፩. የቤተ ክርስቲያን መሪ ሠራተኞች (ባሪዎች) ከአሠሪዎቻቸው (ከጌቶቻቸው) ጋር ተገቢው ግንኙነት እንዲኖራቸው መርዳት አለባቸው (1ኛ ጢሞ. 6፡1-2)።
በታሪክ ውስጥ እጅግ አስቸጋሪ ከነበሩት ውስጥ አንዱ በሠራተኞችና አሠሪዎቻቸው መካከል ያለውን ችግር ለመፍታት ቤተ ክርስቲያን ሊኖራት የሚገባውን ሚና መወሰኑ ነው። በጳውሎስ ዘመን ይህ ግንኙነት በአብዛኛው በባሪያና በጌታ መካከል የሚታይ ነበር። በመጀመሪያው ምእተ ዓመት በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ ባሪያዎች ነበሩ። ሃብታሞችና ነጋዴዎችም የባሪያ አሳዳሪዎች ነበሩ። ከቀድሞዎቹ አማኞች አብዛኞቹ ባሪያዎች ነበሩ። እንደ ፊልሞናና አናሲሞስ ባሪያውም ጌታውም ክርስቲያኖች የሆኑበት አጋጣሚዎችም ነበሩ። በዚህ ሰዎችን በባርነት በማሳደሩ አስከፊ ተግባር የክርስቲያኖች ምላሽ ምን ሊሆን ይገባል? ክርስቲያን የሆኑ ባሮች ነፃ ለመውጣት መታገል ያስፈልጋቸዋል? ለክርስቲያኖች ባሪያ ማሳደሩ ስሕተት ነው? የትኞቹም የመጽሐፍ ቅዱስ ጸሐፊዎች የባሪያ አሳዳሪነትን ተግባር ለማስወገድ ቀጥተኛ የሆነ አሳብ አላቀረቡም። ነገር ግን ሰዎች ሁሉ በእግዚአብሔር ፊት በቤተ ክርስቲያን እኩል እንደሆኑ በመግለጽ የባሪያ አሳዳሪነትን ልምምድ አለመደገፋቸውን አሳይተዋል። ሰዎች ሁሉ ሰብአዊ ክብራቸው ተጠብቆ ሊኖሩ ይገባልና። እንደ አለመታደል ሆኖ በታሪክ ሁሉ ክርስቲያኖች የባሪያ አሳዳሪነት ምን ያህል አስከፊ እንደሆነ ሳይገነዘቡ ቆይተዋል። በምዕራቡ ዓለም፥ ክርስቲያኖች እስከ ዛሬ አንድ መቶ ዓመታት ድረስ ባሪያዎች ነበሩዋቸው። ዛሬም እንኳን በአንዳንድ የዓለም ክፍሎች የባሪያ አሳዳሪነት እንደ ቀጠለ ይገኛል።
ጳውሎስ ጢሞቴዎስ የቤተ ክርስቲያን መሪዎች ክርስቲያን ባሪያዎች በባሪያ አሳዳሪነት ሥርዓት ላይ እንዳያምጹ እንዲነግሯቸው አሳስቧል። ይልቁንም ጌቶቻቸውን ማክበርና ማገልገል ነበረባቸው። ጌታቸው አማኝ ስለሆነ ብቻ የተለየ አያያዝ ወይም አነስተኛ ሥራ እንዲሰጣቸው መጠየቅ አያስፈልጋቸውም ነበር። ነገር ግን በሥራቸው በጌታ ወንድማቸው የሆነውን ሰው እንደሚረዱት በማሰብ፥ የበለጠ ተግተው ሊሠሩ ይገባ ነበር። ምንም እንኳ ዛሬ በብዙ አገሮች ባሪያ አሳዳሪነት ባይኖርም፥ ከዚህ ግንኙነት የመነጩትን መርሆዎች ለሠራተኛና አሠሪ መጠቀም ይቻላል። ክርስቲያን ሠራተኛ አሠሪውን ማክበር ይኖርበታል። ምንም እንኳ አሠሪው ራስ ወዳድና የማይመች ቢሆንም ይህንኑ ማድረግ ይኖርበታል። መጽሐፍ ቅዱስ እንድ ሠራተኛ አሠሪውን እንዲቀናቀን፥ እንዲቃወም ወይም እንዲጠላ አይፈቀድለትም። እንዲሁም አሠሪው አማኝ በመሆኑ ብቻ ሠራተኛው የተለየ አስተያየት እንዲደረግለት ወይም የሥራ ጫና እንዲቀነስለት መጠበቅ የለበትም። ነገር ግን በጌታ ወንድሙ የሆነውን አሠሪውን ለመርዳት የበለጠ ተግቶ መሥራት ይችላል። ሰዓቱን ጠብቆ ተግባሩን የማያከናውን ሰነፍ ሠራተኛ የክርስቶስን ስም ያሰድባል። እግዚአብሔር ልጆቹ ተግተው እንዲሠሩና የሥራ ሰዓታቸውን እንዳያዛንፉ፥ ብሎም አሠሪያቸውን እንዲያከብሩ ይፈልጋል። አሠሪያቸው ክርስቲያን ቢሆንም ባይሆንም ይህንኑ ማድረግ ይኖርባቸዋል።
በተጨማሪም እግዚአብሔር አሠሪዎች ሠራተኞቻቸው በእግዚአብሔር አምሳል የተፈጠሩ ሰዎች መሆናቸውን እንዲገነዘቡ ይፈልጋል። ሠራተኛው አማኝ ከሆነ ደግሞ ሁለቱም የአንድ መለኮታዊ ቤተሰብ አባላት መሆናቸውን መገንዘቡ ተገቢ ነው። ስለሆነም እግዚአብሔር አሠሪው ሠራተኞቹ ያለ አድልዎና ፍትሐዊ በሆነ መንገድ ማስተዳደር ይኖርበታል። ሠራተኞቹ ቤተሰባቸውን ማስተዳደር ይችሉ ዘንድ ተመጣጣኝ ክፍያ ሊደረግላቸው ይገባል።
የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) ክርስቲያን ሠራተኞች ለአሠሪዎቻቸው እንዲህ ዓይነት አመለካከት ያላቸው ይመስልሃል? ለምን? የጳውሎስን ትምህርት ከተከተሉ የሥራቸው ሁኔታ እንዴት እንደሚለወጥ ግለጽ። ለ) አብዛኞቹ ክርስቲያን አሠሪዎች መጽሐፍ ቅዱስ የሚያስተምረውን አመለካከት የሚከተሉ ይመስልሃል? ለምን? እግዚአብሔር በሚፈልገው መንገድ ሠራተኞቻቸውን ለመርዳት ባህሪያቸው እንዴት ሊለወጥ እንደሚገባ ግለጽ።
፪. የቤተ ክርስቲያን መሪ ለሆነው ጢሞቴዎስ የተሰጠ የግል ምክር (1ኛ ጢሞ. 6፡3-21)
ጳውሎስ በመልእክቱ ማጠቃለያ ላይ ጢሞቴዎስን እንደ ምሳሌ በመውሰድ፥ ብዙውን ጊዜ መሪዎች በግላዊ ሕይወታቸው የሚሸነፉባቸውን ነገሮች ይጠቁማል። ሁሉም የቤተ ክርስቲያን መሪዎች እነዚህን አስቸጋሪ ነገሮች በመረዳት ሕይወታቸውን በጥንቃቄ መጠበቅ ይኖርባቸዋል። ይህም የክርስቶስን ስም እንዳያሰድቡ ይረዳቸዋል።
- ጢሞቴዎስ ራሱን ከገንዘብ ፍቅር መጠበቅ አለበት (1ኛ ጢሞ. 6፡3-10)።
ጳውሎስ ይህንኑ ስለ ገንዘብ የሚኖር የተሳሳተ አመለካከት ማብራራት የጀመረው አሁንም ስለ ሐሰተኛ አስተማሪዎች በመጥቀስ ነው። ጳውሎስ የቤተ ክርስቲያን መሪዎች የሐሰተኛ አስተማሪዎችን ባሕርያት በመረዳት ቤተ ክርስቲያናቸውን ሊጠብቁ የሚችሉባቸው በርካታ መንገዶች እንዳሉ ያስረዳል። በመጀመሪያ፥ ሐሰተኛ አስተማሪዎች ሐሰተኛ አስተምህሮዎችን ያቀርባሉ። ማለትም ሚዛናዊ ያልሆኑና መጽሐፍ ቅዱስ ከሚያስተምራቸው እውነቶች ሁሉ ጋር የማይጣጣሙ አሳቦችን ከእግዚአብሔር ቃል እያወጡ ያስተምራሉ። ሁለተኛ፥ ክርስቲያኖች የእግዚአብሔርን ቃል በማጣቀስ መሳሳታቸውን በሚያሳዩዋቸው ጊዜ ለመቀበል ፈቃደኞች አይሆኑም። ብዙውን ጊዜ ሐሰተኛ አስተማሪዎች እናውቃለን በሚሉት አሳብ ስለሚኩራሩ የሌሎችን ትምህርት ራሳቸውን ዝቅ አድርገው ለመቀበል አይፈልጉም። ሦስተኛ፥ አንድነትን ከማበረታታት ይልቅ በቤተ ክርስቲያን ውስጥ ሰዎችን ይከፋፍላሉ። አራተኛ፥ ሐሰተኛ አስተማሪዎች የሌሎችን መልካም ስም ያጎድፋሉ፤ በተለይም ከትምህርታቸው ጋር የማይስማሙትን የቤተ ክርስቲያን መሪዎች ስም ለማጥፋት ይጣጣራሉ። አምስተኛ፥ ለገንዘብና ለግል ጥቅማ ጥቅሞች ከፍተኛ ፍላጎት አላቸው። ሐሰተኛ አስተማሪዎች መሪዎች ለመሆን ይፈልጋሉ። በዚህም የገንዘብ ወይም በሰዎች የመከበር ጥቅም ለማግኘት ይሻሉ።
የውይይት ጥያቄ፡- በቤተ ክርስቲያንህ ላይ ችግር ያስከተሉትን አንዳንድ የሐሰት አስተማሪዎች ግለጽ። እነዚህ ባሕርያት በምን መልኩ ተገልጸዋል?
ጳውሎስ የገንዘብ ፈተና ምን ያህል አደገኛ እንደሆነ ተገንዝቧል። በተለይም ገንዘብ እየተከፈላቸው ለሚያገለግሉ መሪዎች ይህ ከባድ ፈተና ነበር። ጳውሎስ ይህን ሲል ገንዘብና ብልጽግና ክፉ ነው ማለቱ አይደለም። ነገር ግን ገንዘብን ከመጠን በላይ መሻት ለመንፈሳዊ ዕድገታችንና አገልግሎታችን አደገኛ መሆኑን ያስተምራል። አንድ ጊዜ ምን ያህል ገንዘብ ቢኖርህ ያረካሃል የሚል ጥያቄ ብዙ ሚሊዮን ብሮች ለነበሩት ግለሰብ ቀርቦለት ነበር። ሀብታሙም ሰውዬ፥ አንድ ሚሊዮን ቢጨመርልኝ ሲል መልሷል። የሰው ልጅ እግዚአብሔር ምንም ያህል ቢባርከውም ሌላ ነገር ለመጨመር ይፈልጋል።
ከዚሁ በተቃራኒ ጳውሎስ ጢሞቴዎስና የቤተ ክርስቲያን መሪዎች በሙሉ ፈሪሃ እግዚአብሔር ያለበትን እርካታ ንብረታቸው እንዲያደርጉ አሳስቧል። ፈሪሃ እግዚአብሔራዊ ሕይወት እንዲኖረን መጣር አለብን። መሪዎች ባላቸው ነገር መርካትን መማር አለባቸው። ሁልጊዜም ተጨማሪ ሀብት ለማግኘት መጣሩ ሞኝነት ነው። ምክንያቱም የኋላ ኋላ በምንሞትበት ጊዜ አንድም ነገር ይዘን አንሄድምና፡፡ የገንዘብ ፍቅር ደግሞ ለሌሎች ኃጢአቶች ይመራል። ገንዘብ ያላቸውም ሰዎች ለኩራት ኃጢአት ቅርብ ናቸው። አንድ ሰው ቶሎ ገንዘብ ለማካበት በሚፈልግበት ጊዜ ጉቦ ለመስጠት ወይም ለማጭበርበር ይገደዳል። የቤተ ክርስቲያን መሪዎች ከመባ ወይም ከውጪ ድርጅቶችና ለልማት ከሚመጣ ገንዘብ ለመስረቅ ይፈተናሉ። የቤተ ክርስቲያን መሪዎች ባላቸው መርካትና እግዚአብሔር የሚያስፈልጋቸውን ሁሉ እንደሚያሟላላቸው መተማመን አለባቸው። እግዚአብሔር ለሰጣቸው በረከቶች ሊያመሰግኑትና እነዚህኑ በረከቶች እግዚአብሔርን በሚያስከብር መንገድ ለመጠቀም መጣር አለባቸው (1ኛ ጢሞ. 6፡17-19)።
የውይይት ጥያቄ፡– የገንዘብ ፍቅር የቤተ ክርስቲያንን መሪ ሕይወት ሲያበላሽ ያየህበትን ሁኔታ ግለጽ።
- ጢሞቴዎስ ሕይወቱንና እምነቱን በመጠበቅ በእግዚአብሔርና በሰዎች ፊት በንጽሕና መመላለስ ይኖርበታል (1ኛ ጢሞ. 6፡11-21)።
ለመሪዎች ሁለተኛው ዋንኛ ፈተና ወሲባዊ ንጽሕና ነው። በመሆኑም ጳውሎስ ጢሞቴዎስ በዚህ ረገድ ሕይወቱን በንጽሕና እንዲጠበቅ ያዝዘዋል። የትኛውም ክፉ ነገር በተለይም የወሲብ ኃጢአት ለሕይወቱ አደገኛ ስለሆነ በተቻለው አቅም መሸሽ ይኖርበታል። በተቃራኒው ጢሞቴዎስ ጽድቅን፥ ፈሪሃ እግዚአብሔርን፥ እምነትን፥ ፍቅርን፥ ትዕግሥትንና ገርነትን እንዲከተል ተናግሯል። በየዕለቱ እነዚህ ባሕሪያት በሕይወቱ ውስጥ እያደጉ እንዲሄዱ ማድረግ ያስፈልገዋል። ጳውሎስ ጢሞቴዎስ በውሸት እውቀት ከተባለ ለዓለም ከሚመች ከከንቱ መለፍለፍና መከራከር በመራቅ ጊዜውን በአግባቡ እንዲጠቀም ይመክረዋል። አንድ ቀን በኢየሱስ ክርስቶስ ፊት በመቅረብ ሕይወቱን ስለመራበት መንገድ እንደሚገመገምም ያስጠነቅቀዋል። ጢሞቴዎስ በዚያን ጊዜ ለማፈር አይፈልግም ነበር።
የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) የቤተ ክርስቲያን መሪዎች በመንፈሳዊ ሕይወታችው ለማደግ ቢፈልጉና ክርስቶስ አመራራቸውንም ሆነ ሕይወታቸውን እንደሚገመግማቸው ቢያስታውሱ፥ የመሪነት አገልግሎታቸው እንዴት የሚለወጥ ይመስልሃል? ለ) አሁኑኑ በክርስቶስ ፊት ቀርበህ ብትገመግም የምታፍርባቸው ጉዳዮች ምን ምንድን ናቸው? ስለ እነዚህ ጉዳዮች ንስሐ በመግባት መንገድህን ቀይር። መንፈስ ቅዱስ እንዲቀድስህና እግዚአብሔርን ሚያስደስት ሕይወት እንዲኖርህ እንዲያግዝህ ጸልይ።
(ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የአዲስ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)