ጳውሎስ ለአሕዛብ የተመረጠ ሐዋሪያ መሆኑ እና ለኤፌሶን ክርስቲያኖች የተደረገ ጸሎት (ኤፌ. 3፡1-21)

፩) ጳውሎስ ተሰውሮ የኖረውን ስለ ኢየሱስ ክርስቶስ የሚናገረውን የወንጌል ምሥጢር ለማስተማር በእግዚአብሔር የተመረጠ አገልጋይ ነበር (ኤፌ. 3፡1-13)።

ጳውሎስ ለአማኞቹ ሌላ ጸሎት ለመጀመር ፈልጎ ነበር። ነገር ግን እግዚአብሔር ታላቁን ምሥጢር በመግለጽ ረገድ ስለሰጠው ድርሻ አሰበ። ጳውሎስ እግዚአብሔር ስለ ቤተ ክርስቲያን ምሥጢሩን እንዲገልጽ የመረጠው በታላቅነቱ፥ የተማረ በመሆኑ፥ ወይም አይሁዳዊ በመሆኑ ሳይሆን በጸጋው እንደሆነ ያውቅ ነበር። ጳውሎስ ስለዚህ ምሥጢሩን፥ «በወንጌል መስበክ በክርስቶስ ኢየሱስ በሆነ የተስፋ ቃል አብረው እንዲካፈሉ፥ ለቅዱሳን ሐዋርያትና ለነቢያት በመንፈስ አሁን እንደተገለጠ በሌሎቹ ትውልዶች ዘንድ ለሰው ልጆች አልታወቀም» ብሏል። ስለሆነም፥ ምሥጢሩ በብሉይ ኪዳን ዘመን ያልተገለጠውና እግዚአብሔር በአዲስ ኪዳን ዘመን የገለጠው እውነት ነው። ለክርስቲያኖች ይህን ልዩነት ማወቁ ጠቃሚ ነው። አንዳንድ ጊዜ በብሉይ ኪዳን ለእስራኤላውያን የተሰጡትን የተስፋ ቃሎች በቀጥታ ከራሳችን ጋር በማዛመድ ስሕተት እንሠራለን። ምንም እንኳን ከሕይወታችን ጋር የሚዛመዱ መርሆች ቢኖሩም፥ ብዙ ትእዛዛት፥ ሕግጋትና የተስፋ ቃሎች በብሉይ ኪዳን ዘመን የእስራኤልን ሕዝብ የሚመለከቱ ናቸው። እግዚአብሔር በብሉይ ኪዳን ዘመን አዲሱ ሕዝብ የሚገኝባትን ቤተ ክርስቲያን የመፍጠር ዓላማዎቹን ይፋ አላወጣም ነበር። የቤተ ክርስቲያን ዓላማዎቹን በጳውሎስና በሌሎችም አገልጋዮቹ በኩል የገለጸው ከክርስቶስ ሞት በኋላ ነበር። እንግዲህ የተገለጠው ምሥጢር ምንድን ነው? በቤተ ክርስቲያን ውስጥ እግዚአብሔር አሕዛብ በክርስቶስ አማካኝነት ከአይሁዶች ጋር እኩል እንዲወርሱ አድርጓል። ከእንግዲህ በእግዚአብሔር ዓይኖች ፊት በአይሁዶችና በአሕዛብ መካከል ልዩነት የለም።

እግዚአብሔር ቤተ ክርስቲያንን የጀመረው ለምን ዓላማ ነበር? እግዚአብሔር የክርስቶስ አካል በሆነችው ቤተ ክርስቲያን በኩል በገዥዎችና በሰማያዊ ስፍራ ባሉት ባለሥልጣናት ፊት ታላቅ ጥበቡን ለማሳየት ፈልጓል። ይህም መላእክትን፥ ሰይጣንንና አጋንንትን የሚመለከት ነው። እግዚአብሔር የጎሳና የምጣኔ ሀብት ልዩነቶችን ያስወገደበት የቤተ ክርስቲያን (የአዲስ ሕዝብ) መፈጠር ለጥበቡ ታላቅ ምስክር ነው። ምንም እንኳ ቤተ ክርስቲያን ከኃጢአትና ከሐሰት ትምህርቶች ጋር የሚታገሉ ደካማ ሰብአዊ ፍጡራን የሚገኙባት ብትሆንም፥ ለፍጥረት ሁሉ ማለትም ለሰዎችም ሆነ ለመንፈሳውያን ፍጥረታት ታላቅ ጥበቡን የሚያሳይባት የእግዚአብሔር ዋነኛ መሣሪያው ነች።

፪) ጳውሎስ አማኞች የክርስቶስንና ከእርሱ ጋር ያላቸውን ግንኙነት ታላቅነት እንዲገነዘቡ እግዚአብሔር እንዲያጠነክራቸው ይጸልያል (ኤፌ. 3፡14-21)።

በኤፌሶን 3፡1 ጳውሎስ ወደ እግዚአብሔር መጸለይ ከጀመረ በኋላ እግዚአብሔር ለቤተ ክርስቲያን ስላለው አስደናቂ ዕቅድና እርሱም ይህን ታላቅ ምሥጢር በማብራራቱ በኩል የእግዚአብሔር አገልጋይ መሆኑን ገልጾአል። አሁን ጳውሎስ ወደ ጸሎቱ ይመለሳል። ጳውሎስ በዚህ መልእክት የመጀመሪያው ክፍል ባብራራቸው እውነቶች ላይ በመመሥረት፥ አማኞች እንዲማሩና አንዳንድ ጠቃሚ ነገሮችን ከሕይወታቸው ጋር እንዲያዛምዱ ይጸልያል።

ሀ. ክርስቶስ በልባቸው ውስጥ በእምነት ይኖር ዘንድ በውስጥ ሰውነታቸው እንዲጠነክሩ ይጠይቃቸዋል። ጳውሎስ እግዚአብሔር ከከበረው የጸጋው ባለጠግነት ለእነዚህ አማኞች ጸጋንና ኃይልን እንዲሰጣቸው ይጠይቃል። ትልቁ ፍላጎቱ ክርስቶስ በልባቸው ውስጥ በንጉሥነት እንዲኖር ነበር። ጳውሎስ ክርስቶስ ልባቸውን እንዲጎበኝ ብቻ ሳይሆን አብሯቸው በመኖር ከእነርሱ ጋር ኅብረትን እንዲያደርግ ይፈልጋል።

ለ. ጳውሎስ በፍቅር ሥር ሰድደው እንዲመሠረቱ ይጸልያል። ይህ ሥሩን ወደ መሬት አጥልቆ የሰደደን ትልቅ ዛፍ የሚያሳይ ምስል ነው። ጳውሎስ በእግዚአብሔር አስደናቂ ጸጋ ስለ ክርስቶስ ፍቅር የጠለቀ እውቀት እንዲኖረን ይፈልጋል። ሕይወታችንን ክርስቶስ እንደ ግለሰብና እንደ ቤተ ክርስቲያን ለእኛ ባለው ፍቅር በሚማርክበት ጊዜ እርሱን ደስ የሚያሰኝ ማንኛውንም ተግባር ከማከናወን ወደ ኋላ አንልም። እርሱን በመውደድ ለክብሩ እንኖራለን። በዚህ ጊዜ የእግዚአብሔር ክብር በብሉይ ኪዳን ዘመን ቤተ መቅደሱን እንደ ሞላ ሁሉ የእኛንም ሕይወት ይሞላዋል።

እግዚአብሔር ካለን ሕይወት የሚመነጨው ፍቅር እርስ በርሳችንም እንድንፋቀር ያደርገናል።

የውይይት ጥያቄ፡– የጳውሎስን ሁለት የጸሎት ጥያቄዎች ተመልክት። ሀ) እነዚህ ሁለት እውነቶች በሕይወታችን እውን ሊሆኑ የሚገባቸው ለምንድን ነው? ለ) የግልህንና የቤተ ክርስቲያንህን ችግሮች ዘርዝር። የእነዚህ ሁለት የጸሎት ጥያቄዎች መልሶች ለችግሮቻችን ሥሮች መፍትሔ የሚሰጡት እንዴት ነው? ሐ) በጳውሎስ ጸሎት መሠረት፥ እግዚአብሔር እንደሚፈልገው እንድንሆን ከሚያስፈልጉን ነገሮች እንደኛው ምንድን ነው?

(ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የአዲስ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)

Leave a Reply

%d