የቤተ ክርስቲያን መሪ ቤተ ክርስቲያን መበለቶችን የምትረዳበትን መንገድ ማዘጋጀት ይኖርበታል (1ኛ ጢሞ. 5፡1-16)

ጳውሎስ አንድ የቤተ ክርስቲያን መሪ ራሱንና ምእመናኑን እንዴት ከሐሰተኛ ትምህርት እንደሚጠብቅ ካብራራ በኋላ፥ በዝርዝር ጉዳዮች ላይ ያተኩራል። እነዚህም ዝርዝር ጉዳዮች ቤተ ክርስቲያን በማኅበረሰብ ውስጥ መልካም ምሳሌና ምስክርነት እንድትሰጥ የሚያግዛት ናቸው።

1) መሪዎች ከሁሉም የማኅበረ ምእመናን አባላት ጋር በሚያደርጓቸው ግንኙነቶች ጥንቃቄ ማድረግ አለባቸው። መሪዎች ብዙ ትምህርት ቢኖራቸው እንኳን፥ በዕድሜ የሚበልጧቸውን ሰዎች ማክበር አለባቸው። ከቅንዓትና ጥርጣሬ ርቀው፥ የዕድሜ እኩዮቻቸውን እንደ ወንድሞቻቸውና እኅቶቻቸው መቁጠር አለባቸው። ከተቃራኒ ጾታ ጋር በሚኖራቸው ግንኙነት፥ አንድ መሪ ቤተሰባዊ ዝምድና ማድረግ አለበት። ይህም መሪው በኃጢአት እንዳይወድቅ ወይም ደግሞ ሌሎች ሰዎች የተሳሳተ ግምት እንዳይሰጡት ይረዳዋል።

2) መሪዎች በቤተ ክርስቲያን ውስጥ የሚገኙትን መበለቶች በጥንቃቄ መንከባከብ አለባቸው። በጥንት ማኅበረሰቦች ውስጥ፥ መበለቶች ብዙ ችግሮች ነበሩባቸው። መበለቶች የቤተሰቡ አካል ስለማይሆኑ፥ ወላጆቻቸው ከሞቱ በኋላ ከወንድሞቻቸውና ከእኅቶቻቸው ምንም ዓይነት እርዳታ አያገኙም ነበር። የሞቱ ባሎቻቸውም ዘመዶች አያስጠጓቸውም ነበር። መበለቶች ብዙውን ጊዜ ትናንሽ ልጆቻቸውን የሚንከባከቡበትን መንገድ አያገኙም ነበር። እነዚህ ሰዎች ምንም ዓይነት መብት ስላልነበራቸው መሬታቸውን፥ ቤታቸውን የመነጠቅ አደጋ ይደርስባቸው ነበር። በብሉይ ኪዳን ዘመን እግዚአብሔር መበለቶችን ስለመንከባከብ ልዩ ትእዛዝ ሰጥቷል። ጳውሎስ ለጢሞቴዎስ መበለቶችን ስለ መንከባከብ የሚከተለውን አዟል።

ሀ) አማኝ የሆኑ የቤተሰብ አባላት የቤተ ክርስቲያንን እርዳታ ከመጠበቅ ይልቅ መበለት የሆኑ ዘመዶቻቸውን ፍላጎቶች ማሟላት ያስፈልጋቸው ነበር። መበለት የሆነች ዘመዱን ወይም እናቱን ለመንከባከብ የማይፈልግ ሰው ከክርስቲያናዊ ባህሪ ውጪ እየተመላለሰ መሆኑ ተገልጾአል። እንዲህ ዓይነቱ ሰው ‘ከዓለማዊ የከፋ በመሆኑ’፥ የቤተ ክርስቲያን የቅጣት እርምጃ ሊወሰድበት ይገባል። ከቤተሰብ አባሎቿ መካከል ረዳት የለሸ መበለት መኖሯን የምታውቅ ሴት በራስ ወዳድነት የእርዳታ እጆቿን ከመሰብሰብ ወይም ቤተ ክርስቲያን እንድትረዳት ከመጠበቅ ይልቅ መበለቷን መንከባከብ ይገባታል።

ለ) ቤተ ክርስቲያን ምንም ዓይነት ረዳት የሌላቸውን ክርስቲያን ሴቶች የመንከባከብ ኃላፊነት አለባት።

ሐ) በቤተ ክርስቲያን መዝገብ ውስጥ ሰፍረው እርዳታ ሊያገኙ የሚችሉት ያረጁ (ከ 60 ዓመት በላይ) እና ረዳት የለሽ የሆኑ መበለቶች ብቻ ሊሆኑ ይገባል። ጳውሎስ እዚህ ጋ ለማስተላለፍ የፈለገው መልእክት ቤተ ክርስቲያን ወጣት ሴቶች ለችግር እንዳይጋለጡ ወይም በወሲብ ኃጢአት እንዳይወድቁ እንደገና የሚያገቡበትን መንገድ ማመቻቸት እንዳለባት ነው። በዕድሜ የገፉ መበለቶች ወጣት ሴቶችን በመርዳት በመንፈሳዊነት እንዲያድጉና ለምሳሌያዊነት የሚበቁ እናቶችና ሚስቶች እንዲሆኑ መርዳት አለባቸው። እነዚህ በዕድሜ የገፉ መበለቶች በችግር ውስጥ ያሉትን ሰዎች በመርዳቱ ተግባር ላይ ማተኮር ይኖርባቸዋል። የተመቻቸ ሕይወት ከመፈለግ ወይም ባሎቻቸውን በማጣታቸው ከማጉረምረም ይልቅ በተለያዩ ጉዳቶችና ችግር ውስጥ ያሉትን ሰዎች በመርዳቱ ላይ አጽንኦት መስጠት ያስፈልጋቸዋል።

መ) ወጣት መበለቶች እርዳታ የሚያገኙ መበለቶች መዝገብ ውስጥ መስፈር የለባቸውም። መበለቶች በቤተ ክርስቲያን መዝገብ ውስጥ ሰፍረው እርዳታ ከሚያገኙባቸው መንገዶች አንዱ በቤተ ክርስቲያን ውስጥ ለማገልገል መሐላ መፈጸማቸው ሳይሆን አይቀርም። (ድሆች ሳይሠሩ እርዳታ ማግኘት እንደሌለባቸው ከብሉይ ኪዳንና ከጥንታዊ ቤተ ክርስቲያን ምሳሌነት እንረዳለን) ሙሉ ለሙሉ ክርስቶስን ለማገልገል ይችሉ ዘንድ ከእንግዲህ ላለማግባት ቃል ይገባሉ። ነገር ግን እንደገና የማግባትና ከባል-አልባነት ነቀፋ የመላቀቅ ፍላጎት አለባቸው። በመሆኑም ቃል ኪዳናቸውን አፍርሰው ያገባሉ። ወይም ደግሞ ከአንዱ ቤት ወደ ሌላው ቤት እየዞሩ ሰው በማማትና ውጤታማ ተግባር ባለማከናወን ለስንፍና ይጋለጣሉ። ስለሆነም፥ ጳውሎስ ወጣት ሴቶች እንዲያገቡ፥ ልጆች እንዲወልዱና የቤት እመቤትነትን ተግባር እንዲወጡ አዝዟል።

ጳውሎስ ሚስቶቻቸው የሞቱባቸው ሰዎች ስለሚረዱበት መንገድ የሰጠው ማብራሪያ የለም። ስለሆነም እንደገና የማግባት ወይም በቤተሰቦቻቸው የመረዳት ግዴታ ይኖርባቸዋል ማለት ነው።

ከዚህ ትምህርት ውስጥ ቤተ ክርስቲያን ከማኅበረ ምእመናኑ መካከል ችግር ያለባቸውን ሰዎች የመርዳት ኃላፊነት እንዳለባት የሚያስገነዝብ መሠረታዊ አሳብ እንመለከታለን። ቤተ ክርስቲያን ድሆችን ማለትም ወላጅ የሌላቸውን ልጆች፥ መበለቶች፥ ሥራ የሌላቸውን፥ ወዘተ… የመርዳት ኃላፊነት የለብኝም ልትል አትችልም። እነዚህ መመሪያዎችና በ1ኛ ተሰሎንቄ ውስጥ የሚገኙ ሌሎች ምንባቦች እንደሚያሳዩት፥

ሀ) አንድ አማኝ በመጀመሪያ የራሱን ፍላጎቶች ለማሟላት መሻት አለበት። ለቤተ ክርስቲያን ሸክም ላለመሆን ሲሉ ከደረጃቸውም ዝቅ ብለው እንኳን የራሳቸውን ገቢ የሚያገኙበትን መንገድ መፈለግ ይኖርባቸዋል። ቤተ ክርስቲያን ሥራ የሚያገኙበትን መንገድ በመፈለግ ወይም ሥልጠና በመስጠት ድሆችን መርዳት ትችላለች። ነገር ግን ለመሥራት የማይፈልጉትን ድሆች ለረጅም ጊዜ ገንዘብ እየሰጠች ማኖር የለባትም። ብዙውን ጊዜ ለድሆች ገንዘብን መስጠቱ የጥገኝነትን መንፈስ ስለሚያበረታታ ጎጂ ነው። በመሆኑም ገንዘብ ከመስጠት ይልቅ የሥራ ዕድል መፍጠር ጠቃሚ ነው።

ለ) ዝምድና ያላቸው ሰዎች የተራራቀ ቢሆንም እንኳን የቤተ ክርስቲያንን እርዳታ ከመጠበቅ ይልቅ ለቤተሰባቸው አባላት እርዳታ ማድረግ ይኖርባቸዋል። ስለሆነም ዕጓለ ማውታዎችን፥ ድሆችን፥ መበለቶችን መርዳቱ በቀዳሚነት የዘመዶቻቸው ተግባር ይሆናል።

ሐ) ስለሆነም ቤተ ክርስቲያን ረዳት ለሌላቸው ቤተሰብ ትሆንላቸዋለች ማለት ነው። በቤተ ክርስቲያን ይህንኑ ተግባር የምታከናውንበት መንገድ ከባህል ባህል ይለያያል። በመሆኑም ዕጓለ ማውታዎችን በአማኝ ቤተሰቦች ውስጥ ማኖር፥ ለመበለቶች እርዳታ ማድረግና ሥራ ለሌላቸው ድሆች ጊዜያዊ መፍትሔዎችን መስጠት ቤተ ክርስቲያን ከምታከናውናቸው ተግባራት ጥቂቶቹ ሊሆኑ ይችላሉ። በቤተ ክርስቲያን ውስጥ የሚገኙ ቤተሰቦች ራስ ወዳድነትን በማስወገድ ለሥጋዊ ቤተሰቦቻቸው የሚያደርጉትን ያህል እንክብካቤ ለመንፈሳዊ ቤተሰቦቻቸውም ሊያደርጉ ይገባል።

የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) ቤተ ክርስቲያንህ የድሆችን፥ የዕጓለ ማውታዎችንና የመበለቶችን ፍላጎቶች ለማሟላት ምን እያደረገች ነው? ለ) ቤተ ክርስቲያንህ ይህንኑ ተግባር በአጥጋቢ ሁኔታ እንድትወጣ ክርስቶስ ወይም ጳውሎስን ምን ዓይነት ትእዛዛትን የሚሰጡ ይመስልሃል?

(ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የአዲስ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)

Leave a Reply

Discover more from

Subscribe now to keep reading and get access to the full archive.

Continue reading