የወንጌል ማዕከል የክርስቶስ ሞትና ትንሣኤ ነው። በዚህ ጉዳይ ላይ ካላተኮሩ የትኞቹም የወንጌል ታሪኮች ሙሉ ሊሆኑ አይችሉም። በመሆኑም፥ እያንዳንዳቸው ስለ ክርስቶስ ሞትና ትንሣኤ ከራሳቸው ልዩ ገጽታ አንጻር ተርከዋል። ዮሐንስ ወይም ክርስቶስ ይወደው የነበረው ደቀ መዝሙር፥ ከሌሎቹ ደቀ መዛሙርት ይልቅ በእነዚያ የመጨረሻ ቀኖች ስለተፈጸሙት ድርጊቶች ብዙ ጽፎአል። ስለሆነም፥ ዮሐንስ በእነዚያ ጥቂት ሰዓታት በኢየሱስ ላይ ስለተፈጸሙት ነገሮች ከራሱ ዕይታ አንጻር የተለየ አመለካከት ያስጨብጠናል።
የውይይት ጥያቄ፡- ዮሐ 18–19 አንብብ። ከእነዚህ ምዕራፎች ስለ ክርስቶስ ምንን እንማራለን? በመጀመሪያዎቹ ሦስት ወንጌላት ውስጥ ስለ ክርስቶስ ያልተጠቀሱ ምን የተለዩ ነገሮች አሉ?
- የኢየሱስ መታሰር (ዮሐ 18፡1-11)
ዮሐንስ ኢየሱስ በጌቴሴማኒ የአትክልት ስፍራ ጽዋው ከእርሱ ታልፍ ዘንድ ያቀረበውን የጭንቅ ጸሎት አልገለጸም። ዮሐንስ ክርስቶስ በዘመናት ሁሉ ለሚኖሩት ደቀ መዛሙርቱ ከጸለየው የሊቀ ክህነቱ ጸሎት በቀጥታ ወደ ሞቱ አምርቷል። ዮሐንስ ስለ ክርስቶስ በመጨረሻ ሰዓታት ከሚያስተምራቸው ዐበይት እውነቶች አንዱ፥ ክርስቶስ ሙሉ በሙሉ ሁኔታዎችን መቆጣጠር የሚችል መሆኑን ነው። በክርስቶስ የደረሰው ነገር ሁሉ ድንገተኛ አልነበረም። ክርስቶስ እንደሚታሰር ያውቅ ነበር። ቀደም ሲል ክርስቶስ ሰዎች ሊገድሉት ወይም ሊያስሩት በሚመጡበት ጊዜ ጥሎአቸው ዘወር ይል ነበር። አሁን ግን ይዘው ሊያስሩት ወደ መጡት ሰዎች ሄዷል። ክርስቶስ፥ ጴጥሮስ ሰይፉን ወደ ሰገባው እንዲመልስ ባዘዘው ጊዜ፥ «አብ የሰጠኝን ጽዋ ልጠጣ አይገባኝምን?» ብሏል። የመሞቻ ጊዜው ስለ ደረሰ ይህንኑ እያወቀ እንደ መሥዋዕት በግ ሞቱን ለመቀበል ሄደ።
ዮሐንስ በተጨማሪም በእነዚያ የመጨረሻዎቹ ሰዓታት እንኳ ክርስቶስ ኃይልና ሥልጣን እንደ ነበረው አሳይቷል። ኃይልና ግርማው ታላቅ በመሆኑ ይዘው ሊያስሩት ወደ መጡት ሰዎች ሲሄድና ሲያዩት ሁሉም መሬት ላይ ወድቀዋል። በመጨረሻው ዘመን ዓለማውያን ያንን የክርስቶስን ቀን ለመቀበል እንደሚገደዱ ሁሉ፥ ሊይዙት የመጡ ወታደሮችም ከፊቱ ለመንበርከክ ተገድደዋል።
ለክርስቶስ ለመዋጋት ሰይፍ ያነሣው ስምዖን ጴጥሮስ መሆኑን የሚነግረን፥ የዮሐንስ ወንጌል ብቻ ነው። ዮሐንስ በተጨማሪም፥ ጆሮው የተቆረጠበት የሊቀ ካህናቱ ባሪያ ስሙ ማልኮስ ይባል እንደ ነበር ገልጾአል። ይህም ዮሐንስ ሁኔታውን በዓይኑ ያየ ሰው ብቻ ሳይሆን፥ ምናልባትም ማልኮስን ሳያውቀው እንደማይቀር ያሳያል።
- ኢየሱስ በሐናንያ ፊት ቀረበ (ዮሐ 18፡12-27)
የመጀመሪያዎቹ ሦስት ወንጌላት ኢየሱስ በወቅቱ ሊቀ ካህናት በነበረው በቀያፋ ፊት መቅረቡን ሲናገሩ፥ የዮሐንስ ወንጌል ደግሞ በሐናንያ ፊት መቅረቡን ይናገራል። ሮማውያን ከአሥራ አምስት ዓመት በፊት ሐናንያን ከሹመቱ አንሥተውት ነበር (15 ዓ.ም)። ነገር ግን አይሁዶች አሁንም እንደ ሊቀ ካህናት በመቁጠር ከሕጋዊው ሊቀ ካህናቱ በስተጀርባ ሆኖ ተሳትፎ እንዲኖረው ሳያደርጉ አልቀሩም። (ቀያፋ የሐናንያ አማች ነበር።)
በርካታ ምሑራን ለራሱና ለጴጥሮስ ወደ ሐናንያ ግቢ የመግቢያ ፈቃድ ያገኘውና ሁኔታውን ሲከታተል የነበረው፥ «ሌላው ደቀ መዝሙር» ዮሐንስ እንደ ሆነ ይናገራሉ። ዮሐንስ የሀብታም ቤተሰብ በመሆኑ፥ ሊቀ ካህናቱን ለማወቅ ዕድል ነበረው። ዮሐንስ ከሌሎቹ ወንጌላውያን ይልቅ ስለ ጴጥሮስ ክህደት ዝርዝር ጉዳዮችን ጠቃቅሷል። ዮሐንስ፥ ጴጥሮስ የክርስቶስ ተከታይ እንደሆነ በመግለጽ ከከሰሱት ሰዎች አንዳንዶቹን እንደሚያውቅ በመግለጽ፥ ክህደቱን በስፍራው ተገኝቶ እንደ ታዘበ አመልክቷል።
- ኢየሱስ በጲላጦስ ፊት ቀረበ (ዮሐ 18፡28–19፡16)
ዮሐንስ ስለ ምርመራው ሊገልጽ፥ በክርስቶስና በጲላጦስ ንግግር ላይ ትኩረት ሰጥቷል። ዮሐንስ ስለ ኢየሱስና ስለ ጲላጦስ ምላሽ ሦስት እውነቶችን አብራርቷል።
ሀ. ጲላጦስ ኢየሱስ የአይሁድ ንጉሥ መሆን አለመሆኑን ሲጠይ፥ (ይህ ለሮም መንግሥት ክህደት ነበር)፤ ኢየሱስ የሰጠው መልስ ጥንቃቄ የተሞላበት ነበር። አንደኛው፥ ኢየሱስ የአይሁድ ንጉሥ መሆኑን ለጲላጦስ ገለጸ። በሁለተኛ ደረጃ ደግሞ፥ መንግሥቱ ሰማያዊና መንፈሳዊ እንጂ ምድራዊ አለመሆኑን አስረዳ፥ የሮም መንግሥት በዚህ ስጋት ሊይዘው እንደማይገባ አመልክቷል።
ለ. ከዚያም ኢየሱስ ጥያቄውን በመንተራስ ጲላጦስን ተቋቋመው። ኢየሱስ ለእውነት፥ ለፍትሕ፥ ለጽድቅና እግዚአብሔርንም ደስ ለሚያሰኝ ነገር የቆሙት ሁሉ እንደሚሰሙት ገለጸ። ጲላጦስ ብዙ ሃይማኖቶች በተነሡበት አገር ስላደገ፥ የትኛው ሃይማኖት ትክክል እንደሆነ አያውቅም ነበር። በተጨማሪም፥ ተወልዶ ያደገው ስለ ሥልጣን እንጂ ስለ እውነት ምንም ግድ በሌለው ሕዝብ ዘንድ ነበር። ለእርሱ እውነት ምንም ማለት አልነበረም። ጲላጦስ ምንም እንኳ ክርስቶስን ከእስር ለመፍታት ቢፈልግም፥ እውነትን ለክብሩ ወይም ለስሙ ሲል በመለወጥ እንዲሰቀል ፈቅዷል። እርሱ ክርስቶስ እንዲሰቀል የተስማማው፥ «የቄሣር ወዳጅ» አይደለም ተብሎ እንዳይወቀስ በመፍራት ነበር። ይህም ሥራውን ከማሳጣት አልፎ ሞትን ሊያስከትልበት ይችል ነበር።
የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) ብዙውን ጊዜ እውነትን ለሰላም፥ ከሰዎች ሞገስ ለማግኘት፥ ወይም ለግል ጥቅም ስንል እንደምንዘነጋ የሚገልጽ አንድ ምሳሌ ስጥ። ለ) በቤተ ክርስቲያንህ እውነትን ወደ ጎን ገፍተው፥ ሌላ ውሳኔ የሰጡበትን ሁኔታ አስረዳ። እውነትንና ፍትሕን ቢያከብሩ ኖሮ ምን ይመስኑ ነበር?
ሐ. ጲላጦስ ክርስቶስ ንጹሕ እንደሆነ በተደጋጋሚ ከገለጸ በኋላ፥ አይሁዶች ክርስቶስን ለመግደል የፈለጉበት ዋነኛው ምክንያት የእግዚአብሔር ልጅ ነኝ በማለቱ እንደሆነ ተናገሩ። ይህም ጲላጦስን አስፈራው። ክርስቶስ መለኮት መሆኑን በግልጽ እንዲናገር ቢጠይቀውም፤ እርሱ ግን መልስ አልሰጠውም። ነገር ግን ጲላጦስ ሕይወቱን የማጥፋት ሥልጣን እንዳለው ሲናገር፥ ክርስቶስ ሥልጣኑን እግዚአብሔር እንደ ሰጠው ገለጸ። ማንኛውም ፖለቲካዊ መሪ በራሱ ሥልጣን የለውም። በመጀመሪያ፥ ሥልጣን የሚገኘው ከእግዚአብሔር ነው (ዳን. 4፡17)። ሁለተኛ፥ እግዚአብሔር ሁኔታዎችን ሙሉ በሙሉ ስለሚቆጣጠር፥ መሪዎች የእግዚአብሔርን ሉዓላዊ ዕቅድ የሚለጥ ውሳኔ ሊያስተላልፉ አይችሉም።
አሕዛብ ሆኖ ሳለ የክርስቶስን ንጽሕና ለማወጅና በነፃ ለማሰናበት ጲላጦስ የተለያዩ መንገዶችን በሚሞክርበት ወቅት አይሁዶች፥ በተለይም መሪዎቹ ያደረጉት ታላቅ ክፋት በዮሐንስ ወንጌል ውስጥ ተገልጾአል። እነዚህ መሪዎች ለፍትሕ ግድ ስላልነበራቸው፥ ሕገወጥና በኃይል ላይ የተመሠረተ ምርመራ በክርስቶስ ላይ ፈጸሙ። አይሁዶች የሕግ ሰው (ጲላጦስ) የሰጠውን ውሳኔ በመጣስ ክርስቶስን ለመግደል ቆረጡ። ስለሆነም፥ ክርስቶስ በዚህ ጉዳይ እነርሱ ከጲላጦስ የከፉ መሆናቸውን ገልጾአል። አይሁዶች የሚያከብሩት ንጉሥ ቄሣር ብቻ መሆኑን በግልጽ ዐወጁ። ይህ ከብሉይ ኪዳን ትምህርት ጋር ፍጹም የማይስማማ አሳብ ነበር። አይሁዶች ሁል ጊዜም እግዚአብሔር ንጉሣቸው እንደሆነ ያምኑ ነበር (1ኛ ሳሙ. 8፡7)። ማንኛውም ምድራዊ ንጉሥ የሚወክለው ራሱን ብቻ ነው። በዚህ አሳባላቸው ግን የልባቸውን እውነተኛ ገጽታ አሳይተዋል። ሃይማኖተኞች ቢሆኑም እንኳ፥ እግዚአብሔር እንዲገዛቸው ከልባቸው አይፈቅዱም ነበር። ስለሆነም፥ እግዚአብሔር ንጉሣቸው አልነበረም።
የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) የክርስቶስ ንጉሥነት በሕይወትህ የታየባቸውን መንገዶች ግለጽ። ለ) ሌላ ነገር ወይም የራሳችን ፈቃድ ንጉሣችን እንዲሆን መፍቀድ ቀላል የሚሆነው እንዴት ነው?