ኢየሱስ ክርስቶስ፣ የአዲስ ኪዳን ሊቀ ካህናት (ዕብ 8፡1-13)

ጸሐፊው መልእክቱን ካቀረበባቸው ልዩ መንገዶች አንዱ አንድን አዲስ አሳብ ካቀረበ በኋላ መለስ ብሎ በዝርዝር ማቅረቡ ነው። ስለ ክርስቶስ ሊቀ ካህንነት በዝርዝር ከመጻፉ በፊት ጸሐፊው በብዙ ምዕራፎች ውስጥ ክርስቶስ ሊቀ ካህናት መሆኑን ገልጾአል (ዕብ. 2፡17-18፤ 4፡14-16)። በዕብራውያን 8፡1-6 ደግሞ ሁለት አዳዲስ አሳቦችን ያቀርብልናል። እነዚህንም ወደ በኋላ ዘርዘር አድርጎ ያብራራቸዋል።

ሀ) ክርስቶስ ሊቀ ካህናት እንደ መሆኑ፥ በኢየሩሳሌም ከሚገኘው ቤተ መቅደስ በተሻለ ሰማያዊ ቤተ መቅደስ ውስጥ ያገለግላል። ሊቀ ካህናት አገልግሎታቸውን የሚያበረክቱት በቤተ መቅደሶች ውስጥ ነበር። በመሆኑም አይሁዶች ቤተ መቅደሱ የሚሻል ከሆነ፥ አገልግሎቱ የላቀ እንደሚሆን ያስቡ ነበር። ስለሆነም፥ ጸሐፊው ሁለት ዓይነት ሊቃነ ካህናት የሚያገለግሉባቸውን ሁለት ቤተ መቅደሶችን ያነጻጽራል። እነዚህም ሁለት ዓይነት ሊቃነ ካህናት የሚያገለግሉባቸው ነበሩ። አይሁዳውያን ሊቃነ ካህናት የሚያገለግሉበት የኢየሩሳሌሙ ቤተ መቅደስ በሰማይ ያለው ቤተ መቅደስ ግልባጭ (ሞዴል) ነበር። ክርስቶስን የሚያገለግለው በዚሁ ቅዱስና ግልባጭ ባልሆነው ቤተ መቅደስ ውስጥ ነበር። ይኸው ክርስቶስ ከአይሁዳውያን ሊቃነ ካህናት እንደሚበልጥ የሚያመለክት መስፈርት ነው። ጸሐፊው በዕብ 9፡1-10 ይህንኑ አሳብ ሰፋ አድርጎ ያብራራዋል።

ለ) ከሊቀ ካህናት አገልግሎቶች አንዱ መሥዋዕቶችን ማቅረብ በመሆኑ፥ ክርስቶስ ከእንስሳት መሥዋዕቶች የሚበልጥ መሥዋዕት አቅርቧል። በመስቀል ላይ ራሱን በመሞት አቅርቧል። ይህ ዕብ. 8፡3 ፍንጭ የተሰጠው ሲሆን፥ ዕብ 9፡11-10፡18 በሰፊው ተብራርቷል። ይኸው አሳብ ቀደም ሲል በዕብ 7፡26-27 ቀርቧል።

ጸሐፊው የኢየሱስ አገልግሎት ከአሮን አገልግሎት እንዴት እንደሚበልጥ ከማብራራቱ በፊት የኢየሱስን ታላቅነት ለማሳየት ቀጣዩን ዐቢይ ርእሰ ጉዳይ ይጠቅሳል። ካህናት ስለሚያገለግሉበት ሁኔታ ከእግዚአብሔር ዘንድ ትእዛዛቱን ስለተቀበሉ፥ ጸሐፊው ለሁለቱ ዓይነት ሊቃነ ካህንነት የሚሰጡትን ትእዛዛት ወይም የሚሰጠውን የአገልግሎት መሠረቶች ያነጻጽራል። ጸሐፊው ብሉይና አዲስ ኪዳናትን ያነጻጽራል። አሮጌው ኪዳን እንደ ወደቀ አምልኮ ወይም የመንግሥተ ሥርዐት ነበር። በዚያው አሮጌ የአምልኮ ሥርዓት ውስጥ አምልኮውን የሚመራው አሮን ነበር። አሁን ግን እግዚአብሔር «አዲስ ኪዳን» ሰጥቶናል። ይህም የአዲሱ የአምልኮ ሥርዓት ነው፡፡ አንድ መንግሥት ወድቆ ሌላው ሰሚተካበት ጊዜ፥ በአመዛኙ የሕገ መንግሥት ለውጥ ይደረጋል። ይህም ለአዲሱ መንግሥት አሥራር በሚያመች መልኩ የሚቀረጽ ይሆናል። በተመሳሳይ መንገድ፥ አዲስ ኪዳን በሚመሠረትበት ጊዜ አዲስ ሥርዓትና አዲስ ሊቀ ካህናት አስፈላጊዎች ይሆናሉ። ይህም አዲሱን የአምልኮ መንገድ ለማካሄድ ያስችላል። እግዚአብሔር ይህንን አዲስ ሥርዐት «አዲሱ» ኪዳን ብሎ መጥራቱ የብሉይ ኪዳን የአምልኮ ሥርዐት እንዳከተመለት ያመለክታል። ይህም በ70 ዓመተ ምሕረት ሮማውያን የኢየሩሳሌምን ቤተ መቅደስ በደመሰሱበት ወቅት ተግባራዊ ሆኗል።

ጸሐፊው፥ «አሁን ግን በሚሻል ተስፋ ቃል በተመሠረተ በሚሻል ኪዳን ደግሞ መካከለኛ እንደሚሆን፥ በዚያ ልክ እጅግ የሚሻል አገልግሎት አግኝቷል።» ይላል። አይሁዳውያን ክርስቲያኖች በብሉይ ኪዳን ሥር ወደሚካሄድ አሮጌ ሥርዐት መመለሱ ሞኝነት መሆኑን ለማመልከት ሁለት ነገሮችን ይጠቅሳል።

ሀ) በሲና ተራራ የተጀመረው አሮጌው ኪዳን ከአዲሱ ዝቅ ያለ ነው። እግዚአብሔር በአዲስ የቃል ኪዳን ሥርዐት ለመቀየር የተስፋ ቃል መግባቱ የአሮጌውን ዝቅተኛነት ያሳያል። ማንም ቢሆን ፍጹሙን ነገር አስወግዶ አነስተኛውን ነገር ሊተካ አይፈልግም። የአሮጌው ቃል ኪዳን እንከን ያለበት በመሆኑና የእግዚአብሔርን ዕቅዶች (ሰዎችን ወደ ድነት (ደኅንነት) ሊያመጣ ስላልቻለ፥) እግዚአብሔር የሚሻል አዲስ ኪዳን መሥርቶአል።

ለ) እግዚአብሔር በኤርምያስ 31፡31-34 የተስፋ ቃል የሰጠው አዲሱ ኪዳን በአያሌ መንገዶች ከሲና ተራራው እሮጌ ኪዳን በሚሻሉ የተስፋ ቃሎች ላይ የተመሠረተ ነበር።

  1. አሮጌው ኪዳን በቅድመ-ሁኔታ ላይ የተመሠረተ ነበር። እግዚአብሔር ሕዝቡ ከታዘዙት እንደሚባርካቸው ገልጾ ነበር። ነገር ግን ካልታዘዙት እንደሚቀጣቸው ገልጾአል። የብሉይ ኪዳን ታሪክ እንደሚያሳየው፥ አይሁዶች ቃል ኪዳኑን ሊታዘዙ ባለመቻላቸው የእግዚአብሔርን ቁጣና ፍርድ ሲቀበሉ ኖረዋል፡፡ እንዲያውም፥ እግዚአብሔር ለኤርምያስ አዲሱን ቃል ኪዳን ለመስጠት ቃል በገባ ጊዜ አይሁዶች ወደ ባቢሎን ምርኮ ሊጋዙ ተቃርበው ነበር። በተቃራኒው አዲስ ኪዳን በመታዘዝ ቅድመ ሁኔታ ላይ የተመሠረተ አይደለም። ነገር ግን በልብ መለወጥ ላይ የተመሠረተ ነው። ይህም እግዚአብሔር በክርስቶስ ኢየሱስ ለሚያምኑ ሁሉ የሚያከናውነው ተግባር ነው።
  2. ብሉይ ኪዳን ሰዎች እግዚአብሔርን እንዲታዘዙ ቢጠይቅም፥ የሚታዘዙበትን ኃይል አልሰጣቸውም ነበር። በመሆኑም፥ ያ ዘመን ባለመታዘዝ ተለይቶ የሚታወቅ ነበር። በአዲስ ኪዳን፥ እግዚአብሔር ሕጉን በሰዎች አእምሮና ልብ ላይ ለመጻፍ ቃል ገብቷል። ይህም ሰዎች ቃሉን ሊታዘዙ ያስችላቸዋል። በአዲሱ ኪዳን መታዘዝ የሚመጣው ከተለወጠ ልብ ነው። እንደ የብሉይ ኪዳን ዘመን ሰዎች እግዚአብሔርን የሚታዘዙት እንዳይቀጣቸው በመፍራት አይደለም።
  3. በብሉይ ኪዳን ዘመን ሰዎች ሙሉ በሙሉ እግዚአብሔርን አልታዘዙትም ነበር። እንደ ሙሴና ዳዊት ያሉ ሰዎች እግዚአብሔርን ሲታዘዙት፥ አብዛኞቹ ሰዎች ግን ባለመታዘዝ ነበር የኖሩት። በአዲስ ኪዳን የእግዚአብሔር ሕዝብ አምላካቸውን በመታዘዛቸው ተለይተው ይታወቃሉ።
  4. በብሉይ ኪዳን የእግዚአብሔር ሕዝብ ጊዜያዊ ይቅርታና ከኃጢአት መንጻት የሚያገኙት በተደጋጋሚ መሥዋዕቶችን በማቅረብ ነበር። በአዲሱ ኪዳን ግን እግዚአብሔር የሕዝቡን ኃጢአቶች ሁሉ ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ ይቅር እንደሚልና መልሶም እንደማያስታውስ ቃል ገብቷል።

የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) እግዚአብሔር በአዲስ ኪዳኑ ለእኛ የሚሰጠን እነዚህ የተስፋ ቃሎች አይሁዶች በብሉይ ኪዳን ዘመን ከተቀበሏቸው የተስፋ ቃሎች የሚበልጡት እንዴት ነው? ለ) የአንተ ሕይወት በብሉይ ኪዳን ዘመን አይሁዶች ከእግዚእብሔር ጋር ከነበራቸው ግንኙነት የሚለየው እንዴት ነው? ሐ) እግዚአብሔርን አሁን ስላለህበት አዲስ ኪዳን ለማመስገን ጊዜ ውሰድ።

(ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የአዲስ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)

Leave a Reply

%d bloggers like this: