እግዚአብሔርን ስላለመታዘዝ የተሰጠ ማስጠንቀቂያ (ዕብ. 12፡14-29)

ጸሐፊው ስለ መንፈሳዊ ሩጫችን ከገለጸ በኋላ፥ ለሩጫው ብቁ እንዳንሆን የሚያደርጉትን ነገሮች እንደሚከተለው ይዘረዝራል፡-

ሀ) ቅድስናችንን ማጣት (ባለማቋረጥ በኃጢአት ውስጥ መኖር)። ይህም እግዚአብሔርን እንዳናይ ይከለክለናል።

ለ) በሕይወታችን ውስጥ ባሉት ነገሮች ወይም በጎዱን ሰዎች መማረር፡፡

ሐ) አሁን ሕይወታችንን በምናሻሽልበት ሁኔታ ላይ በማተኮር መንፈሳዊ ውርላችንን መሽጥ። ይህም ኤሳው መንፈሳዊ ብኩርናውን ለምግብ እንደ ሸጠው ማለት ነው። ለሰማያዊ በረከቶች እንደ መኖር አሁን በምንፈልጋቸው ቁሳዊ በረከቶች ላይ እናተኩራለን። ይህም እምነታችንን እንድናመቻምችና በጥሩ ሁኔታ እንዳንሮጥ ይከለክለናል።

ጸሐፊው ከአይሁዳውያን አማኞች ፊት የተጋረጡትን ሁለት ምርጫዎች ለማመልከት እግዚአብሔር በሲና ተራራ ላይ ለሙሴና ለእግዚአብሔር ሕዝብ ሕጉ ወደተሰጠበት የብሉይ ኪዳን ዘመን ይመለሳል። ጸሐፊው ሁለት ተራሮች እንዳሉ ይገልጻል። አንደኛው ያለፈ ተራራ ሲሆን፥ ሁለተኛው ደግሞ ወደፊት የሚመጣ ተራራ ነው።

ሀ) የሲና ተራራ፡- የቀድሞው ተራራ እግዚአብሔር ወርዶ ለእስራኤል ሕዝብ ሕጉን የሰጠበት የሲና ተራራ ነው። ያ ምን ዓይነት አስፈሪ ጊዜ ይሆን? በዚያ መለከቶች፥ ድምፆችና ታላቅ ፍርሃት ነበር። ማንም ተራራውን ከነካ እስከሚሞት ድረስ የእግዚአብሔር ክብር ኃይለኛ ነበር። ሕጉን መጣስ ትልቅ ፍርድን አስከተለ፡፡ ይህ አይሁዳውያን አማኞች ክርስቶስን በመካድ ወደ ብሉይ ኪዳን አምልኮአቸው ሊመለሱ የተፈተኑበት ተራራ ነው።

ለ) የጽዮን ተራራ፡- ይህ የወደፊቱ (ዘላለማዊ) ተራራ ነው። ዛሬ በእምነት ስንመላለስ በዚሁ ተራራ ላይ እንጓዛለን። የጽዮን ተራራ ስሙን ያገኘው ሰለሞን ቤተ መቅደሱን ወይም የእስራኤል ርእሰ ከተማ የሆነችውን ኢየሩሳሌምን ከገነባበት ኮረብታ ነው። እነዚህ ሁለቱም የሕያው እግዚአብሔር መኖሪያ ወደሆነችው መንግሥተ ሰማይ ያመለክታሉ። ለመሆኑ በዚህች ታላቅ ከተማ ውስጥ የሚኖሩት እነማን ናቸው?

  1. በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ መላእክቶች ይኖሩበታል።
  2. ከየዘመናቱ የተውጣጡ አማኞች ይኖሩባታል (እነዚህም በሰማያት እንደ ዜጎች የተጻፉ የበኩራት ማኅበር ተብለው ተገልጸዋል)።
  3. የሁሉም ዳኛ የሆነው እግዚአብሔር አብ አለ፡፡
  4. የብሉይ ኪዳን አማኞች (ፍጹማን የሆኑ የጻድቃን መንፈሶች)።
  5. ደሙ በመስቀሉ ላይ በፈሰሰ ጊዜ አዲሱን ኪዳን ያስተዋወቀው ክርስቶስ በዚያ አለ።

እኔና አንተ የዚህች ታላቅ ከተማ አካል ነን ብለን ተስፋ እናደርጋለን። ይህም የሚወሰነው እዚህ ምድር ላይ ሳለን በምናሳልፈው ውሳኔ ላይ ነው።

አይሁዳውያን አማኞች እምነታቸውን ቢክዱ የመንግሥተ ሰማይ ዜግነታቸውን ሊያጡ ይችሉ ነበር። አንድ ቀን በሲና ተራራ ከተፈጸመው የሚበልጥ የመሬት መንቀጥቀጥ ይከሰታል። እግዚአብሔር አዲስ ሰማይንና ምድር ስሚያዘጋጅበት ጊዜ ዓለም ትናወጣለች። በዚህ ጊዜ የሚቀሩት በክርስቶስ ያመኑና የመንግሥተ ሰማይ አባላት የሆኑ ሰዎች ብቻ ይሆናሉ። ወደዚች ከተማ እስከምንደርስ ድረስ ለአሁኑ ዘመን አኗኗራችን ጥንቃቄ ማድረግ ይኖርብናል። እግዚአብሔርን በማክበርና በመፍራት ልናመልከው ይገባል። እግዚአብሔር አፍቃሪና ሰላማዊ አባት ብቻ ሳይሆን በፍርዱ የሚባላ እሳትም ጭምር ነው።

የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) ይህንን ዓለም የሙጥኝ ብለን እንዳንይዝ ዓይኖቻችንን በመንግሥተ ሰማይና በዘላለሙ መንግሥት ላይ መትከሉ ለምን የሚጠቅም ይመስልሃል? ለ) ሌሎች ክርስቲያኖች መንፈሳዊ ሩጫቸውን የሚያደናቅፍ ምን ተግባር ሲፈጽሙ አይተሃል? ሐ) ስለ እግዚአብሔር የፍቅርና የፍርድ ባሕርያት ጥንቃቄ የተሞላበትን ሚዛናዊ አቋም ልንይዝ የምንችለው እንዴት ነው?

(ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የአዲስ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)

Leave a Reply

Discover more from

Subscribe now to keep reading and get access to the full archive.

Continue reading