የአንደኛ ጴጥሮስ ጸሐፊ

የውይይት ጥያቄ፡- 1ኛ ጴጥሮስ 1፡1 አንብብ። ሀ) የዚህ መልእክት ጸሐፊ ማን ነው? ለ) እራሱን እንዴት ይገልጸዋል? ይህ ጳውሎስ ሁልጊዜ ራሱን ከሚገልጽበት ሁኔታ የሚለየው ወይም የሚመሳሰለው እንዴት ነው? ሐ) የዚህ መልእክት ተቀባዮች እነማን ናቸው። በዚህ መልእክት ውስጥ የተገለጸበት ሁኔታ ምን ይመስላል?

የአንደኛ ጴጥሮስ መልእክት ጥንታዊ የደብዳቤ አጻጻፍ ስልት በመከተል የጸሐፊውን ማንነት በማስተዋወቅ ይጀምራል። እርሱም ጴጥሮስ መሆኑን ይነግረናል። ጴጥሮስ ልክ እንደ ጳውሎስ ራሱን ሐዋርያ ብሎ ይጠራዋል። ይህን ያደረገው በቤተ ክርስቲያኒቱ ውስጥ ሌሎች ጴጥሮስ ተብለው የሚጠሩ ሰዎች ስለነበሩ፥ የመልእክቱ ጸሐፊ ማን እንደሆነ ለይቶ ለማሳወቅ ብቻ ሳይሆን፥ ከዚህ በበለጠ ግን መልእክቱን ለመጻፍ ምን ሥልጣንና ስፍራ እንዳለው ለሕዝቡ ለማሳወቅ ይፈልጋል። መልእክቱን የሚጽፈው እንደ ኢየሱስ ክርስቶስ ሐዋርያ ነው።

ሐዋርያው ጴጥሮስ ምናልባትም በቀድሞይቱ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ እጅግ የታወቀ የቤተ ክርስቲያን መሪ ሳይሆን አይቀርም። የጴጥሮስ አይሁዳዊ ስሙ ስምዖን ሲሆን፥ በገሊላ የተወለደ አይሁዳዊ ነበር። ይህች ስፍራ በፓለስታይን ምድር ውስጥ ብዙም ያላደገች ነበረች። በገሊላ አካባቢ አይሁዶችም አሕዛብም ይኖሩ ነበር። ጴጥሮስ ያደገው ምናልባትም የግሪክና የአረማይክ ቋንቋዎችን እየተናገረ ይሆናል። አባቱ ዓሣ አጥማጅ ነበር። ከዚህም የተነሣ ከወንድሙ እንድርያስ ጋር ዓሣ አጥማጆች ሆኑ። የጴጥሮስ መንፈሳዊ እድገት የጀመረው መጥምቁ ዮሐንስን ባገኘው ጊዜ ሳይሆን አይቀርም። ወንድሙ እንድርያስ የመጥምቁ ዮሐንስ ተከታይ ስለነበር፥ ጴጥሮስም እንዲሁ የዮሐንስ ደቀ መዝሙር የነበረ ይመስላል (ዮሐ 1፡40-42)።

ክርስቶስ ከተጠመቀ ከጥቂት ጊዜያት በኋላ እንድርያስ ጴጥሮስን ከክርስቶስ ጋር አስተዋወቀው። ከዚያም በኋላ ጴጥሮስ ቀሪ ዘመኑን ሁሉ ክርስቶስን ይከተልና ያገለግል ጀመር። ክርስቶስ መጀመሪያ አገልግሎቱን በገሊላ በጀመረ ጊዜ ጴጥሮስ አብሮት ጥቂት ጊዜ ካሳለፈ በኋላ (ዮሐ. 2)፥ ቤተሰቡ ወደሚተዳደርበት ዓሣ የማጥመድ ተግባር የተመለሰ ይመስላል። ኢየሱስ ይፋዊ አገልግሎቱን በጀመረ ጊዜ፥ ካከናወናቸው ተግባራት አንዱ ጴጥሮስ ከደቀ መዛሙርቱ አንዱ እንዲሆን መጥራት ነበር። ጴጥርስ አንድ ቀን በዓለም ሁሉ የእግዚአብሔርን መንግሥት የሚያሰራጭ ተማሪ ነበር (ማቴ. 4፡18-20)።

ለቀጣይ ሦስት ተኩል ዓመታት፥ ጴጥሮስ ከኢየሱስ ጋር በመሆን ተአምራቱን ሲመለከት፥ ስብከቶቹን ሲሰማና በክርስቶስ ለአገልግሎት ሲላክ እንመለከታለን። በዚህም አገልግሎቱ ተአምራትን የማድረግና በእሥራኤል ምድር ሁሉ ለመስበክ ተልኮአል። ጴጥሮስ የመሪነት፥ የድፍረትና የችኩልነት ባሕርያት ያሉት ይመስላል። ብዙም ሳይቆይ የደቀ መዛሙርቱ ቃል አቀባይ ሆነ ክርስቶስ ጴጥሮስን ከብዙ ተከታዮቹ መካከል ለይቶ ብዙ ጊዜውን አብሯቸው ከሚያጠፋው ከ12ቱ ደቀ መዛሙርቱ ውስጥ አካተተው። በተጨማሪም፥ ክርስቶስ ለወደፊት የቤተ ክርስቲያን መሪነት ይጠቅሙ ዘንድ ተጨማሪ ጊዜ ወሰደ። ከሚያሠለጥናቸው ሦስት ደቀ መዛሙርት (ከያዕቆብና ዮሐንስ ጋር) አንዱ ጴጥሮስ ነበር።

ጴጥሮስ ኢየሱስ የእግዚአብሔር ልጅ የሆነ መሢሕ እንደሆነ በድፍረት ባወጀ ጊዜ (ማቴ. 16፡16-20)፥ ክርስቶስ ስሙን ከስምዖን ወደ ኬፋ (አረማይክ) ወይም ጴጥሮስ (ግሪክ) ለወጠው። ይህም ዓለት የሚል ፍቺ ይስጣል። ይህ የስም ለውጥ ለጴጥሮስ የሚሰጠውን ልዩ ኃላፊነት እና ሥልጣን ያመለክታል። ጴጥሮስ ክርስቶስ ቤተ ክርስቲያኑን የሚመሠርትበት ዓለት ይሆን ነበር። ብዙም ሳይቆይ ግን የጴጥሮስ ድፍረትና እምነት ግን ይከስማል። ክርስቶስ ከመሰቀሉ በፊት በአይሁድ አለቆች በሚመረመርበት ወቅት፥ ጴጥሮስ ኢየሱስን ሦስት ጊዜ ካደው። ጴጥሮስ በዚያን ሌሊት ክርስቶስን መካዱን በፍጹም ሊረሳው አልቻለም። በአንደኛ ጴጥሮስ ውስጥ እንኳን ሳይቀር ስለዚሁ ጉዳይ ይጠቅሳል። ሥቃይ ልቡን እየናጠው ጴጥሮስ በምሬት አለቀሰ። ከትንሣኤ በኋላ ግን፥ ኢየሱስ ፍቅሩንና ይቅርታውን በሚያሳይ መልኩ ጴጥሮስን አነጋገረው። በዚህም ጊዜ የቤተ ክርስቲያን ዋና መሪ ወደ መሆኑ ኃላፊነት እንደገና መልሶ አስቀመጠው።

ጴጥሮስ በቀድሞይቱ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ ዋና መሪ መሆኑ በሐዋርያት ሥራ መጽሐፍ የመጀመሪያዎቹ ገጾች ውስጥ ተመልክቷል። መንፈስ ቅዱስ በሐዋርያት ላይ በወረደ ጊዜ፥ የመጀመሪያውን ስብከት ያቀረበውና አይሁዶች በኢየሱስ አምነው የመንፈስ ቅዱስን ስጦታ እንዲቀበሉ የጋበዛቸው ጴጥሮስ ነበር (የሐዋ. 2)። እግዚአብሔር ጴጥሮስ ለማኙን የመፈወስ የመጀመሪያውን ተአምር እንዲሠራ ተጠቅሞበታል (የሐዋ. 3)። ለእምነቱ በቀዳሚነት ስደትንና መከራን የተቀበለው ጴጥሮስ ነው። ወደ በኋላም ጴጥሮስ በዚሁ ርእሰ ጉዳይ ላይ ጽፎአል (የሐዋ. 4)። የቀድሞይቱ ቤተ ክርስቲያን ለሰማርያውያን ወንጌልን በሰበከች ጊዜ የሰማርያውያንን እምነት እንዲገመግሙና ለሰማርያውያን አማኞች ሁሉ የመንፈስ ቅዱስን ስጦታ እንዲያስተላልፉ ቤተ ክርስቲያን ጴጥሮስና ዮሐንስን ነበር የላከቻቸው (የሐዋ. 8፡14-17)። (ሰማርያውያን ከፊል አይሁዶችን ከፊል አሕዛብ ነበሩ።) እግዚአብሔር አሕዛብን ወደ ቤተ ክርስቲያን የሚያመጣበት ጊዜ ሲደርስ፥ ጴጥሮስ ከቆርኔሌዎስ ጋር እንዲገናኝ አደረገ። ጴጥሮስ እየመሰከረ ሳለ መንፈስ ቅዱስ በመጀመሪያዎቹ አሕዛብ አማኞች ላይ ወረደ (የሐዋ. 10)። አሕዛብ ተጠምቀው ወደ አይሁዳዊነት ሳይለወጡ መንፈስ ቅዱስን ከእግዚአብሔር መቀበላቸው የጴጥሮስን አስተሳሰብ ለወጠው። በመሆኑም ወደ በኋላ ጴጥሮስ እግዚአብሔር በክርስቶስ ኢየሱስ የሚያምኑትን አሕዛብ እንደሚቀበል አጥብቆ ሲከራከር እንመለከታለን (የሐዋ. 15፡7-11)።

እግዚአብሔር ወንጌልን ወደ አሕዛብ ሁሉ ለማድረስ ጳውሎስ የተባለ ሌላ ሰው አስነሣ። ለጊዜው የአይሁዶች ሐዋርያ የተባለው ጴጥሮስ (ገላ. 2፡8) በኢየሩሳሌም ተቀምጦ በፍልስጥኤም ምድር ላሉ አይሁዶች ሁሉ ሲሰብክ ኖረ። ጴጥሮስ ከቦታ ቦታ እየተዘዋወረ የሚያገለግል ሰባኪ በመሆኑ ምክንያት ይመስላል፥ በኢየሩሳሌም የነበረችው የእናት ቤተ ክርስቲያን አመራር የክርስቶስ ወንድም ለነበረው ለያዕቆብ ተሰጠ (ገላ. 1፡19)። ጴጥሮስ እስከሚሞትበት ጊዜ ድረስ በመጨረሻዎቹ 20 ዓመታት ምን ዓይነት ሁኔታ ውስጥ እንደነበር የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ በግልጽ አይነግረንም። ጳውሎስ ጴጥሮስ በአንጾኪያ እንደነበረ ይናገራል (ገላ. 2፡1-14)። ምናልባትም ወደ ቆሮንቶስ ተጉዞ አይሁዳውያን ክርስቲያኖች እንዲከተሉት ሳይጠይቃቸው አልቀረም (1ኛ ቆሮ. 1፡12)። የበለጠ ትክክለኛ የሚመስለው ኢየሩሳሌም ቤተ ክርስቲያን ከተጠናከረበት ጊዜ በኋላ፥ ጴጥሮስ በምሥራቃዊ የሮም ግዛት ውስጥ እየተዘዋወረ የወንጌል መልእክተኝነት አገልግሎት ይሰጥ እንደነበር የሚያሳየው ይሆናል። ጴጥሮስ በጳንጦስና በገላትያ፥ በቀጰዶቅያም፥ በእስያም፥ በቢታንያ ለተበተኑ መጻተኞች መልእክት ለማስተላለፍ በመፈለጉ ምናልባትም በእነዚህ አካባቢዎች ወንጌልን እንደ ሰበክ ሊያመለክት ይችላል። ጴጥሮስ የኋላ ኋላ ወደ ሮም እንደ ሄደ የቤተ ክርስቲያን ታሪክ ያመለክታል። በዚያ ምን ያህል ጊዜ እንደ ሠራ አልተጠቀሰም። አንዳንድ ምሁራን ጳውሎስ በሮም ቤተ ክርስቲያን ውስጥ የነበሩትን አንዳንድ ክፍፍሎች ለማስተካከል ጴጥሮስን ጋብዞት ነበር ይላሉ። ነገር ግን በኔሮ ዘመነ መንግሥት ክርስቲያኖች ላይ ስደት በተነሣ ጊዜ ጴጥሮስ በምርኮኛነት ተወሰደ። አንድ የቤተ ክርስቲያን ታሪክ እንደሚያሳየው፥ ሮማውያን ጴጥሮስን ለመግደል በመጡ ጊዜ እንደ ጌታ ኢየሱስ ለመሰቀል ባለመፈለጉ፥ ራሴን ዘቅዝቃችሁ ስቀሉኝ ብሏል። ይህ እውነት ይሁን እውነት አይሁን የሚታወቅ ነገር የለም። ምናልባትም ጴጥሮስ የሞተው ጳውሎስ በሞተበት ጊዜ አካባቢ ሳይሆን አይቀርም። ይህም በ67 ዓመተ ምሕረት አካባቢ መሆኑ ነው።

የአንደኛ ጴጥሮስ መልእክት የተጻፈው በጴጥሮስ ነው። ጴጥሮስ ይህንን መልእክት የጻፈው በሕይወቱ መጨረሻ አካባቢ ነው። ይህ መልእክት የተጻፈበት የግሪክ ቋንቋ ከፍተኛ ጥራት ስላለው ምናልባትም መልእክቱን የጻፈው ስልዋኖስ (ሲላስ) ሳይሆን አይቀርም። ሲላስ ግሪክን በሚገባ ያውቅ የነበረ ሲሆን፥ ጴጥሮስ የሚናገረውን አሳብ በዚሁ መልእክት ውስጥ ሳያሰፍር አልቀረም። ጴጥሮስ በእርጅናው ዘመን ይህን መልእክት ሲጽፍ ከክርስቶስ ጋር ለረጅም ጊዜ የኖረ በመሆኑ መከራን መቀበል ምን እንደሆነ ያውቅ ነበር። በወጣትነቱ ጊዜ እርሱ እንዳደረገው ክርስቶስን እንዳይክዱና በመከራ ታግሰው እግዚአብሔር ያዘጋጀላቸውን ሽልማት እንዲቀበሉ ያበረታታቸዋል።

(ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የአዲስ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)

Leave a Reply

Discover more from

Subscribe now to keep reading and get access to the full archive.

Continue reading