በክርስቶስ አንድ መሆን (ኤፌ. 2፡11-22)

የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) በዓለም ውስጥ የሚገኙትን አንዳንድ የጎሳ፥ የምጣኔ ሀብትና የጾታ ክፍፍሎች ዘርዝር። ለ) እነዚህ ልዩነቶች ብዙውን ጊዜ በቤተ ክርስቲያን ውስጥ የሚንጸባረቁበትን ሁኔታ ግለጽ። ሐ) እነዚህ ልዩነቶች የሚያስከትሏቸው አሉታዊ ውጤቶች ምን ምንድን ናቸው?

በአይሁዶች አስተሳሰብ፥ ዓለም በሁለት ምድቦች የተከፈለች ነበረች። እነዚህም ሁለት ቡድኖች «የተገረዙት» ምርጥ የእግዚአብሔር ሕዝቦችና የቃል ኪዳን በረከቶችን ይጋሩ ዘንድ ያልተመረጡት (ያልተገረዙት) አሕዛብ ነበሩ። በእስያ ክፍለ ሐገራት አብዛኛውን ቁጥር የሚይዙት አሕዛብ እንጂ አይሁዳውያን አልነበሩም። ስለሆነም፥ ጳውሎስ ከማመናቸው በፊት እንደ አሕዛብ ያሳለፉትን ሕይወት ያስገነዝባቸዋል። ጳውሎስ እግዚአብሔር በጸጋው ቤተ ክርስቲያንን በመሠረተ ጊዜ የነበረውን አስደናቂ ፍቅር ያብራራል። ከክርስቶስ ሞትና እግዚአብሔር፥ ቤተ ክርስቲያን በምትባለው አካል ውስጥ የሚገኙትን አዲስ ሕዝብ ከመፍጠሩ በፊት አሕዛብ ተስፋ በሌለው ሁኔታ ውስጥ ነበሩ።

ሀ. አሕዛብ የእግዚአብሔር ትኩረት የሆነው የታላቁ እስራኤል ሕዝብ አካል አልነበሩም። ሁልጊዜም ወደ ውጭ የተገለሉና የተናቁ ሰዎች ነበሩ።

ለ. ለተስፋው ቃል ኪዳን እንግዶች ነበሩ። አሕዛብ የአብርሃም ቃል ኪዳን፥ የሲና ተራራ ቃል ኪዳን፥ የአሮን ቤተሰብ ቃል ኪዳን፥ የከነዓን ምድር ቃል ኪዳንና የዳዊት ቃል ኪዳን ተካፋይ አልነበሩም። የነበራቸው ተስፋ ቢኖር እግዚአብሔር አንድ ቀን በአብርሃም በኩል እንደሚባርካቸው የሚያመለክት ፍንጭ ብቻ ነበር። ስለሆነም አሕዛብ ከእግዚአብሔር የብሉይ ኪዳን የቸርነት ምርጫና በረከት ውጭ ነበሩ።

ሐ. አሕዛብ ተስፋ አልነበራቸውም። ከክርስቶስ ሞት በፊት እነዚህ አሕዛብ እግዚአብሔር ከሕዝቡ ጋር ስለሚዛመድበት ሁኔታ ከገለጸው ቃል ኪዳን ውጭ በመሆናቸው በእግዚአብሔር ዘንድ ተቀባይነትን አግኝተው የሚድኑበት ተስፋ አልነበራቸውም።

መ. ያለ እግዚአብሔር ነበሩ። አሕዛብ በብዙ አማልክት ቢያምኑም፥ አንዱንና እውነተኛ የሆነውን አምላክ አያውቁም ነበር። እግዚአብሔር ማንነቱንና እንዴት ሊያመልኩት እንደሚገባ የገለጸበትን ብሉይ ኪዳን አልተሰጣቸውም ነበር። ስለሆነም፥ ተስፋ በሚያስቆርጥ ሁኔታ ውስጥ ነበሩ።

እንግዲህ በአዲስ ኪዳን ምን ለውጥ ታየ? ክርስቶስ በመስቀል ላይ ሲሞትና የአሕዛብን የበረከት በር ሲከፍት ምን ተከሰተ?

ሀ. እግዚአብሔር በክርስቶስ ሞት (በክርስቶስ ደም) አማካኝነት ከእርሱ ጋር የሚዛመዱበትን ዕድል ሰጣቸው። አሕዛብን ወደ ራሱ አስጠጋቸው።

ለ. ክርስቶስ በብሉይ ኪዳን አይሁዶችንና አሕዛብን የከፋፈለውን የመለያየት ግድግዳ አስወገደ። በእነዚህ ሁለት ሕዝቦች መካከል የነበረውን የጥላቻ ግድግዳ አፈረሰ።

ሐ. ኢየሱስ «አዲሱ ሰው» ወይም «አንድ አካል» የተባለችውን ቤተ ክርስቲያን ፈጠረ። አሁን ቅርብ የነበሩት አይሁዶች ወደ እግዚአብሔር ለመምጣት በሚፈልጉበት ጊዜ፥ በክርስቶስ በኩል ወደ አይሁድ ሕዝብ ሳይሆን ወደ ቤተ ክርስቲያን መግባት ይኖርባቸዋል። ርቀው የነበሩት አሕዛብ ስለ ክርስቶስ ሰምተው በሚያምኑበት ጊዜ በእግዚአብሔር ዘንድ ተቀባይነትን አግኝተው ወደ ቤተ ክርስቲያን ይገባሉ። አይሁዶችና አሕዛብ እኩል ሆነዋል። አይሁዶችም ሆኑ አሕዛብ የሚድኑት በክርስቶስ በማመን ነው። በቤተ ክርስቲያን ውስጥም ቢሆን ሁለቱም አንድ ናቸው።

መ. አይሁዶችም ሆኑ አሕዛብ በቤተ ክርስቲያን ውስጥ ተመሳሳይ በረከቶችን ያገኛሉ። ሁለቱም፥

1) ከእግዚአብሔር ሕዝብ ጋር ባላገሮች ናቸው። ይህም በእኩል ደረጃ የእግዚአብሔር ሕዝብና የእግዚአብሔር መንግሥት አካል መሆናቸውን ያሳያል።

2) የእግዚአብሔር ቤተሰብ አባላት ናቸው። ጳውሎስ የቤትን ምስያ በመጠቀም፥ በክርስቶስ በኩል አይሁዶችና አሕዛብ የአዲሱ ቤት አካል መሆናቸውን ገልጾአል። የጥንት ቤቶች በሚሠሩበት ጊዜ በወሳኝ ስፍራዎች ላይ ትላልቅ የመሠረት ድንጋዮች ይቆሙ ነበር። ከሁሉም የሚተልቅና የሚሻል የማዕዘን ድንጋይም ይጠቀሙ ነበር። በእግዚአብሔር መንፈሳዊ ቤት፥ ታላላቆቹ ድንጋዮች የቤተ ክርስቲያን መሥራቾችና መሪዎች የሆኑት ሐዋርያትና ነቢያት ናቸው። ነገር ግን በዚህ አዲስ የእግዚአብሔር ቤት ውስጥ እጅግ ጠቃሚ የሆነ አንድ ዓለት ነበር። እርሱም የማዕዘን ድንጋይ የሆነው ክርስቶስ ነበር። ይህ አዲሱ የቤተ ክርስቲያን ሕንፃ በእግዚአብሔር ዓላማና ንድፍ መሠረት እንዲሠራ የሚያደርገው ክርስቶስ ነው።

3) ቅዱስ ቤተ መቅደስ። አይሁዶች በኢየሩሳሌም የሚገኘው ቤተ መቅደስ ልዩ የእግዚአብሔር ሕዝብ መሆናቸውን የሚያሳይ ልዩ ተምሳሌት እንደሆነ ያስቡ ነበር። የአይሁድ ክርስቲያኖችም በኢየሩሳሌሙ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ ያመልኩ ነበር። ይህን ልምምድ ያቋረጡት ጳውሎስ ይህን መልእክት ከጻፈ ከ10 ዓመታት ያህል በኋላ ነበር። በቤተ መቅደሱ ውስጥ አሕዛብ ወደ ውስጥ ሲገቡ እንደሚሞቱ የሚያስጠነቅቅ ውስብስብ ምልክት ነበር። ጳውሎስ ግን የእግዚአብሔር ንድፍ የሆነ የተሻለ፥ አዲስና «ቅዱስ» ቤተ መቅደስ እንደ ተሠራ ገልጾአል። ይህም የእግዚአብሔር ልጆች ኅብረት የሚያደርጉባትን ቤተ ክርስቲያን የሚያመለክት ነው።

4) እግዚአብሔር በመንፈስ የሚያድርበት መኖሪያ። የብሉይ ኪዳን የተስፋ ቃል፥ አይሁዶች የመገናኛውን ድንኳንና በኋላም ቤተ መቅደሱን በገነቡ ጊዜ እግዚአብሔር በዚያ ውስጥ እንደሚኖር ነበር (ዘጸ. 29፡45-46)። ይህንን በግልጽ ለማሳየት የመገናኛው ድንኳንና ቤተ መቅደሱ በተሠራ ጊዜ፥ የእግዚአብሔር ክብር ከሰማይ ወርዶ ቅድስተ ቅዱሳኑን ይሞላ ነበር (ዘጸ. 40፡34-38)። ነገር ግን ጳውሎስ አሁን የእግዚአብሔር ልጆች መንፈሳዊ ቤተ መቅደሱ መሆናቸውን ካብራራ በኋላ፥ እግዚአብሔር አይሁዶች በሚያከብሩት ቤተ መቅደስ ውስጥ እንዳደረ ሁሉ በእኛም ውስጥ እንዳደረ አመልክቷል። መንፈስ ቅዱስ በልባችን ውስጥ በማደር የሕያው፥ ዘላለማዊና ሁሉን ቻይ አምላክ የመኖሪያ ስፍራ ያደርገናል።

የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) በሚቀጥለው ጊዜ ወደ ቤተ ክርስቲያንህ ስትሄድ ዙሪያ ገባውን እየተመለከትህ ይህንኑ ስለ ቤተ ክርስቲያንና ስለ እግዚአብሔር ሕዝብ የተሰጠውን መግለጫ አስብ። እነዚህ ከእግዚአብሔር ጋር ስላለን ግንኙነት የሚናገሩ በረከቶች ሊያበረታቱንና አኗኗራችንን ሊለውጡ የሚገባቸው እንዴት ነው? ለ) ብዙውን ጊዜ በቤተ ክርስቲያን ውስጥ ከዘር፥ ምጣኔ ሀብት ወይም ከትምህርት ጋር በተያያዘ ክፍፍሎች ይከሰታሉ። ይህ እግዚአብሔር ልጆቹን ሁሉ አንድ ለማድረግ ካለው ፍላጎት ጋር የሚቃረነው እንዴት ነው? እነዚህን የመለያየት ግድግዳዎች ለማስወገድ ምን ማድረግ ይቻላል?

(ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የአዲስ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)

Leave a Reply

%d bloggers like this: