የ1ኛ ጢሞቴዎስ መዋቅር
1ኛ ጢሞቴዎስ መልእክት በዋነኛነት ልምድ ያካበተ የቤተ ክርስቲያን አገልጋይ ገና ወጣት ለሆነ አገልጋይ ያስተላለፈው ምክር ነው። ጳውሎስ መንፈሳዊ ልጁና ወጣት የቤተ ክርስቲያን መሪ የሆነው ጢሞቴዎስ ንጹሕ ሕይወት ለመምራትና ቤተ ክርስቲያኒቱንም በንጽሕና ለመጠበቅ ይችል ዘንድ ሊያውቃቸው የሚገባቸውን አንዳንድ ነገሮች ያስገነዝበዋል። ምንም እንኳ በመጽሐፉ ውስጥ ግልጽ የሆነ አስተዋጽኦ ባንመለከትም፥ ጠቅለል ባለ መልኩ በሦስት ዐበይት ክፍሎች ሊከፈል ይችላል።
1) የቤተ ክርስቲያን መሪ ለሆነው ጢሞቴዎስ የተሰጠ የግል ምክር (1ኛ ጢሞ. 1)። ጳውሎስ ጢሞቴዎስ እውነተኛውን የእምነት ትምህርት ትቶ ሐሰተኛ ትምህርቶችን እንዳይከተል ወይም ክርስቶስን ከማመን ወደ ኋላ እንዳይመለስ ያስጠነቅቀዋል። በሐሰተኛ ወይም ትርጉም በሌላችው ትምህርቶች ተወስደው እምነታቸውን የጎዱ ሌሎች የቤተ ክርስቲያን መሪዎች ነበሩ። በሕይወታቸው እግዚአብሔርን የማያስከብሩና እምነታቸው የፈረሰባቸው አገልጋዮችም እንዲሁ ነበሩ።
2) የእግዚአብሔርን ቤተ ክርስቲያን ስለሚያስተዳድርበት ሁኔታ የተሰጠ ምክር (1ኛ ጢሞ. 2፡1-6፡2)። ጳውሎስ ጢሞቴዎስ እግዚአብሔርን በሚያስከብር መንገድ ቤተ ክርስቲያንን እንዴት እንደሚያስተዳድር ይመክረዋል። በዚህ ክፍል ውስጥ ጳውሎስ ስለ ጸሎት ተገቢ አለባበስ፥ የቤተ ክርስቲያን መሪዎችን ስለ መምረጥ፥ የሐሰተኛ አስተማሪዎችን ስለ መቋቋም፥ መበለቶችን መንከባከብና ስለ ባሮች ትኩረት ሰጥቶ አስተምሯል።
3) የቤተ ክርስቲያን መሪ ለሆነው ጢሞቴዎስ የተሰጠ የግል ምክር (1ኛ ጢሞ. 6፡3-21)። ጳውሎስ አሁንም የቤተ ክርስቲያንን መሪ ውጤታማነት ሊያጠፉት ስለሚችሉት ነገሮች ጢሞቴዎስን በማስጠንቀቅ የመጀመሪያ መልእክቱን ይደመድማል። በገንዘብ ፍቅር እንዳይነደፍና ሕይወቱን በእግዚአብሔር ዓይኖች ፊት በንጽሕና እንዲጠብቅ ይነግረዋል።
የ1ኛ ጢሞቴዎስ አስተዋጽኦ
- የቤተ ክርስቲያን መሪ ለሆነው ጢሞቴዎስ የተሰጠ የግል ምክር (1ኛ ጢሞ. 1)።
ሀ) ጳውሎስ ጢሞቴዎስ የወንጌልን እውነት እንዲጠብቅ ያስጠነቅቀዋል (1ኛ ጢሞ. 1፡1-11)።
ለ) ጳውሎስ ወንጌሉ ክርስቶስ ለኃጢአተኞች ካለው ፍቅር እንደሚመነጭ የራሱን የግል ተሞክሮ በመግለጽ ያብራራል (1ኛ ጢሞ. 1፡12-17)።
ሐ) ጳውሎስ ጢሞቴዎስ በኃጢአት እንዳይወድቅ ትምህርቱንና የግል ሕይወቱን ንጽሕና እንዲጠበቅ ይመክረዋል (1ኛ ጢሞ. 1፡18-21)።
- የእግዚአብሔርን ቤተ ክርስቲያን ስለ ማስተዳደር የተሰጠ ምክር (1ኛ ጢሞ. 2፡1-6፡2)።
ሀ) አንድ የቤተ ክርስቲያን መሪ ምእመናን የጸሎት ሰዎች እንዲሆኑ ያስተምራል (1ኛ ጢሞ. 2፡1-8)።
ለ) የቤተ ክርስቲያን መሪ ሴቶች በቤተ ክርስቲያን ውስጥ ምሳሌያዊ ሕይወት እንዲኖሩ ይረዳቸዋል (1ኛ ጢሞ. 2፡9-15)።
ሐ) የቤተ ክርስቲያን መሪ ምእመናን ሽማግሌዎችንና ዲያቆናትን በጥንቃቄ እንዲመርጡ ይረዳቸዋል (1ኛ ጢሞ. 3)።
መ) የቤተ ክርስቲያን መሪ የሐሰት አስተማሪዎችን ለመከላከል የእምነትን እውነት ይጠብቃል (1ኛ ጢሞ. 4)።
ሠ) የቤተ ክርስቲያን መሪ ቤተ ክርስቲያኒቱ መበለቶችን የምትንከባከብበትን መንገድ እንድታዘጋጅ ይረዳል (1ኛ ጢሞ. 5፡1-16)።
ረ) የቤተ ክርስቲያን መሪ ያለ አድልዎ በሚያበረክተው አገልግሎት በምእመናን ሊከበር ይገባዋል (1ኛ ጢሞ. 5፡17-24)።
ሰ) የቤተ ክርስቲያን መሪ ሠራተኞች (ባሪያዎች) ከአሠሪዎቻቸው (ከጌቶቻቸው) ጋር ተገቢ ግንኙነት እንዲኖራቸው ይረዳል (1ኛ ጢሞ. 6፡1-2)።
- የቤተ ክርስቲያን አገልጋይ ለሆነው ጢሞቴዎስ የተሰጠ ግላዊ ምክር (1ኛ ጢሞ. 6፡3-21)
ሀ) ጢሞቴዎስ ራሱን ከገንዘብ ፍቅር ማራቅ ያስፈልገው ነበር (1ኛ ጢሞ. 6፡3-10)
ለ) ጢሞቴዎስ በሰዎች ሁሉ ፊትና በእግዚአብሔር ንጹሕ ሆኖ ለመገኘት ይችል ዘንድ ሕይወቱንና እምነቱን መጠበቅ ያስፈልገው ነበር (1ኛ ጢሞ. 6፡11-21)።
(ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የአዲስ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)