ጳውሎስ ስለ ቆላስይስ ክርስቲያኖች ያቀረበው ምስጋናና ጸሎት (ቆላ. 1፡1-14)

«ይህ ታላቅ ጀማ ስብከት ወንጌል እንዳያመልጥዎ። በጉባኤው ላይ ታላቅ የፈውስ አገልጋይ ይጋበዛል። ማንኛውም ዓይነት በሽታ ያለበት ሰው ከበሽታው ይፈወሳል»። «ይህ ከአያት ቅድማያቶቻችን ያገኘነው ሃይማኖት ነው። ስለሆነም እንከተለዋለን።» «ዶ/ር እገሌ ሦስት ዲግሪዎች ያሉት ዝነኛ የዩኒቨርስቲ ሌክቸረር ነው። ትምህርቱን መስማት አለብን።»

ዓለም ቀልባችንን በሚስቡ ድምፆች የተሞላች ነች። ሁሉም እንድንሰማቸው ይፈልጋሉ። «እኛ ምሥጢር አለንና። እኛ ጥሩውንና ትክክለኛውን እናውቃለን» ይሉናል። ከላይ የተጠቀሱት ሕይወታችንን ለመለወጥና ችግሮቻችንን ለመፍታት ያስችላሉ ስለተባሉ መረጃዎች የሚናገሩ የዓለም ድምፆች ምሳሌዎች ናቸው። ኮሚኒዝም፥ ካፒታሊዝም፥ ዲሞክራሲ፥ ዝግመተ ለውጥ (ኢቮሉሽን)፥ እንዴት ሀብታም መሆን እንደሚቻል፥ እያለ ዝርዝሩ ይቀጥላል ። በእግዚአብሔር ቃል ሥር ላልሰደደ ክርስቲያን እነዚህ የዓለም ድምፆች ብዙ ግራ መጋባትን ሊፈጥሩ ይችላሉ። ብዙ ክርስቲያኖች ወደ ዩኒቨርስቲ ገብተው እግዚአብሔርን ከማያውቁ ፕሮፌሰሮች ጋር በሚፋጠጡበት ጊዜ እምነታቸውን ያጣሉ። ትምህርታቸው መልካምና ትክክለኛ ይመስላል። በመጨረሻ ግን ባአቸውን ይቀራሉ።

የውይይት ጥያቄ፡- ክርስቲያኖች መልካም በሚመስሉ ፍልስፍናዎችና ትምህርቶች ሲወሰዱ የተመለከትኸው እንዴት ነው?

የቆላስይስ ክርስቲያኖች በአካባቢያቸው የነበሩትን የአንዳንድ ታላላቅ መምህራን ትምህርቶች ይሰሙ ነበር። የብሉይ ኪዳን ሕግጋትን ለማስከበር የሚጥሩ አይሁዶችና ክፉ ቁሳዊ ባሕርያችንን ለማሸነፍ የሚያስችል ልዩ ምሥጢራዊ እውቀት አለን የሚሉ ግሪኮች ድምፆቻቸውን ከፍ አድርገው ይጮኹ ነበር። ይህ ክርስቲያኖቹን ግራ አጋባቸው። ለዚህ ችግር መፍትሔው ምን ነበር? እነዚህን ከዓለም የሚመጡ ተቃራኒ ድምፆች እንዴት መከላከል ይቻላል? ጳውሎስ ስለ ክርስቶስ ግልጽ ግንዛቤ በመጨበጥ እነዚህኑ ትምህርቶች መከላከል እንደሚቻል ያምናል። ክርስቶስ ማን ነው? ክርስቶስ በፊት፥ አሁንና ወደፊት በሕይወቴ ላይ ለውጥን የሚያስከትለው እንዴ ነው? ጳውሎስ አስፈላጊ ናቸው ብሎ ያመነባቸው ጥያቄዎች እነዚህ ብቻ ነበሩ። ሌሎች ትምህርቶች ሁሉ በክርስቶስና በክርስቶስ ላይ ባለን እምነት ላይ ተመሥርተን የምንገመግማቸው ናቸው። ጳውሎስ የቆላስይስን እማኞች ለሳቡት አወዛጋቢ ፍልስፍናዎች የሰጠው ምላሽ ክርስቶስን ማመልከትና እርሱ ብቻ የእውነት እስኳል የሆነበትን ምክንያት በዝርዝር ማብራራት ነበር።

የፈውስ አገልጋይ ወይም የአባቶቻችን እምነት የእምነታችን መሠረት ሊሆን አይችልም። ብዙ ዲግሪዎችን መሰብሰብ አንድን ሰው ከመሳሳት ነጻ አያደርገውም። እውነትን የምንገመግመው በክርስቶስና ከእርሱ ጋር ባለን ግንኙነት ላይ ተመሥርተን ነው። እግዚአብሔርም በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ስሕተት የሌለው እውቀት ሰጥቶናል። ይህም እግዚአብሔር ለሰው ልጆች ያስተላለፈው መልእክት ነው።

  1. ጳውሎስ ስለ ቆላስይስ ክርስቲያኖች እግዚአብሔርን ያመሰግናል (ቆላ.1፡1-8)።

የቤተ ክርስቲያን መሪዎች በሕይወታቸው ውስጥ ስለሚታይ መንፈሳዊ እድገትና ደህና አድርገው ለሚያከናውኗቸው ተግባራት ምእመኖቻቸውን ማመስገን ይኖርባቸዋል። ይህ ሰዎችን በማበረታታት በእድገታቸው እንዲገፉ ያግዛቸዋል። ብዙውን ጊዜ የቤተ ክርስቲያን መሪዎች ጊዜያቸውን የሚያጠፉት ምእመኖቻቸውን በመውቀስ ነው። በመንፈሳዊ ሕይወታችሁ አልተነቃቃችሁም፤ ከጸሎት ስብሰባ ቀርታችኋል ሲሉ ያማርራሉ። አንዳንድ የቤተ ክርስቲያን አባላት ወደ ቤተ ክርስቲያን በሚመጡበት ጊዜ መሪዎች የሚሰነዝሩት ትችትና ጩኸት ያሰለቻቸዋል። ጳውሎስ እንደ ገላትያ ቤተ ክርስቲያንን ሊያወድም የደረሰ ሁኔታ እስካላጋጠመው ድረስ ብዙውን ጊዜ መልእክቱን የሚጀምረው ጠንካራ ጎኖቻቸውን በማመስገን ነው።

የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) የቤተ ክርስቲያን መሪዎች ብዙውን ጊዜ ለምእመኖቻቸው አሉታዊ አመለካከት ስለሚይዙበት ሁኔታ አብራራ። ምእመናን ሁልጊዜም መሳሳታቸው ብቻ ሲነገራቸውና ለምንም ነገር ምስጋና ሳይቀርብላቸው ሲቀር ምን ዓይነት ምላሽ ይሰጣሉ? ለ) ስለ ቤተ ክርስቲያንህና ስለ ቤተ ክርስቲያንህ መሪዎች እግዚአብሔርን የምታመሰግንባቸውን አሥር ነገሮች ዝርዝር። አሁን ስለ እነዚህ ነገሮች እግዚአብሔርን በማመስገን ጸልይ። በዚህ ሳምንት ለቤተ ክርስቲያን መሪዎች ምስጋናህን የምታቀርብበትን አጋጣሚ ፈልግ።

ራሱን ሐዋርያው ጳውሎስ ነኝ ሲል ካስተዋወቀና ለቆላስይስ ቤተ ክርስቲያን ሰላምታ ካቀረበ በኋላ፥ ጳውሎስ ስለ ቆላስይስ ቤተ ክርስቲያን የሰጣቸውን ሦስት ነገሮች ይዘረዝራል። ጳውሎስ የቆላስይስን ቤተ ክርስቲያን ጎብኝቶ ስለማያውቅ እነዚህን ነገሮች የሰማው ከሥራ አጋሩና ምናልባትም በቆላስይስ ካገለገለው ከኤጳፍራ ሳይሆን አይቀርም።

ሀ. ጳውሎስ በክርስቶስ ላይ ስላላቸው እምነት እግዚአብሔርን ያመሰግናል። ይህም ድነት (ደኅንነትን) ያገኙበት እምነት ብቻ ሳይሆን፥ ክርስቶስ ለችግሮቻቸው መፍትሔ እንደሆነ በማመን የሕይወታቸው ቀዳሚ አጀንዳ አድርገው እንዲከተሉት አስችሏቸዋል።

ለ. ጳውሎስ ለቅዱሳን ሁሉ ስላላቸው ፍቅር ያመሰግናቸዋል። የሚገባትን ያህል ፍቅርና አንድነት ልታሳይ ካልቻለችው የፊልጵስዩስ ቤተ ክርስቲያን በተቃራኒ የቆላስይስ ክርስቲያኖች እርስ በርሳቸው ይዋደዱ ነበር። ፍቅራቸውም ራስን በመንከባከብና በመርዳት ላይ የተመሠረተ የራስ ወዳድነትን ፍቅር አልነበረም። ጳውሎስ ፍቅራቸው አይተው ለማያውቋቸው ክርስቲያኖች ጭምር እንደደረሰ ይነግራቸዋል።

ሐ. ጳውሎስ በሰማይ ስለተዘጋጀላቸው ተስፋ እግዚአብሔርን ያመሰግናል። የቆላስይስ ክርስቲያኖች ዓይኖቻቸውንና ልቦቻቸውን ያሳረፉት በሰማይ እንጂ በምድራዊ ሁኔታዎች ላይ አልነበረም። እነዚህ ሰዎች የክርስቶስን ምጽአት ይናፍቁ ነበር። ለክብሩ ከኖሩ እንደሚሸልማቸው በመገንዘብ ለክርስቶስ ይሠሩ ነበር።

የውይይት ጥያቄ፡– እምነት፥ ተስፋና ፍቅር የሚሉ ሦስት ቃላት በዓለም ውስጥ የሚሰበከውን ወንጌል ጠቅለል አድርገው ይገልጻሉ። ሀ) እነዚህ ሦስት ቃላት ወንጌሉን፥ ከእግዚአብሔርና ከሰዎች ጋር የሚኖረንን ግንኙነትና ሕይወታችንን የምንመራበትን ሁኔታ ጠቅለል አድርገው የሚገልጹት እንዴት ነው? ለ) እነዚህ ሦስቱ ቃላት በሕይወትህ ውስጥ እንዴት እየተገለጡ እንደሆነ አብራራ።

  1. ጳውሎስ ለቆላስይስ ክርስቲያኖች ይጸልያል (ቆላ. 1፡9-14)።

ብዙውን ጊዜ የምንጸልየው በአካል ለምናውቃቸው ሰዎች ነው። ጳውሎስ ግን በአካል ላልተገናኛቸውም ሰዎች መጸለዩ ተገቢ እንደሆነ ተገንዝቧል። በዚህ መንገድ በመንፈሳዊ እድገታቸውና አገልግሎታቸው ውስጥ ሊሳተፍ ይችል ነበር። ጳውሎስ በአካል ለሚያውቋቸው ለእነዚህ ክርስቲያኖች ስለምን ለመጸለይ እንደ ፈለገ መመልከቱ ጠቃሚ ነው።

ሀ. እግዚአብሔር ጥበብንና መንፈሳዊ ማስተዋልን በመስጠት በፈቃዱ እውቀት እንዲሞላቸው ይጸልያል። እነዚህ ክርስቲያኖች ከክርስቶስ በሚያርቋቸው እርባና ቢስ ፍልስፍናዎች ግራ ተጋብተው ነበር። ስለሆነም ጳውሎስ እግዚአብሔር በትክክለኛ እውቀት እንዲሞላቸው ይጸልያል። ጳውሎስ እግዚአብሔር ለእነዚህ ክርስቲያኖች ምን ማመን፥ እንዴት መኖር እንዳለባቸው እንዲያውቁ ከእግዚአብሔር የሆነውንና ከከንቱ ፍልስፍና መለየት፥ ጊዜያዊውንና ዘላለማዊውን ማገናዘብ እንዲችሉ እንዲያግዛቸው ይፈልጋል።

ለ. ጳውሎስ የእግዚአብሔርን ፈቃድ በማወቃቸው፥ አማኞቹ ለጌታ እንደሚገባ እንዲኖሩና በሁሉም ነገር እንዲያስከብሩት ይጠይቃቸዋል። እውነቱን ማወቅ ብቻ አይበቃም። እውነት የተሰጠው አኗኗራችንን ለመለወጥ ነው። ትክክለኛ ነገሮችን ስናስብና የእግዚአብሔርን ፈቃድ ስናውቅ እግዚአብሔር እንደሚፈልገው እንኖር ዘንድ ሕይወታችንን እናስተካክላለን። በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ የተገለጸውን የእግዚአብሔርን ፈቃድ ሳናውቅ በእግዚአብሔር መንገድ ላይ ልንመላለስ አንችልም። ነገር ግን አእምሯችን ዓለም መልካም ናቸው በምትላቸው ነገሮች ተሞልቶ ከእውነት ያርቀናል።

ሐ. ጳውሎስ ኃይልን ሁሉ ይሞሉ ዘንድ ይጸልያል። እውነቱን ብናውቅም ይህንኑ ሕይወት የምንኖርበትን ኃይል ልናጣ እንችላለን። የውስጡ ሰውነታችን ደካማ በመሆኑ ለራስ ወዳድነትና ኃጢአት ያዘነበለ ነው። ስለሆነም ጳውሎስ የቆላስይስ ክርስቲያኖች እንደሚገባቸው ለመኖር የእግዚአብሔርን ኃይል ይላበሱ ዘንድ ይጸልይላቸዋል። ይህ ኃይል ትዕግሥትን፥ ጽናትንና ደስታን ይሰጣቸዋል።

የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) ይህን ጸሎት ለራስህ፥ ለቤተ ከርስቲያንህ ምእመናንና ለቤተ እምነትህ አባላት ብትጸልይ፥ ምን ለውጥ የሚከሠት ይመስልሃል? ለ) የጳውሎስን ጸሎት ብዙውን ጊዜ ለራሳችንና ለሌሎች ከምንጸልየው ጸሎት ጋር አነጻጽር። የጳውሎስ የጸሎት ጥያቄዎች እኛ ብዙውን ጊዜ ከምንጸልይባቸው ጉዳዮች እንዴት እንደሚሻሉ እብራራ።

(ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የአዲስ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)

Leave a Reply

Discover more from

Subscribe now to keep reading and get access to the full archive.

Continue reading