መግቢያ (ገላ. 1፡1-10)

ጥላሁን ከቤተ ክርስቲያኒቱ ታዋቂ ወጣቶች አንዱ ነበር፡ በሰንበት ትምህርት ቤት መምህርነትና የኳዩር ዝማሬን በመሳሰሉት የተለያዩ አገልግሎቶች ይሳተፍ ነበር። ጥላሁን ይህን ታዋቂነት ስለወደደ ሰዎች ያሚፈልጓቸውን ነገሮች ማድረጉን ቀጠለ። አብዛኞቹ ወጣቶች ስሜታዊ አምልኮን ስለሚወዱ ጥላሁን ፕሮግራም ስሚመራበት ጊዜ ሁሉ ምእመናኑ ጮክ ብሎ ስሜታዊ እንቅስቃሴ እንዲያደርግ ያበረታታል። አንዳንድ አባላት የፈውስ አገልግሎት በመፈለጋቸው ጥላሁን ይህንኑ አዘጋጀ። በሰዎች ዘንድ ማራኪና ተወዳጅ ሆኖ የነበረው ነገር ጥላሁን የሚያምንበትና የሚለማመደው ነገር ነበር።

የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) ገላ. 1፡10 እንብብ። እግዚአብሔርን ሳይሆን ሰዎችን ለማስደሰት ስለ መሞከር ጳውሎስ ምን ማለጠንቀቂያ ሰጠ? ሰዎችን ለማስደሰት በምንሞክርበት ጊዜ ማንን እናገለግላለን? ለ) እግዚአብሔርን ለማስደሰት መሞከር አንድን ሰው ታዋቂና ተወዳጅ ላያደርግ የሚችለው እንዴት ነው? ሰዎችን ለማስደሰት መሞከር እግዚአብሔርን እንዴት ሊያስቆጣ እንደሚችል እንዳንድ ምሳሌዎችን ስጥ። ሐ) በተለይ ለቤተ ክርስቲያን መሪዎች ሰዎችን ከማስደሰት ይልቅ እግዚአብሔርን ለማስደሰት መሥራት ጠቃሚ የሚሆነው እንዴት ነው? መ) ለቤተ ክርስቲያን መሪዎች የምእመናንን ፍላጎቶች ማዳመጥ አስፈላጊ የሚሆነው እንዴት ነው?

ብዙዎቻችን የጥላሁን ዓይነት ችግር አለብን። ሰዎችን ለማስደሰት እንፈልጋለን። ስለሆነም እግዚአብሔርን ማስደሰታችንን ሳናረጋግጥ ሰዎችን በማስደሰቱ ላይ አጽንኦት እንሰጣለን። ባሕላችን ስሕተት ቢሆንም እንኳ ኳየራችን የሚያደርገውን፥ ሌሎች ተማሪዎች በትምህርት ቤት የሚሆኑትን፥ ወዘተ… እንድንከተል ያስተምረናል። ተወዳጅነትን ለማትረፍና በቡድኑ ውስጥ ለመታቀፍ ስንል ይህንኑ እናደርጋለን። ሰዎች ክርስቶስን ለማስከበር ከልባቸው በሚጥሩበት ቡድን ውስጥ ካለን ይሄ ብዙም አሳሳቢ አይሆንም። የቤተ ክርስቲያን መሪዎች የምእመኖቻቸውን ፍላጎቶችና ምርጫዎች ማወቃቸውም ጠቃሚ ነው። ታዋቂነት ወይም መንፈሳዊ ለመሆን መፈለግ እግዚአብሔር ከሚፈልገው ጎዳና የሚመልሰን ከሆነ፥ የክርስቶስ ሳይሆን የሰዎች ባሪያዎች ሆነናል ማለት ነው። በመጽሐፍ ቅዱስ ብዙውን ጊዜ አብዛኛው ሕዝብ ትክክል እንዳልሆነ እንረዳለን። አብዛኛው ሕዝብ ትክክለኛ ያልሆኑ ምክንያቶች ስላሉት የተሳሳቱ ተግባራትን ይፈጽማል። አብዛኛውን ጊዜ የእግዚአብሔር ሰዎች እግዚአብሔርን ይታዘዙ ዘንድ ከአብዛኛው ሕዝብ መንገድ ተለይተው ብቻቸውን እንዲቆሙ ተጠርተዋል። እነዚህ ሰዎች የእግዚአብሔር ባሪያዎች ነበሩ። ፊንሐስ ዘመዱን ገድሏል (ዘኁል. 25፡1-13)። ዳዊት ብቻውን ጎልያድን ተጋፍጧል። ኤልያስ ብቻውን የሕዝቡን ርኩሰት ተቃውሟል። ጳውሎስ በቤተ ክርስቲያን ውስጥ ክርስትናን የሥራ ሃይማኖት ለማድረግ የተደረገውን ጥረት ተቃውሟል። እንዲያውም ጳውሎስ የጥንቷ ቤተ ክርስቲያን ታላቅ ሐዋርያ የነበረ ጴጥሮስ ስሕተትን በፈጸመ ጊዜ ገሥጾታል። ጓደኛውና የወንጌሉ ሥራ ባልደረባ የነበረውን በርናባስንም ተገዳድሮታል። እግዚአብሔር ቀዳሚ ጉዳያችን «ሰው ምን ይለኛል» ሳይሆን፥ «እግዚአብሔር ምን ይለኛል» የሚል እንዲሆን ይፈልጋል።

ጳውሎስ የጥንቱን ዘመን የደብዳቤ አጻጻፍ በመከተል፥ የመልእክቱ ጸሐፊ መሆኑን ይናገራል። ብዙውን ጊዜ ጳውሎስ ሌሎች ጸሐፊዎችን ስለሚጠቀም ጠቅላላውን መልእክት ስለ መጻፉ እርግጠኞች አይደለንም። (ለምሳሌ፥ ሮሜ 16፡22ን ተመልከት።) በገላትያ 6፡11 ጳውሎስ፦ «እንዴት ባሉ ታላላቆች ፊደላት በእጄ እንደ ጻፍሁላችሁ እዩ» ብሏል። ይህ ፊርማውንና የመደምደሚያ ሃሳቡን ሊያመለክት ይችላል፤ ወይም ደግሞ ጳውሎስ የገላትያን መልእክት በገዛ እጁ መጻፉን ሊያሳይ ይችላል።

የጳውሎስ መግቢያ ብዙውን ጊዜ በመልእክቱ ውስጥ ሊያተኩር የፈለገውን አሳብ ያሳያል። ጳውሎስ ለገላትያ ሰዎች በጻፈው መልእክት መግቢያ ውስጥ በሐዋርያነት ምንጭ ላይ አጽንኦት ሰጥቷል። በገላትያ አብያተ ክርስቲያናት ውስጥ የሚሠሩ የሐሰት አስተማሪዎች ጳውሎስ ክርስቶስ በምድር ላይ በነበረበት ጊዜ አብሮት ስላልነበረ እውነተኛ ሐዋርያ አይደለም ይሉ ነበር። ከሞት የተነሣውን ጌታ ካለማየቱም በላይ በኢየሩሳሌም ያሉት ሐዋርያት ስላልመረጡትና ስላልላኩት ጳውሎስ ሐሰተኛ ነው ብለው የሐሰት አስተማሪዎቹ ተናገሩ። በገላትያ 1-2 በዚህ ክስ ላይ በማተኮር መልእክቱን በቀጥታ ከክርስቶስ እንደ ተቀበለና ከዚህም የተነሣ እውነተኛ እንደሆነ ያሳያቸዋል። ጳውሎስ ትምህርቱን በሚያስተዋውቅበት ጊዜ ሐዋርያ ነኝ የሚለው ሐዋርያነቱና መልእክቱ እንደ ጴጥሮስ ካሉ ዝነኛ ሰዎች ወይም እንደ ሐዋርያት ካሉ ቡድኖች ስለመነጨ አለመሆኑን ያስረዳል። የሐዋርያነት ጥሪው በቀጥታ ከክርስቶስ ነበር የመጣው።

መልእክቱ የተላከው በገላትያ ለሚገኙ አብያተ ክርስቲያናት» ነበር። አብዛኞቹ የጳውሎስ መልእክቶች የሚላኩት በከተማ ውስጥ ለሚገኙ አብያተ ክርስቲያናት ወይም ግለሰቦች ነበር። ይህ መልእክት ግን በገላትያ አውራጃ ውስጥ ለሚገኙ አያሌ አብያተ ክርስቲያናት ሳይላክ አልቀረም።

ጳውሎስ ሰላምታውን ካቀረበ በኋላ በሰላምታው ውስጥ የወንጌሉን ቁም ነገር (አስኳል) ያብራራል። ክርስቲያኖች ጸጋና ሰላም የሚያገኙት ክርስቶስ ራሱን ለኃጢአታቸው መሥዋዕት አድርጎ ስለሰጣቸው ነው። የክርስቶስ ሞት መንፈሳዊ ድነትን (ደኅንነትን) ከማስገኘቱም በላይ «ከአሁኑ ክፉ ዘመንም» ያድነናል። ለእግዚአብሔር ቅዱሳን እንሆን ዘንድ ተለይተናል።

የአዲስ ኪዳን ጸሐፊዎች፥ ታሪክ ሁለት ዘመናትን እንደሚያካትት ያስባሉ። አዳምና ሔዋን ኃጢአትን በፈጸሙ ጊዜ የተጀመረ «የአሁኑ ክፉ ዘመን» አለ። ይህ ዘመን ክርስቶስ ለመግዛት ሲመለስና ኃጢአትን ሲደመስስ ከፍጻሜ ይደርሳል። በክርስቶስ የመስቀል ላይ ሞትና በመንግሥቱ ጅማሬ የተጠነሰሰው «ወደፊት የሚመጣ ዘመን» አለ (ማቴ. 12፡32)። ክርስቶስ ወደ ምድር ተመልሶ በፍጹማዊ ሥልጣን በሚገዛበት ጊዜ ዘላለማዊ መንግሥቱ ይጀመራል። በዘላለሙ መንግሥት ኃጢአት ወይም በእግዚአብሔር ላይ የሚፈጸም ዓመፅ አይኖርም፡፡ አሁን ክርስቶስ በሕይወታችን ውስጥ በሚገዛበት ጊዜ ይህንኑ መንግሥት «እንቀምሳለን»። ወደፊት በዘላለሙ መንግሥት ከክርስቶስ ጋር በምንነግሥስት ጊዜ ይህንኑ ሊመጣ ያለውን ዘመን ሙሉ ለሙሉ እንቋደሰዋለን።

ከሌሎች የጳውሎስ መልእክቶች በተቃራኒ፥ በገላትያ መልእክት ውስጥ አንድም የምስጋና ቃል አልተጠቀሰም። ነገር ግን ጳውሎስ ከመበሳጨቱ የተነሣ በገላትያ ክርስቲያኖች ላይ ቁጣና ንዴትን ወዲያውኑ ማሳየት ይጀምራል። በጥቂት ዓመታት ውስጥ ከእውነተኛው ወንጌል ወደ ሌላ የሐሰት ወንጌል ተመልሰው ነበር። ወደ እግዚአብሔር መድረስ የሚቻለው በተለያዩ መንገዶች አማካኝነት ሳይሆን በአንድ እውነተኛ ወንጌል ብቻ ነው። በእውነተኛው ወንጌል ላይ የሚጨምር፥ የሚቀንስ ወይም የተለየ ወንጌል የሚያቀርብ ሁሉ ሰዎችን ሊያድን የማይችለውን ሐሰተኛ ወንጌል ያስተምራል። ጳውሎስ እጅግ የተቆጣው ሰዎች ለዘላለም ወደ መንግሥተ ሰማይ ወይም ሲኦል የሚሄዱበት ዕድል የሚወሰነው እውነተኛ ወይም ሐሰተኛ ወንጌል በማመናቸው ምክንያት በመሆኑ ነው። ስለሆነም መልአክ ከሰማይ ቢመጣና እርሱ ራሱም ቢለወጥ እንኳ ሌላ ወንጌል የሚሰብኩትን ሰዎች እንዳይሰሙ አስጠንቅቋቸዋል። ጳውሎስ የሐሰት ትምህርት የሚያስፋፉ ሰዎችን ሌሎችን ወደ ሲኦል እየሰደዱ በመሆኑ ራሳቸው ሲኦል ቢወርዱ እንደሚወድ በቁጣ ተናግሯል።

የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) ሰዎች ያሻቸውን እንዲያምኑ ዝም ብሎ ከመተው ይልቅ የወንጌሉን እውነት በጽኑ አቋም መከላከል የሚያስፈልገው ለምንድን ነው? ለ) ይህን ማድረግ ከባድ የሚሆነው ለምንድን ነው? ሐ) የሐሰት ትምህርት እንዲስፋፋ አንከላከል ብንፈቅድ የእግዚአብሔር ባሪያዎች ስለመሆናችን ወይም ለሰዎች ስላለን በጎ አስተሳሰብ ምን ያሳያል?

ጳውሎስ ቀላሉን መስመር ተከትሎ እንደ ሐሰት አስተማሪዎቹ ሰዎችን ለማስደሰት ሲል እምነቱን ወይም ወንጌሉን ለመለውጥ አልፈለገም። ሰዎችን ቢያስቆጣም እንኳ ጳውሎስ እንደ እግዚአብሔር ሐዋርያ ለማገልገል ቆርጧል። ከዚህ ውጭ የሆነ ምንም ዓይነት ምርጫ ሰዎች ወደ ሲኦል እንዲወርዱና እርሱም የሰዎች ባሪያ እንዲሆን ያደርገው ነበር።

(ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የአዲስ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)

Leave a Reply

%d bloggers like this: