የውይይት ጥያቄ፡- ጳውሎስ በኤፌሶን 1፡15-23 ያቀረበውን ጸሎት ብዙውን ጊዜ አንተ ለሰዎች ከምትጸልየው ጋር አነጻጽር። የጳውሎስን ጸሎት ከእኛ ጸሎት የሚለዩት ነገሮች ምን ምንድን ናቸው?
የጳውሎስን ጸሎት እኛ ብዙውን ጊዜ ለሰዎች ከምንጸልየው ጸሎት ጋር ስናነጻጽር፥ ብዙ ልዩነቶችን ልንመለከት እንችላለን። ብዙውን ጊዜ ለሰዎች በምንጸልይበት ጊዜ እግዚአብሔር በሥጋ እንዲባርካቸው እንጠይቃለን። እግዚአብሔር ጤና እንዲሰጣቸው፥ በጉዞ ወቅት ከአደጋ እንዲጠብቃቸው፥ ምግብ እንዲሰጣቸው፥ ወዘተ… እንጠይቃለን። ጳውሎስ የእግዚአብሔር ሕዝብ ከዚህ የጠለቀና የላቀ ፍላጎት እንዳለው አጢኗል። ይህም የመንፈሳዊ ዕድገት፥ በተለይም እግዚአብሔርን በሚያስከብር እውቀት ማደግ ነው። ጳውሎስ ለኤፌሶን ክርስቲያኖች በጻፈው በዚሁ የመጀመሪያው ጸሎት ውስጥ የሚከተሉትን ነገሮች ልንመለከት እንችላለን።
ሀ. ጳውሎስ «እርሱን በማወቅ የጥበብና የመገለጥን መንፈስ እንዲሰጣችሁና በእግዚአብሔር ዕውቀት እንድታድጉ» እያለ ይጸልያል። ጳውሎስ ለኤፌሶን ክርስቲያኖች መልእክት የጻፈበት ዓላማ እግዚአብሔር ልጆቹን ስለሚባርክበት ሁኔታ በማወቅ እንዲያድጉ ነበር። እግዚአብሔርን የበለጠ ስናውቅና ከእርሱ ጋር የቀረበ ግንኙነት ሊኖረን፥ ጸሎታችን ከእግዚአብሔር ፈቃድ ጋር ይስማማል። እግዚአብሔርን በበለጠ ስናውቅ መንፈሳዊ ጉዟችን ጽኑ ይሆናል። እውቀት ለመንፈሳዊ ጤንነታችን መሠረት በመሆኑ፥ ምርጫ ውስጥ የሚገባ ጉዳይ አይደለም። የሚያሳዝነው ብዙ ክርስቲያኖች በእግዚአብሔር እውቀት ለማደግ አይፈልጉም። ስለ እግዚአብሔር፥ ስለ ባሕርያቱ፥ ስለ ተግባራቱ፣ ስለ ፈቃዱ፥ ወዘተ.. ጊዜ ወስደው አያጠኑም። ይህም ለሐሰት ትምህርት፥ ሚዛናዊ ላልሆነ አምልኮና ለኃጢአት ያጋልጣቸዋል።
የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) ስለ እግዚአብሔር ያለህ የጠለቀ እውቀት በመንፈሳዊ ጉዞህ እንዴት እንደረዳህ ግለጽ። ለ) የጸሎት ሕይወትህን እንዴት እንደረዳው አስረዳ። ሐ) ምእመናን ስለ እግዚአብሔር ባላቸው እውቀትና ግንኙነት እንዲያድጉ ለማገዝ ቤተ ክርስቲያንህ ምን እያደረገች ነው? መ) ይህ አጥጋቢ ውጤት እንዲያስገኝ ምን ሊያደርጉ ይችላሉ?
ለ. ጳውሎስ አማኞች ስለ ወደፊት ሕይወታቸው፥ ስለ ብልጽግናቸውና የእግዚአብሔርን ዘላለማዊ መንግሥት ስለ መውረሳቸው ግልጽ ግንዛቤ እንዲኖራቸው ይጠይቃል። ዓለም እንደ በሽታ፥ ስደትና ሞት ባሉት ተስፋ አስቆራጭ ነገሮች የተሞላች ነች። መፍትሔው ምንድን ነው? እንግዲህ ተስፋ የሚሰጠን ምንድን ነው? ጳውሎስ በዘላለማዊ ቤታችን የሚጠብቀንን በትክክል መረዳቱ ተስፋ እንደሚሰጠን ያውቅ ነበር። ስለሆነም፥ የወደፊቱን ታላቅ ስፍራና በረከት እንገነዘብ ዘንድ እግዚአብሔር እንዲረዳን ጸልዮአል።
ሐ. ጳውሎስ የኤፌሶን ክርስቲያኖች እግዚአብሔር ለልጆቹ የሚሰጠውን ታላቅ ኃይል ተረድተው እንዲጠቀሙበት ጸልዮአል። እግዚአብሔር በሚፈልገው መንገድ የተቀደሰ ሕይወት ልንኖር የምንችለው ይህንን ኃይል ስንጠቀም ነው። ይህ ምን ዓይነት ኃይል ነው? ጳውሎስ ይህ በክርስቶስ ሕይወት ውስጥ የነበረው ዓይነት ኃይል እንደሆነ ገልጾአል። ያ ኃይል፥ 1) ክርስቶስን ከሞት አስነሥቷል። 2) ክርስቶስን በሰማይ በእግዚአብሔር ቀኝ አስቀምጦታል። 3) ክርስቶስን በሰማይና በምድር የመጨረሻው ባለሥልጣን አድርጎታል። ጳውሎስ በምድር ላይ የክርስቶስ አካል የሆነችው ቤተ ክርስቲያን ይህንን አስደናቂ ኃይል ልትጠቀም እንደምትችል ገልጾአል።
የውይይት ጥያቄ፡- ስለ ጸሎቶችህ አስብ። ሀ) ለራሳችንና ለሌሎች የምናቀርባቸው ጸሎቶች በሥጋዊ በረከቶች የሚሞሉት እንዴት ነው? ለ) ጸሎቶችህን ከጳውሎስ ጸሎቶች ጋር ለማመሳሰል ምን ዓይነት ለውጦችን ማድረግ ትችላለህ?
(ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የአዲስ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)