የቆላስይስ መልእክት መግቢያ

አንድ ሳይንቲስት በእንቁራሪት ላይ ምርምር አደረገ። መጀመሪያ ውኃ አፈላና እንቁራሪቷን እዚያው ውስጥ ጨመራት። ውኃው በነካት ጊዜ እንቁራሪቷ ትዘል ጀመር። የፈላው ውኃ ሲያቃጥላትም አልሞተችም። ሌላዋን እንቁራሪት ደግሞ በቀዝቃዛ ውኃ ውስጥ ጨመራት። የውኃውና የእንቁራሪቱ የሙቀት መጠን ተመጣጣኝ ስለነበር ይህችኛዋ እንቁራሪት ሳትዘል ዝም ብላ ተቀመጠች። ከዚያም ላይንቲስቱ ቀዝቃዛውን ውኃ እዚያው ውስጥ ካለችው እንቁራሪት ጋር አነስተኛ ሙቀት ባለው ምድጃ ላይ ጣደ። ውኃው ቀስ በቀስ እየፈላ ሄደ። የሚገርመው እንቁራሪቷ ምንም ዓይነት የመንፈራገጥ ምልክት ሳታሳይ በውኃ ሙቀት ተጠብሳ እስክትሞት ድረስ ዝም አለች።

እግዚአብሔር ቤተ ክርስቲያን ከዓለም እሴቶችና የአኗኗር ስልቶች እንድትለይ ጠርቷታል። በዓለም ውስጥ እንደ ጨውና ብርሃን እንድንኖር ታዝዘናል። ብዙውን ጊዜ አማኞች የስደት «ግለት» ወይም ሌሎች ሃይማኖቶች በሚያጋጥሟቸው ጊዜ፥ ልዩ ማንነታችንን ለመጠበቅ እንጥራለን። ስደትና ሌሎች ሃይማኖቶች እምብዛም ለቤተ ክርስቲያን አስጊዎች አይደሉም። ነገር ግን ሰይጣን በተዘዋዋሪ መንገድ ቤተ ክርስቲያንን ለማጥፋት ሲፈልግ ዓለምን እንድትመስል ያደርጋታል። ሰይጣን ክርስቲያኖች ከሚያምኗቸው ትምህርቶችና እምነቶች በመጠኑ ለየት ያለ አስተሳሰብ በማቅረብ ቀስ በቀስ ወንጌሉንና ክርስቲያኖች በዓለም ውስጥ የሚኖሩበትን ሁኔታ ይለውጣል። በቤተ ክርስቲያን ላይ ትልቁ አደጋ የሚመጣው የክርስቲያኖችን እምነትና አኗኗር ቀስ በቀስ ከሚቀይሩ አነስተኛ ማመቻመቾች ወይም ከዓለም እንዳንለይ ከሚያደርጉ አነስተኛ የአኗኗር ስልት ለውጦች ነው።

የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) ሰይጣን ቀስ በቀስ የሐሰት ትምህርቶችንና ዓለማዊነትን በማምጣት ቤተ ክርስቲያንን ለማጥፋት ሲሞክር ያየህበትን ሁኔታ ግለጽ። ለ) የቤተ ክርስቲያን መሪዎች ለዚህ ዓይነቱ ዝንባሌ ምን ዓይነት ምላሽ መስጠት ይኖርባቸዋል? ሐ) የሐዋ. 20፡28-31 አንብብ። ጳውሎስ የኤፌሶንን ቤተ ክርስቲያን መሪዎች ያስጠነቀቀው ስለ ምንድን ነው?

ለቤተ ክርስቲያን እጅግ አደገኛ ከሆኑት ነገሮች አንዱ ዓለማዊነት ነው። ዓለማዊነት ከሁለት ገጽታዎች የሚመጣ ነው። የመጀመሪያው፥ እምነትን በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ከሚገኝ ንጹሕ ወንጌል የመለወጥ ዓለማዊነት ነው። በዚህ ፋንታ የሐሰት አስተማሪዎች ሌላ ወንጌል ያቀርቡልናል። አንዳንዶች በክርስቶስ ከማመን ላይ ሰናይ ምግባራትን ይጨምራሉ። (ለምሳሌ፥ ሰባተኛው ቀን አድቬንቲስት።) ሌሎች በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ የሌለ የተስፋ ቃል ይጨምራሉ። (ለምሳሌ፥ እግዚአብሔር ክርስቲያኖችን ሀብታም ያደርጋል የሚሉ የብልጽግና ሰባኪዎች።) ሌሎች ደግሞ የክርስቲያኖችን የሚመስል አምልኮ እያካሄዱ አንድ-በሦስት የሆነውን (ሥሉሠ ዋሕድ) እግዚአብሔርን ይክዳሉ። (ለምሳሌ፥ «ኢየሱስ ብቻ» ቤተ ክርስቲያን) ይህ ሁሉ በእውነት ላይ የተመሠረተ አምልኮ የሚፈልገውን አምላክ ደስ እንዳናሰኝ ለማደናቀፍና እምነታችንን ለመለወጥ ሰይጣን የሚያደርገው ጥረት ነው። በሐዋ. 20፥ ጳውሎስ ብዙም ሳይቆይ አባሎቻቸው ሐሰተኛ ትምህርቶችን እንደሚቀበሉ በመግለጽ የኤፌሶንን ቤተ ክርስቲያን መሪዎች አስጠንቅቋቸዋል።

ሁለተኛው ዓይነት ዓለማዊነት የሚመጣው ክርስቲያኖች የዓለማውያንን እሴቶች ተቀብለው እንደ ዓለማውያን ሲኖሩ ነው። ዓለም ወሲባዊ ኃጢአትን ታደፋፍራለች። ብዙውን ጊዜ ይህ ችግር በቤተ ክርስቲያን ውስጥ ይታያል። ዓለም ትምህርት፥ ሀብት፥ እንዲሁም ቁሳዊ ቅርስ ወሳኝ ነገሮች እንደሆኑ ታስተምራለች። ብዙ ምእመናንም ይህንኑ አስተሳሰብ ይጋራሉ።

ጳውሎስ የቆላስይስን ቤተ ክርስቲያን ጎብኝቶ አያውቅም ነበር። ነገር ግን ቤተ ክርስቲያኒቱ አንዳንድ ዓለማዊ እምነቶችን እየተቀበለች መሆኗን በሰማ ጊዜ፥ ደብዳቤ ጻፈላት። ብዙውን ጊዜ መናፍስትን ለመለየትና (1ኛ ቆሮ. 12፡10) ዓለም የምታስተምራቸውን አሳቦችና እነዚህ አሳቦች በቤተ ክርስቲያን ላይ የሚያደርሱትን ጥፋት ለመመልከት ትልቅ ጥበብን ይጠይቃል። ብዙውን ጊዜ የሐሰት ትምህርትና የዓለማዊ አኗኗር ጥፋቶች ቀስ በቀስ ወደ ሕይወታችን ውስጥ ስለሚዘልቁ ሳትንፈራገጥ ተጠብሳ እንደሞተችው እንቁራሪት ችግሩን ለይተን ለማወቅ እንቸገራለን። ጳውሎስ የሐሰት ትምህርት እሳት እየጎዳቸው እንደሆነና ወደ ጥፋትም እንደሚወስዳቸው ይነግራቸዋል። ጳውሎስ በክርስቶስ ወንድሞቹና እኅቶቹ የሆኑት ክርስቲያኖች በስሕተት ሕይወት እንዲመላለሱ አልፈለገም። ጳውሎስ የሐሰት ትምህርቶች ሊጋለጡና ሐሰትን የሚከተሉ ሰዎች ግልጽ ውሳኔ ሊሰጣቸው እንደሚገባ ተረድቶ ነበር።

በዘመናችንም ክርስቲያኖች ነን እያሉ ወደ ቤተ ክርስቲያን ሾልከው የሚገቡ ብዙ የሐሰት ትምህርቶች አሉ። የብልጽግና ወንጌል ክርስቶስ ካመንን ሀብታሞች እንደምንሆን ይናገራል። ሌሎች ደግሞ ብናምን ከሁሉም ዓይነት በሽታ እንደምንፈወስ ያስተምራሉ። እንደ ኢየሱስ ብቻ፥ የይሖዋ ምስክሮች፥ ሞርሞኖች፥ የአዲሱ ዘመን እንቅስቃሴና የመሳሰሉት ሃይማኖቶች ክርስቲያኖች ነን የሚሉትን ሰዎች እያወኩ ናቸው። ለረዥም ጊዜያት የቤተ ክርስቲያን መሪዎች ሰዎች ቤተ ክርስቲያናቶቻቸውን ለቅቀው በመሄዳቸው ሲማረሩ ቆይተዋል።

የሰይጣንን የውሸት እውነቶች በማጋለጥ በስሕተት ውስጥ የሚወድቁ ምእመኖቻችንን ለማስጠንቀቅ ጊዜው አይደለምን? መሪዎች ዛሬ ለዚህ ችግር ምላሽ የሚሰጡበትን መንገድ ለማወቅ ጳውሎስ በቆላስይሳ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ የተፈጠረውን የሐሰት ትምህርት ካስተናገደበት ሁኔታ የምንቀስመው እውቀት ይኖራል?

(ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የአዲስ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)

Leave a Reply

Discover more from

Subscribe now to keep reading and get access to the full archive.

Continue reading