የእግዚአብሔር ልጆች የሰይጣንን ውሸት ከማመን ይልቅ እውነትን መጠበቅ ይኖርባቸዋል (1ኛ ዮሐ 2፡18-27)።

ምንም እንኳ ይህ የ1ኛ ዮሐንስ መልእክት ክፍል እንዴት ለእግዚአብሔር መኖር እንዳለብን የሚያመለክት ተግባራዊ ትምህርት ቢሆንም፥ ቀዳሚ ትኩረቱ ግን በሐሰተኛ ትምህርቶች በምንከበብበት ጊዜ እንዴት ለእውነት መኖር እንዳለብን ማሳየት ነው።

ዮሐንስ በመጨረሻው ሰዓት ወይም ክርስቶስ ሊመለስ ሲል ከሚከሰቱት ነገሮች አንዱ የሐሰተኛ ትምህርቶች መበራከት መሆኑን ይናገራል። ዮሐንስ ሁለት ዓይነት የክርስቶስ ተቃዋሚዎች (ሐሳዊ መሲሆች) እንዳሉ ይገልጻል። የመጀመሪያው፥ የክርስቶስ ተቃዋሚ ነው። ዮሐንስ ይህን ሲል ክርስቶስ ሊመለስ ሲል ዓለምን ለመግዛትና የእግዚአብሔርን ሕዝብ ለማጥፋት ሰይጣን የሚሾመውን ዋነኛ ክፉ የዓለም ገዢ ማለቱ ነው (ራእይ 13፡1-8)። ሁለተኛ፥ ሌሎች ብዙ የክርስቶስ ተቃዋሚዎች ይኖራሉ። ይህ በሰይጣን ኃይል እውነትን የሚዋጉትን ሁሉ ያጠቃልላል። ይህም ሐሰተኛ አስተማሪን ሊያመለክት ይችላል። ዮሐንስ በጠቀሰው ምሳሌ ውስጥ ይህንን መመልከት ይቻላል። ወይም ደግሞ የእግዚአብሔርን ሕዝብ ለማጥፋት የሚጥረውን የፖለቲካ መሪ ሊያመለክት ይችላል። ለምሳሌ ያህል፥ ሙሶሎኒ የክርስቶስ ተቃዋሚ ነው ማለት ይቻላል። ሰዎች ከርስቶስን ሳይሆን የክርስቶስን ተቃዋሚ እንደሚከተሉ የሚያሳየው ምንድን ነው?

ሀ) ከእውነተኛ አማኞች መለየታቸው። ከሐሰተኛ አስተማሪዎች የተነሣ አንዳንድ ሰዎች ቤተ ክርስቲያንን የለቀቁ ይመስላል። ዮሐንስ እነዚህ ሰዎች የለቀቁት ቀድሞውንም የሚያድን እምነት ስላልነበራቸውና የክርስቶስ አካል ባለመሆናቸው ነው ይላል።

ለ) እነዚህ ሰዎች ከመጽሐፍ ቅዱስ ጋር የማይስማማ የተሳሳተ ትምህርት ያስተምሩ ነበር። በዮሐንስ ዘመን ክርስቶስ በሥጋ የተገለጠ አምላክ መሆኑን ክደዋል። ዮሐንስ እንዲህ ዓይነቱን መሠረታዊ እውነት መካድ ክርስቶስን ብቻ ሳይሆን እግዚአብሔር አብንም መካዳቸውን የሚያረጋግጥ መሆኑን ይናገራል። በዛሬው ዘመናችን እነዚህ መሠረታዊ እውነቶች እንደ ሥላሴ፥ የድነት መንገድ (በጥረታችን የእግዚአብሔርን ሞገስ የምናገኝበት ሳይሆን ዳሩ ግን በክርስቶስ በማመን የምንቀበለው የእግዚአብሔር ስጦታ)፥ ድነት የሚገኘው በክርስቶስ ብቻ ወይም በሌሎች ሃይማኖቶች ጭምር የሚሉ ይሆናሉ። ሐሰተኛ ትምህርት በሚገጥመን ጊዜ ምላሻችን ምን ይሆናል? በመጀመሪያ፥ በቤተ ክርስቲያን ታሪክ ሁሉ ውስጥ አልፈው ወደ እኛ በደረሱት የመጽሐፍ ቅዱስ እውነት ላይ አጽንኦት መስጠት ይኖርብናል። እነዚህ እውነቶች በእግዚአብሔር ቃል ውስጥ ይገኛሉ። ሁለተኛ፥ መንፈስ ቅዱስን መተማመን አለብን። በግል፥ በተለይም በክርስቶስ አካል ውስጥ መንፈስ ቅዱስ ሰዎች ከእውነት ወደ ሰይጣን ውሸቶች የሚቅበዘበዙባቸውን መንገዶች ለአማኞች ይገልጻል።

(ማስታወሻ፡- አንዳንድ ጊዜ ክርስቲያኖች ዮሐንስ በዚህ ስፍራ መንፈስ ቅዱስ ያስተምራቸዋል ሲል ምን ማለቱ እንደሆነ በትክክል ሳይረዱ ይቀራሉ። ዮሐንስ ይህን ሊል በቤተ ክርስቲያን ውስጥ አስተማሪዎች አያስፈልጉንም ማለቱ አይደለም። መጽሐፍ ቅዱስ አስተማሪዎች የሚያስፈልጉ መሆናቸውን በተደጋጋሚ ይገልጻል። እንዲያውም፥ ይህ መንፈስ ቅዱስ አንዳንድ አማኞች በቤተ ክርስቲያን ውስጥ እንዲያገለግሉ የሚሰጣቸው ቁልፍ መንፈሳዊ ስጦታ ነው (ማቴ. 28፡20፤ 1ኛ ቆሮ. 12፡28፥ ኤፌ. 4፡11፤ ቆላ. 3፡16)። ስለሆነም፥ እግዚአብሔር በቤተ ክርስቲያን ውስጥ እውነትን እንዲያስተምሩ፥ በስጦታዎች ያበለጸጋቸውን ሰዎች ማዳመጥ ይኖርብናል። ይህ መጽሐፍ ቅዱስን ማጥናት የለብንም ማለትም አይደለም። ይህም የእግዚአብሔርን እውነት እንጂ ከመንፈስ ቅዱስ እንዲመጣ የሚያስቡትን የራሳቸውን አሳብ እንዳያስተምሩ ይረዳቸዋል (2ኛ ጢሞ. 3፡16-17)።

ይህ ክፍል የተመሠረተው ሐሰተኛ አስተማሪዎች በሚያስተምሩት አሳብ ላይ ነው። እነዚህ ሰዎች ሐዋርያት ወይም መንፈስ ቅዱስ ከሚያስተምረው የበለጠ ልዩ ምሥጢራዊ እውቀት እንዳላቸው ይናገሩ ነበር። ዮሐንስ በሚጽፍላቸው ክርስቲያኖች ለማስተማር የፈለጉት ይህንኑ ምሥጢራዊ እውቀት ነበር። እግዚአብሔር ከገለጠው ውጭ ክርስቲያኖች የሆነ ምሥጢራዊ እውቀት መሻት የለባቸውም። አማኞች በልባችን ውስጥ መንፈስ ቅዱስ አለን። እርሱም ወደ እውነት ሁሉ ይመራናል። መንፈስ ቅዱስ ሁሉን አማኞችን ለማስተማር የሚጠቀምበት ዋነኛው መሣሪያ ደግሞ የእግዚአብሔር ቃል ነው፡፡ አንድን አዲስ ነገር ከመፈለግ ይልቅ መንፈስ ቅዱስ ከጻፈው መጽሐፍ ውስጥ እንዲያስተምረን መፍቀድ አለብን። ሁሉም አማኝ የሚያስተምረው መንፈስ ቅዱስ በውስጡ እንዳደረበት ቢታወቅም፥ ሰይጣን አንድን አማኝ በቀላሉ ሊያስት ስለሚችል መንፈስ ቅዱስ በአማኞች መካከል የሚሰጠውን ትምህርት መከታተሉ ጠቃሚ ነው። አማኞች መንፈስ ቅዱስ እያስተማራቸውና ወደ እውነት ሁሉ እየመራቸው እንዳለ የሚያውቁት የመንፈስ ኅብረት ሲኖራቸውና የእግዚአብሔርን ቃል በተሟሟቀ ሁኔታ በሚያጠኑበት ጊዜ ነው። የእግዚአብሔርን ቃል በጥንቃቄ በምታጠና ቤተ ክርስቲያን ውስጥ መጽሐፍ ቅዱስ በግልጽ ያላስቀመጠው አሳብ ክፍፍል በሚፈጥርበት ጊዜ፥ ይህ በተለምዶ ከመንፈስ ቅዱስ ስለማይሆን ጥንቃቄ ማድረግ ይኖርብናል።

የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) ሐሰተኛ አስተማሪዎች በቤተ ክርስቲያን ውስጥ ክፍፍል ሲፈጥሩ የተመለከትክበትን ሁኔታ ግለጽ። ለ) ዮሐ 17 አንብብ። በዚህ ክፍል ውስጥ ክርስቶስ የጸለየውና ዛሬም መንፈስ ቅዱስ ሕይወታችንን ሊያዛምድበት የሚፈልገው እውነት ምንድን ነው? ሐ) አንዳንድ ክርስቲያኖች መንፈስ ቅዱስ በውስጣቸው ስላለ ሰዎች እንዲያስተምሯቸው ወይም የእግዚአብሔርን ቃል መማር እንደማያስፈልጋቸው ሲናገሩ ሰምተህ ታውቃለህ? ይህ ጤናማ አመለካከት ነው? ለምን? መ) 2ኛ ጴጥ. 1፡20-21፤ 2ኛ ጢሞ. 3፡16–17 አንብብ። እነዚህ ጥቅሶች መንፈስ ቅዱስ መጽሐፍ ቅዱስን እንደ ጻፈ ብቻ ሳይሆን፥ መጽሐፍ ቅዱስ እግዚአብሔር ሰዎችን ለማረም፥ ለመገሠጽ፥ እና በጽድቅ ለማሠልጠን፥ ወዘተ… የሚጠቀምበት መሣሪያ መሆኑንም ያስረዳሉ። መንፈስ ቅዱስና መጽሐፍ ቅዱስ በስሕተት እንዳንወድቅ እውነትን በማስተማሩ በኩል ለእኛ የሚያበረክቱት አስተዋጽኦ ምንድን ነው?

(ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የአዲስ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)

Leave a Reply

%d bloggers like this: