የክርስቶስ መሥዋዕት ከእንስሳት መሥዋዕቶች ይበልጣል (ዕብ. 9፡13-10፡18)

እስከአሁን ጸሐፊው ክርስቶስ የሚሻል ሊቀ ካህናት የእውነተኛ አምልኮ መሪ እንዲሁም ለምትበልጥ ሰማያዊ ቤተ መቅደስ ውስጥ የሚያገለግል መሆኑን ገልጾአል። በመቀጠልም፥ የዕብራውያን መልእክት ጸሐፊ የክርስቶስ መሥዋዕት በምድራዊ ቤተ መቅደሱ ውስጥ ከቀረቡት መሥዋዕቶች ሁሉ እንደሚበልጥ ያስረዳል። ጸሐፊው አይሁዳውያን ሊቃነ ካህናት ካቀረቧቸው መሥዋዕቶች የክርስቶስ መሥዋዕት ምን ያህል እንደሚበልጥ ለማሳየት የሚከተሉትን እውነቶች ገልጾአል፡

ሀ. ክርስቶስ እራሱን ስለ ሠዋና ሊቃነ ካህናት የእንስሳትን መሥዋዕት ያቀርቡ ስለነበር፥ የክርስቶስ መሥዋዕት ሊቃነ ካህናት በብሉይ ኪዳን ከሰዉአቸው መሥዋዕቶች ሁሉ ይበልጣል። ለስርየት ቀን ሊቃነ ካህናት የፍየሎች እና የኮርማዎችን ደም፥ እንዲሁም የጊደር አመድ እግዚአብሔር ለሕዝቡ ኃጢአት የሠጣቸው ጊዜያዊ የማንጫ መንገዶች ተምሳሌቶች ነበሩ። ነገር ግን መለኮታዊ እና ሰብአዊ የሆነው የእግዚአብሔር ልጅ ክርስቶስ የራሱን ደም ወደ ሰማይ አቀረበ። ክርስቶስ እንከን የለሽ እና ምንም ኃጢአት ያልተገኘበት ሆኖ ለሰው ልጆች ኃጢአት እራሱን ሠውቷል።

ለ. የክርስቶስ ደም የእንስሳት መሥዋዕቶች እንደሚያደርጉት ጊዜያዊ፥ ውጫዊና ሥርዓታዊ መንፃት ሳይሆን፥ ፍጹም መንጻትን በማስከተል ሰዎች ሕያው እግዚአብሔርን እንዲያመልኩ ነፃ አውጥቷቸዋል።

ሐ. ክርስቶስ እግዚአብሔር በአዳምና ሔዋን ውድቀት ጊዜ የመሠረተውን የአምልኮ መርሆ ከፍጻሜ አድርሷል። ይቅርታ የሚመጣው ደም ሲፈስ ወይም የአንዱ ሕይወት በሌላው ሲተካ ብቻ ነው። በብሉይ ኪዳን በእንስሳት ደም የኃጢአት ይቅርታ ይገኝ ነበር። የአምልኮ ስፍራ የሆነው የመገናኛው ድንኳን ሳይቀር በደም መርጨት መንጻት ያስፈልገው ነበር። ክርስቶስ ከእንስሳት ደም የከበረ ደሙን ባቀረበ ጊዜ በሰማያዊቷ ቤተ መቅደስ ውስጥ ይህንኑ የሚመስል ተግባር አከናውኗል።

መ. የክርስቶስ ደም በስርየት ቀን እንደሚቀርቡት የብሉይ ኪዳን መሥዋዕቶች ለአንድ ዓመት ብቻ የሚሠራ ሳይሆን፥ የእግዚአብሔርን ሕዝብ ሁሉ ለሁልጊዜ ያነጻል። በዚህም ዘላለማዊ ይቅርታን ያስገኝላቸዋል። እንደ አሮጌው የአምልኮ ሥርዐት መሥዋዕቶች በየቀኑ መቅረብ አያስፈልጋቸውም።

ክርስቶስ አንድ ጊዜ ብቻ መሞቱ በቂ ነው። የክርስቶስ መሥዋዕት የሰዎችን ኃጢአት የሚያነጻው ከሞቱ በኋላ ብቻ አይደለም። ነገር ግን ከመሞቱ በፊት በብሉይ ኪዳን ዘመን የነበሩትን የእግዚአብሔርን ሕዝብ ኃጢአትም ያነጻል። የእርሱ ደም በመጀመሪያው ኪዳን ሥር ለነበሩት እውነተኛ አማኞች ይቅርታን እና ነጻነትን ያስገኝላቸዋል።

ክርስቶስ ለኃጢአታችን ሁሉ ተገቢውን ዋጋ ከፍሏል። ስለሆነም እኛ ለኃጢአታችን የምንከፍለው ነገር አይኖረንም። አይሁዳውያን አማኞች የእንስሳት መሥዋዕት ለማቅረብ በመፈለጋቸው የክርስቶስን ሞት ዋጋ እያሳጡ ነበር። ዛሬም ብዙ ክርስቲያኖች ለኃጢአታቸው ዋጋ ለመክፈል በመፈለጋቸው የክርስቶስን ሞት ከንቱ ያደርጋሉ። (ለምሳሌ፥ ለቄስ መናዘዝ፥ ከሚገባ በላይ ማልቀስ፥ ደረትን መድቃት፥ የምነና ጉዞ ማድረግ፥ ወዘተ. . .)

ክርስቲያኖች ሆነን ሳለ ኃጢአት በምንሠራበት ጊዜ የእግዚአብሔርን ይቅርታ የምንጠይቀው ከሲኦል ዘላለማዊ ፍርድ ለማምለጥ አይደለም (1ኛ ዮሐ 1፡9)። የክርስቶስ ደም ቀድሞውኑ ኃጢአታችንን ሁሉ ሸፍኖታል። ቀደም ሲል ክርስቶስ የበፊቱን፥ የአሁኑን እና የወደፊት ኃጢአታችንን ሁሉ በደሙ ሸፍኖታል። አንድ አማኝ ለኃጢአቱ ይቅርታ በሚጠይቅበት ጊዜ ከእግዚአብሔር ጋር የነበረውን ኅብረት መልሶ ያገኘዋል። ይህም ኅብረት በኃጢአት ምክንያት ተቋርጦ የነበረው ነው።

ሠ. አይሁዳውያን ሊቀ ካህናት በመቶዎች ለሚቆጠሩ ዓመታት ለእግዚአብሔር ሕዝብ ይቅርታ ለማስገኘት በየዓመቱ ወደ ቅድስተ ቅዱሳኑ ሲገቡ ኖረዋል። ክርስቶስ ግን የእግዚአብሔርን ዕቅዶች ለመፈጸም ሁለት ጊዜ ብቻ መምጣት ያስፈልገዋል። ክርስቶስ መጀመሪያ ሲመጣ የእግዚአብሔር ሕዝብ የኃጢአት ይቅርታን አምጥቶላቸዋል። ዳግም በሚመለስበት ጊዜ ደግሞ ሀ) የእግዚአብሔርን ልጆች በመለወጥ እና በማክበር ደኅንነታቸውን ፍጹም ያደርገዋል። ለ) ለማመን በማይፈልጉት ላይ ፍርዱን ይገልጣል።

ረ. የብሉይ ኪዳን ሕግና የአምልኮ ሥርዓት ጊዜያዊ ሲሆኑ ክርስቶስ የጀመረው አዲሱ ኪዳን ግን ዘላለማዊ ነው፡፡ እንደ መገናኛው ድንኳን ሁሉ ሕጉ ወደፊት የሚመጡ የመልካም ነገሮች ጥላ ነበር። ጸሐፊው ይህን ሲል የብሉይ ኪዳን ሕግና የአምልኮ ሥርዓት ጊዜያዊ እና ዝቅተኛ ደረጃ የሚሰጠው መሆኑን መግለጹ ነበር። ይህም ለኃጢአተኞች የሚፈስሰውን የክርስቶስ ደም የሚያካትት የተሻለ እና የተሟላ የአምልኮ ሥርዓት እስኪመጣ ድረስ እግዚአብሔር ለሕዝቡ የሰጠው ሥርዓት ነበር። አዲሱ የእግዚአብሔር ፍጹም የአምልኮ ሥርዓት ከመጣ በኋላ የብሉይ ኪዳኑ ጊዜያዊ አምልኮ አስፈላጊ አልሆነም።

ሰ. የእንስሳት ደም የሰዎችን ኃጢአት የሚያነጻው ለጊዜው ብቻ ነበር። የክርስቶስ ሞት ግን የተሟላ፥ ዘላለማዊ መንጻትንና ይቅርታን ያስገኛል፡፡ የብሉይ ኪዳን የአምልኮ ሥርዓት የሚካሄደው በፍየሎች እና በኮርማዎች ደም ነበር። የእንስሳት መሥዋዕት በተደጋጋሚ መቅረቡ እንስሳ ለሰው ልጅ ኃጢአት ምትክ ሊሆን እንደማይችል ያመለክታል። አለዚያ ተከታታይ የእንስሳት መሥዋዕቶች ማቅረብን አስፈላጊ አይሆንም ነበር። የብሉይ ኪዳን መጻሕፍት ራሳቸው እግዚአብሔርን ለማርካት የእንስሳት መሥዋዕቶች መቅረባቸው በቂ እንዳልሆነ ያመለክታሉ (1ኛ ሳሙ. 15፡22፤ መዝ. 51፡17፤ ኢሳ. 1፡11፤ 66፡2-3)። ስለሆነም እግዚአብሔርን የሚያስደስት ሌላ ዓይነት መሥዋዕት ማቅረቡ የግድ ነበር። ክርስቶስ እግዚአብሔር የተሻለ መሥዋዕት እንዲቀርብለት የወጠነውን ዕቅድ በሁለት መንገዶች አሟልቷል። በመጀመሪያ፥ ሰውነቱን እንደ ፈቃደኛ ኃጢአት የሌለውና ታዛዥ መሥዋዕት አቅርቧል። ክርስቶስ ፍጹም ሰውና ፍጹም አምላክ በመሆኑ፣ የተሻለ መሥዋዕት ሊሆን በቅቷል። ሁለተኛ፥ ኢየሱስ አንድ ጊዜ ብቻ ለሰው ልጅ ኃጢአት ለመሞት መቻሉ እጅግ የሚበልጥ ነበር። ኢየሱስ ለሰው ልጆች ኃጢአት አንድ ጊዜ ብቻ ሊሞት መገደዱ ከሁሉ የተሻለ ነገር ነበር። ይኸው አንድ መሥዋዕት ኃጢአተኛ የነበሩት የእግዚአብሔር ልጆች በሙሉ ፍጹማን፥ ሙሉአን፥ በእግዚአብሔር ዘንድ ተቀባይነት ያላቸው ሊያደርጋቸው ችሏል።

ሸ. የእንስሳት መሥዋዕቶችን የማቅረቡ ሰብአዊ አገልግሎት ሊጠናቀቅ ባለመቻሉ ቀደም ሲል የነበሩት ሊቃነ ካህናት ተግባራቸውን ፈጽመው ሊቀመጡ አልቻሉም ነበር። ነገር ግን የክርስቶስ የመሥዋዕትነት አገልግሎት ለአንድ ጊዜ ስለተጠናቀቀ እና ሌላ ተጨማሪ መሥዋዕት ስለማያስፈልግ፥ ክርስቶስ በአብ ቀኝ ተቀምጧል። ከመሥዋዕቱ መቅረብ በኋላ የተከሰተው ሁኔታ እግዚአብሔር በክርስቶስ ፍጹም መሥዋዕት እንደረካ ያረጋግጣል። በመገናኛው ድንኳን ውስጥ ወንበር ስላልነበረ እና አገልግሎቱም ስላልተጠናቀቀ፥ ሰአሮጌው ኪዳን ዘመን ሊቀ ካህናቱ ሊቀመጥ አይችልም ነበር። ሊቀ ካህናታችን ኢየሱስ ግን በእግዚአብሔር ቀኝ ሊቀመጥ ችሏል። እራሱን በመስቀል ላይ ለእግዚአብሔር ካቀረበ በኋላ፥ ክርስቶስ ተጨማሪ እንስሳትን ወይም እራሱን እንደገና መሠዋት አላስፈለገውም፤ ምክንያቱም ደሙ የሰውን ልጆች ኃጢአት በሙሉ ያነጻልና። ክርስቶስ በእግዚአብሔር ቀኝ ተቀምጦ በሚገዛበት በአሁኑ ወቅት እግዚአብሔር ጠላቶቹ ለክርስቶስ እስኪገዙለት ድረስ መሥራቱን ይቀጥላል። በአዲስ ኪዳን ውስጥ ክርስቶስ በሰማይ ቆሞ የምንመለከትበት ብቸኛ ስፍራ ከልጆቹ መካከል ሊሞት የነበረውን አንድ ሰው ወደ መንግሥተ ሰማይ ለመቀበል ብቻ ነው (የሐዋ. 7፡55)።

ጸሐፊው በመልእክቱ ማጠቃለያ ላይ በብሉይ ኪዳን ውስጥ ከተጻፉት የአዲስ ኪዳን ተስፋዎች ሁለት የመጨረሻ ማረጋገጫዎችን ያቀርባል። እነዚህም በአሁኑ የአምልኮ ሥርዓት የእንስሳት መሥዋእቶች ለምን እንደማያስፈልጉ የሚያስረዱ ናቸው (ኤር. 31፡33)። በመጀመሪያ፥ በአዲስ ኪዳን የእግዚአብሔር ቃል በሕዝቡ ልብ ላይ ስለሚጻፍ፥ ሕዝቡ እግዚአብሔርን ለመታዘዝ ይፈልጋሉ፥ ሁለተኛ፥ እግዚአብሔር የሕዝቡን ኃጢአት ይቅር ለማለት ቃል ገብቷል። እግዚአብሔር ይቅርታን ስለሰጠ የእንስሳት መሥዋዕት ማቅረቡ አስፈላጊ አይሆንም። ስለሆነም የአይሁዳውያን ክርስቲያኖች ወደ እንስሳት መሥዋዕት መመለሱ ሞኝነት ነበር። ይህ እግዚአብሔር በብሉይ ኪዳን ውስጥ የሰጠውን የተስፋ ቃል ቸል እንደ ማለት ነበር። እንዲሁም የእግዚአብሔር ልጆች በክርስቶስ ሞት በማመን የሚያገኙትን ፍጹም ይቅርታን አለመቀበልም ነበር።

የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) ይህ ክፍል ዛሬ የእንስሳት መሥዋዕቶችን ማቅረብ ከንቱ እንደሆነና በክርስቶስ ሞት አላማመናችንን የሚያሳየው እንዴት ነው። ለ) ሌሎች ክርስቲያኖች ግን የሚያከናውኗቸው እና ክርስቶስ ኃጢአታቸውን ለማስወገድ እንደ ሞተ አለማመናቸውን የሚያጋልጡ አንዳንድ ተግባራት ምን ምንድን ናቸው?

1 thought on “የክርስቶስ መሥዋዕት ከእንስሳት መሥዋዕቶች ይበልጣል (ዕብ. 9፡13-10፡18)”

Leave a Reply

Discover more from

Subscribe now to keep reading and get access to the full archive.

Continue reading