. ጉዳዩ የተአምራት ሳይሆን የልብ ጉዳይ ነበር። በክርስቶስ የሚያምኑ ሰዎች መሢሕ መሆኑን ቀደም ሲል ተረድተው ነበር። የእርሱም በጎች በመሆናቸው በጎቹ ድምፁን ያውቁታል። የክርስቶስ ተከታዮች የዘላለም ሕይወት አላቸው። ከዚህም በተጨማሪ ዋስትናም አላቸው፤ ምክንያቱም በእጁ መዳፍ ይጠብቃቸዋል። በምድር ብርቱ የሆነው እግዚአብሔር አብ ክርስቲያኖችን ለክርስቶስ ሰጥቷል። ክርስቶስ ከእግዚአብሔር አብ ጋር አንድ ስለሆነ (ይህ ማለት ግን የ«ኢየሱስ ብቻ» ተከታዮች እንደሚሉት አንድ አካል ማለት አይደለም)፤ ማንም የክርስቶስን በጎች ከእጁ ሊወስድ አይችልም። እግዚአብሔር አብና እግዚአብሔር ወልድ የእግዚአብሔርን መንጋ ለመጠበቅ ከወሰኑ፥ ከክርስቶስ እጅ ፈልቅቆ ሊወስዳቸው የሚችለው ማን ነው? ማንም የለም።

የውይይት ጥያቄ፡– ሮሜ 8፡31–39 አንብብ። ሀ) እነዚህ ጥቅሶች እግዚአብሔር ለልጆቹ የሚያደርገውን አስደናቂ ፍቅርና ጥበቃ በተመሳሳይ መንገድ የሚያሳዩት እንዴት ነው? ለ) በችግርህ ጊዜ እነዚህ ምንባቦች የሚያጽናኑህ እንዴት ነው?

የማያምኑት አይሁዶች ኢየሱስ ከሰው የተለየ መሆኑን በትክክል ተገንዝበዋል። እርሱ ሌላው «የእግዚአብሔር ልጅ» (son of god) ነኝ እያለ አለመሆኑን ተረድተዋል። እንዲህ ዓይነቱ የአይሁዶች አነጋገር እንደ ዳዊት ያሉ ሰዎችን የሚያመለክት ስያሜ ነበር (መዝ. 2)። ክርስቶስ ግን የእግዚአብሔር ልዩ ልጅ መሆኑን እየገለጸ ነበር – ከእግዚአብሔር አብ የተለየ ቢሆንም፥ ሙሉ በሙሉ አምላክ ነው። አይሁዶች ይህንን እንደ ስድብ በመቁጠር ክርስቶስን ለመግደል ፈለጉ።

(ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የአዲስ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)

Leave a Reply

%d bloggers like this: