የባቢሎን ጥፋት (ራእይ 17:1-18:24)

የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) ዘፍጥ. 11፡1-9 አንብብ። ባቢሎን በመባል በምትታወቀው ሰናዖር ላይ ምን ተከሰተ? ለ) ከመጽሐፍ ቅዱስ መዝገበ ቃላት ስለ ባቢሎን የተጻፈውን አንብብና ስለ ባቢሎን ታሪክ በተለይም ከእግዚአብሔር ሕዝብ ጋር ስላላቸው ግንኙነት ማጠቃለያ ጻፍ። ሐ) ራእይ 17-18ን አንብብ። ስለ ባቢሎን የተጻፈውን ገለጻና እግዚአብሔር ባለው መሠረት የተፈጸመውን አሳብ ዘርዝር።

ራእይ 17-18 በባቢሎን ላይ ሊሆን ስላለው ነገር በሁለት አቅጣጫ ይጽፋል። ራእይ 17 ከሃይማኖታዊ እይታ አንጻር ስለጠፋችው ባቢሎን ይናገራል። ራእይ 18 ደግሞ የንግድ ማዕከል በነበረችው ባቢሎንና ለኑሮአቸውና ለብልጽግናቸው ሲሉ የተደገፏት ሕዝብ በሚሰጡት ምላሽ ላይ ያተኩራል። 

ባቢሎን ግን ማንን ትወክል ይሆን? ዮሐንስ በብሉይ ኪዳን ዘመን በኤፍራጥስ ወንዝ አካባቢ የጥንት ሥልጣኔ ማዕከል የነበረችውን ነባራዊዋን ባቢሎንን እየገለጸ ነው? ወይስ ተምሣሌታዊ ገጽታ ስላላው ሌላ ነገር እየተናገረ ነው? ተመራማሪዎች ሦስት የተለያዩ አመለካከቶች አሉአቸው? አንደኛ፥ ዮሐንስ ስለ ነባራዊዋ ባቢሎን እንደተናገረ የሚያምኑ ጥቂት ተመራማሪዎች አሉ። የባቢሎን ከተማ የረጅም ጊዜ ታሪክ ያላት ናት። ለመጀመሪያ ጊዜ የተጠቀሰችው በዘፍጥ. 11፡1-9 ሰናዖር በሚለው ስሟ ነው። ይህቺም ከተማ ከጥፋት ውኃ በኋላ ሰዎች ስማቸውን ለማስጠራት እስከ ሰማይ የሚደርስ ግንብ የገነቡባት ስፍራ ናት። በዚህም ምክንያት እግዚአብሔር ቋንቋቸውን በመለወጥ በምድር ዙሪያ ሁሉ በተናቸው። ወደ በኋላ ባቢሎን ኢየሩሳሌምንና መቅደሱን በማፍረስ ብዙ አይሁዶችን በ586 ዓ.ዓ ወደ ምርኮ በመውሰዷ የአይሁዶች ዋነኛ ጠላት ሆናለች። ከዚያም በኋላ ለአንድ መቶ ዓመታት ያህል አስፈላጊ ብትሆንም፥ በኋላ የሜዶንና የፋርስ መንግሥታት አሸንፈዋታል። በዚህም ምክንያት በኢሳይያስ በተነገረው ትንቢት መሠረት ፈራረሰች (ኢሳ. 13)። በአዲስ ኪዳን ዘመን ባቢሎን በአካባቢዋ ከሚኖሩ ጥቂት መንደርተኞች በስተቀር የፈራረሰች ከተማ ነበረች። የሆነ ሆኖ ግን፥ በመጨረሻው ዘመን የክርስቶስ ተቃዋሚ ከተማይቱን መልሶ በማቋቋም የግዛቱ ማዕከል እንደሚያደርጋት የሚያምኑ አንዳንዶች አሉ። ይህ እውነት ከሆነ ራእይ 17–18 የሚገልጸው የክርስቶስ ተቃዋሚን የግዛቱን ዋና ከተማ ጥፋት ነው ማለት ነው።

ሁለተኛ፥ ባቢሎን በአዲስ ኪዳን ዘመን የነበረችውን ሮምን በተምሳሌትነት የምታመለክት ናት ብለው የሚያምኑ ጥቂት ሰዎችም አሉ። በአዲስ ኪዳን ዘመን በነበሩት ሌሎች የአይሁዶችና የክርስቲያን ሥነ ጽሑፎችም ውስጥ ባቢሎን የሮም ተምሳሌት ነበረች። ሮም የአይሁዶች ጠላት ስትሆን፥ በ70 ዓ.ም ኢየሩሳሌምንና መቅደሱን አፍርሳለች፡፡ ይህም ባቢሎን በኢየሩሳሌምና በቤተ መቅደሱ ላይ ካደረገችው ጋር ተመሳሳይነት አለው። በተጨማሪም እርሷ የእግዚአብሔር ሕዝብ የሆኑትን አይሁድንና ክርስቲያኖችን ያሳደደች መንግሥት ናት። ከዚያም በኋላ በ1ኛ ጴጥሮስ 5፡13 ጴጥሮስ ባቢሎን የሚለውን ስም የተጠቀመው ሮምን ለማመልከት ሳይሆን አይቀርም። ስለሆነም፥ ብዙ ምሁራን ዮሐንስ የሮምን ውድመት እያመለከተ መሆኑን ይናገራሉ።

ሦስተኛ፥ በይበልጥ፥ ባቢሎን እግዚአብሔርን የሚቃወሙትን ሁሉ በተምሳሌትነት የምታመለከት ይመስላል። በሰይጣን ቁጥጥር ሥር ውሎ ሰዎችን የሚያታልለውን የትኛውንም ሃይማኖት ትወክላለች። እውነትንና የእግዚአብሔርን ሕዝብ የሚቃወም መንግሥት የሚኖርባትን (እንደ ሮም ያለች) ከተማ ታመለክታለች። በዚህ መልኩ ሮም በአንድ በኩል ባቢሎን መሆኗን እንመለከታለን። ነገር ግን ከሁሉም የከፋችው ባቢሎን ዓለም በሙሉ እግዚአብሔርን እንዲዋጋ የሚያስተባብረው ሐሳዊ መሢሕ መንግሥት ትሆናለች። ስለሆነም ዮሐንስ ባቢሎን እንደምትወድቅ ሲገልጽ፥ በእግዚአብሔርና በመንገዶቹ ላይ የሚያምጹ ሁሉ እንደሚወድሙ መግለጹ ነው። ይህም ማለት የውሸት ሃይማኖቶች፥ ክፉ የመንግሥት ሥርዓቶች፥ ቁሳዊ ኢኮኖሚዎች፥ ወዘተ… ይጠፋሉ ማለት ነው። የሐሳዊ መሢሕ የመጨረሻው መንግሥት ዓለም እስከ አሁን አይቶት የማያውቀው ክፉ በመሆኑ፥ በዚህ ስፍራ በቀዳሚነት የተጠቀሰው ባቢሎን ይኸው ነው።

ብዙ ምሁራን ዮሐንስ ሁለት ተምሳሌታዊ ከተሞችን እያነጻጸረ ነው ይላሉ። አንደኛዋ የክፋት ተምሳሌት የሆነችው ባቢሎን ናት። ይህች ከተማ በሰይጣን ቁጥጥር ሥር ውላ ሁልጊዜም የእግዚአብሔርን መንገድ እየተቃወመች የሰዎችን መንገድ ከፍ ከፍ ታደርጋለች። ሌላዋ እግዚአብሔር የሚቆጣጠራቸውና እርሱን የሚያከብሩ ነገሮች ሁሉ ተምሳሌት የሆነችው አዲሲቱ ኢየሩሳሌም ነች።

አዲሲቱ ኢየሩሳሌም እግዚአብሔር በንግሥና የሚገዛባትና ሰዎች እርሱን እየታዘዙ የሚያከብሩባት ከተማ ነች። ለዘላለም የምትኖረው ይህቺው ኢየሩሳሌም ናት።

ዮሐንስ ቀደም ሲል ስለ ባቢሎንና ስለሚደርስባት ፍርድ ሁለት ጊዜያት ጠቅሷል (ራእይ 14፡8፤ 16፡19)። የመጨረሻው የጽዋ ፍርድ ስለ መውደሟ ይናገራል። ራእይ 17–18 ስለ ታላቂቱ ባቢሎንና እግዚአብሔር ስለሚያመጣባት ውድመት ተጨማሪ ገለጻዎችን ያቀርባል። 

፩. ሃይማኖታዊዋ ባቢሎን፡ ከአውሬው ላይ የተቀመጠችው ሴት (ራእይ 17) 

የውይይት ጥያቄ፡- ሃይማኖትና መንግሥታት በእግዚአብሔር ሕዝብ ላይ ስደት ለማምጣት እንዴት አብረው ሲሠሩ እንደተመለከትክ ግለጽ።

ቀደም ሲል እንደተመለከትነው፥ ብዙውን ጊዜ ሐሰተኛ ሃይማኖትና ክፉ መንግሥታት እግዚአብሔርና ሕዝቡን ለመውጋት አብረው ይሠራሉ። ዮሐንስ ይህንን እውነት የአንዲትን ጋለሞታ ሴት ተምሳሌታዊ ራእይ በማቅረብ ያብራራል። ይህች ሴት ጋለሞታ የተባለችው ሰዎችን ከእውነተኛ ፍቅርና ለእግዚአብሔር ታማኝ ከመሆን ስለምትመልስ ነው። ይህቺ ሴት በብዙ ውሆች ላይ ትቀመጣለች። ይህም በሁሉም አገር ውስጥ እንደምትገኝ ያመለክታል። ሴቲቱ የተቀመጠችበት ቀይ አውሬ የስድብ ስሞች የሞሉበት፥ ሰባት ራሶችና አሥር ቀንዶች ያሉት ነው። ሃይማኖታዊዋ ባቢሎን ከፖለቲከኛዋ ባቢሎንና ከዘንዶው ጋር የጠበቀ ቁርኝት አላት። ሁሉም ተመሳሳዮች ናቸው። ይህቺ ጋለሞታ የሐሳዊ መሢሕን ያህል ሥልጣንና ኃይል አላት። ሴቲቱ እንደ ዘንዶው ማለትም እንደ ሰይጣን ናት። ዘንዶው ወይም ሰይጣን ከእግዚአብሔር ጋር በሚያደርገው ውጊያ እንድታግዘው ባሕሪውንና ኃይሉን ይሰጣታል። ይህቺ ሴት በሐምራዊ፥ በወርቅና በከበሩ ድንጋዮች አጊጣለች። ይህም ይህቺ ሴት የተከበረችና እንደ ንግሥት የምትታይ መሆኗን ያመለክታል። ከተከታዮቿ ባገኘችው ሀብት በልጽጋ ነበር። (አብዛኞቹ የሐሰተኛ ሃይማኖት መሪዎች ወደ ብልጽግናው ያደላሉ። ይህ ሐሰተኛ ሃይማኖት እንደ አብዛኞቹ ሐሰተኛ ሃይማኖቶች ሁሉ ውጭው ሲታይ የተከበረ ይመስላል። በውስጡ ግን ታላቅ ክፋት ተሰውሯል። ይህንን አክራሪ ሙስሊሞች እነርሱ የሚፈልጉትን ነገር የማያደርጉትን በሺዎች የሚቆጠሩ ሰዎች ከሚገድሉበት ወይም ክርስትና የመንግሥት ሃይማኖት በመሆን በመሪዎቹ አማካኝነት የተለየ አሳብ የሚይዙትን ሰዎች ከሚገድልበት (እንደ መስቀል ዘመቻ ዘመን) ሁኔታ ጋር የሚመሳሰል ነው። ይህ ሃይማኖት ምንም ዓይነት ስም ይኑረው ለክርስቶስ ምስክርነት የሚሰጡትን ቅዱሳን ደም የሚያፈስ የእግዚአብሔር ሕዝብ ጠላት ነው።

መልአኩ ጋለሞታይቱ ከተቀመጠችበት አውሬ ጀምሮ ራእዩን ያብራራል። ዮሐንስ ስለ አውሬው የሚናገረውን ሁሉ መረዳቱ አስቸጋሪ ነው። ምክንያቱም ተምሳሌቱ መንግሥትንም ሰውንም ያመለክታልና ነው። እንዲሁም ተምሳሌቱ በዮሐንስ ዘመን የሮምን መንግሥት፥ እንዲሁም በሐሳዊ መሢሕ ፍጻሜውን ወደሚያገኝበት የመጨረሻው ዘመን የሚያመለክት ይመስላል። የዚህ ራእይ አያሌ ገጽታዎች ከዚህ በታች ቀርበዋል።

ሀ) “አስቀድሞ ነበር፥ አሁንም የለም፥ ከጥልቁም ይወጣ ዘንድ አለው። ወደ ጥፋትም ይሄዳል።” አንዳንድ ሰዎች ይህ ክፋት በሃይማኖትና በመንግሥታት ውስጥ የሚኖር መሆኑን ያሳያል ይላሉ። ሰዎች ምንም ያህል ክፋትን ለማጥፋት ቢታገሉም፥ ሁልጊዜም ተመልሶ ይመጣል። ክፋት ሙሉ በሙሉ የሚደመሰሰው በክርስቶስ ዳግም ምጽአት ብቻ ነው። ይህ ምናልባትም በራእይ 13 እንደ ሞተና ከዚያም ነፍሰ እንደ ዘራ የተመለከትነውን ከባህር የወጣ አውሬ ወይም ሐሳዊ መሢሕን የሚያመለክት ይሆናል (ራእይ 13:3-4)።

ለ) ሰባቱ ራሶች ሰባት ኮረብቶችና ሰባት ነግሥታት ናቸው። ከሰባቱ ነገሥታት አምስቱ ቀደም ሲል ሞተዋል። አንዱ በሥልጣን ላይ ነው። ሌላኛው ደግሞ ገና ወደ ፊት ይመጣል። ከዚያም ከሰባተኛው ንጉሥ የሚመጣው ስምንተኛው ንጉሥ ሐሳዊ መሢሕ ይሆናል። የሮሜ ከተማ መጀመሪያ በሰባት ኮረብታዎች ላይ እንደ ተመሠረተች ከታሪክ እንረዳለን። ይህም በዚህ ስፍራ የተገለጸችው ሮም እንደሆነች የሚያመለክት ይመስላል። ይህ አስቸጋሪ ገለጻ ምሁራን የተለያዩ አመለካከቶችን እንዲይዙ አድርጓቸዋል። አንዳንዶቹ ዮሐንስ ከእርሱ በፊት ስለነበሩት አምስት ነገሥታት፥ በዘመኑ ስለነበረው አንድ ንጉሥና ከእርሱ በኋላ ስለሚመጡ ሁለት ነገሥታት፥ በአጠቃላይም ስምንት የሮም ነገሥታት እየተናገረ ነው ይላሉ። ሌሎች ሰባት ነገሥታት ከምድር የሚነሡ ዓለማዊ መንግሥታት መሆናቸውን ይናገራሉ። እነዚህም ከዮሐንስ ዘመን በፊት አምስቱ (እንደ ግብጽ፥ አሶር፥ ባቢሎን፥ ሜዶንና ፋርስ፥ ግሪክ)፥ የሮም መንግሥት እንዲሁም የሐሳዊ መሢሕ መንግሥት የሚመነጭበት ሌላ መንግሥት ናቸው። አሁንም ሌሎች ዮሐንስ በተምሳሌታዊ መልኩ የክፋትን ኃይል እያመለከተ ነው የሚሉ አሉ። ክርስቶስ በመስቀል ላይ በሞተ ጊዜ የክፋትን ኃይል አሸንፎአል። አማኞችም ለክርስቶስ በመታዘዛቸው ምክንያት ነፍሳቸውን አሳልፈው እየሰጡ ክፋትን ያሸንፋሉ (ራእይ 12፡11)። በዮሐንስ ዘመን ግን ክፋት አሁንም በሮም መንግሥት ውስጥ ነግሦ አማኞችን በማሳደድ ላይ ነበር። ነገር ግን ወደፊት የሚኖረው አንድ የክፋት ራስ ብቻ ነበር። ይህም የሐሳዊ መሢሕ መንግሥት ነው። ነገር ግን ዮሐንስ ይኸው ክፋት በቅርቡ እንደሚጠፋ ለአማኞች ያረጋግጣል።

ሐ) ይህ የመጨረሻው የሐሳዊ መሢሕ መንግሥት ከሐሳዊ መሢሕ ጋር ቃል ኪዳን ከሚገቡ አሥር አገሮች የተመሠረተ ነው። የዮሐንስ ራእይ እግዚአብሔር ይህንንም ሁኔታ እንደሚቆጣጠር ያመለክታል። እነዚህ መንግሥታት ሥልጣን የሚይዙት ለአንድ ሰዓት ብቻ ነው። ይህ የጊዜውን አጭርነት ያመለክታል። እነዚህ የቃል ኪዳን አገሮች ተባብረው በጉን ይዋጋሉ። ነገር ግን በጉ የሆነው ኢየሱስ ክርስቶስ የጌቶች ጌታና የነገሥታት ንጉሥ በመሆኑ፥ ከቅዱሳኑ ጋር እነዚህን የዓለም መንግሥታት ያሸንፋቸዋል።

ለመሆኑ ጸረ እግዚአብሔር፥ ጸረ እውነት፥ በሆነችው የዓለም ሃይማኖት ላይ (ጋለሞታይቱ) ምን ይደርሳል? ለጊዜው በዓለም መንግሥታት ሁሉ ላይ ኃይል ይኖራታል። ከሐሳዊው መሢሕ ጋር በቅርብ አብራ ትሠራለች። ብዙም ሳይቆይ ግን የፖለቲካ መሪዎችና ሐሳዊው መሢሕ ያጠፉአታል። አንዳንዶች ምሁራን ይህ የመጨረሻው ዘመን ዓለም አቀፍ ሃይማኖታዊ ሥርዓት ሐሳዊ መሢሕን በመደገፍ የሚጀምር መሆኑንና ሐሳዊው መሢሕ ግን በግሉ ለመመለክ በመፈለጉ ይህንን ሃይማኖት ለማክሰም እንደሚነሣሣ ያሳያል ይላሉ። ሌሎች ይህ ምንም እንኳን ብዙውን ጊዜ ሃይማኖትና ፖለቲካ አብረው ቢሠሩም፥ የኋላ ኋላ እርስ በርሳቸው የሚጣሉ መሆናቸውን ያሳያል ይላሉ። የሃይማኖት መሪዎች ሰዎች እንዲከተሏቸውና እንዲያከብሯቸው ይፈልጋሉ። የመንግሥታት መሪዎችም እንደዚሁ፥ ሁለቱም ዓይነት መሪዎች የሰዎችን ታማኝነት ለማግኘት ስለሚፈልጉ እርስ በርሳቸው ይዋጋሉ። በመጨረሻው ዘመን፥ ሐሳዊ መሢሕ ሰዎች እርሱን ብቻ እንጂ ሌሎችን እንዳያመልኩ ያስገድዳል። በመሆኑም ሃይማኖታዊቷን ባቢሎንን ያጠፋታል። (ማስታወሻ፡ አንዳንዶች በዚህ ውስጥ ብዙውን ጊዜ ክፋት ከራሱ ጋር የሚጣላና ራሱን የሚያጠፋ መሆኑን ይመለከታሉ።)

ምንም እንኳን ይህን ራእይ ለመረዳት አስቸጋሪ ቢሆንና፥ ምሁራን የተለያዩ አተረጓጎሞችን ቢያቀርቡም፥ እግዚአብሔር እርሱን የምትቃወመውን ባቢሎንን እንደሚያጠፋት ግልጽ ነው። ከተቃውሞው መካከል አንደኛው ሃይማኖታዊ ነው። ሰዎች አማራጭ የአምልኮ መንገዶች አድርገው የቀረጹአቸው ሐሰተኛ የሃይማኖት ሥርዓቶች ይከሰታሉ። በመጨረሻው ዘመን፥ ዓለም አቀፍ ሃይማኖት የሚመሠረት ይመስላል። ይህም ሐሳዊ መሢሕን የሚያመልክ ነው። የኋላ ኋላ ግን እግዚአብሔር ሐሰተኛ ሃይማኖታዊ ሥርዓቶችን በሙሉ ያጠፋቸዋል። ሌላኛዋ ዓይነት ባቢሎን ፖለቲካኛዋ ባቢሎን ናት። ይህም በሐሳዊ መሢሕ የሚጠናቀቀውን የዓለም መንግሥት የሚያሳይ ነው። ይህም በራእይ 19 ውስጥ እንደምንመለከተው በእግዚአብሔር የሚጠፋ ነው። 

የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) እግዚአብሔር አንድ ቀን ሁሉንም ሐሰተኛ ሃይማኖቶችና በሰይጣን ኃይል የሚሠሩትን ፖለቲካዊ ሥርዓቶች ጨምሮ ባቢሎኖችን እንደሚያጠፋ ማወቃችን እንዴት ያበረታታናል? ለ) ይህ ለእግዚአብሔር ንጹሕ ሆኖ ከመቆየት ይልቅ ከባቢሎኖች ጋር ስለ መተባበር ምን ማስጠንቀቂያ ይሰጠናል?

፪. የነጋዴዋ ባቢሎን ውድመት (ራእይ 18)

የሰውን ልጅ የሚያጠፉ ሦስት ኃይላት አሉ። እነዚህም ሐሰተኛ ሃይማኖቶች፥ ክፉ መንግሥታትና በጥቂቶች ቁጥጥር ሥር ውሎ ፍትሕ አልበኝነትንና የእኩልነት መጓደልን የሚያስፋፋው በራስ ወዳድነት ላይ የተመሠረተ የኢኮኖሚ ሥርዓት ነው። ስርቆት፥ ግድያ፥ ጦርነት፥ ድህነት፥ ጉቦኛነት ሁሉ ሰዎች ከመንግሥተ ሰማይ ብልጽግና ይልቅ በገንዘብ ላይ የማተኮራቸው ውጤት ነው። እነዚህ ሁሉ ባቢሎን ተብለው ይጠራሉ። እነዚህ ሁሉ በታሪክ የተለየ የክፋት ገጽታ ያሳያሉ። ይህም እግዚአብሔር የወጠነው ዕቅድ የማይከተል ፀረ እግዚአብሔር ተግባር ነው። እነዚህ ሦስቱም የባቢሎን ዓይነቶች በሰይጣን ቁጥጥር ሥር የሚካሄዱ ናቸው። በማቴዎስ 6፡21 ክርስቶስ መዝገባችን ባለበት ልባችን በዚያ እንደሚሆን ተናግሯል።

በራእይ 18 ዮሐንስ ብዙውን ጊዜ ከመንግሥታት ጋር አብሮ የሚሠራው የዓለም ፍትሐዊ ያልሆነ የኢኮኖሚ ሥርዓት ተጠቃሚዎች ከነበሩት ወገኖች እይታ አንጻር የባቢሎንን ውድመት ገልጾአል። አብዛኞቹ መንግሥታት ሀብታሞችንና ነጋዴዎችን እንጂ ድሆችን እይደግፉም። የመንግሥት የሥራ ኃላፊዎች ሀብታሞች ሲሆኑ፥ በራስ ወዳድነት ሀብታቸውን ለማካበት ይጥራሉ። ፍትሐዊ ባልሆነ መንገድም ይህንኑ ከማድረግ ወደ ኋላ አይሉም። ዮሐንስ የዓለምን ቁሳዊ የአኗኗር ዘይቤ እግዚአብሔር ከሚያጠፋት ከተማ ጋር ያነጻጽራል። የገንዘብ ፍቅር፥ ቁሳዊ ሀብትና የምቾት አኗኗር የምድርን ነገሥታት ያወደሙ የዝሙት ተግባራትም ሆነው ተገልጸዋል። እግዚአብሔርም የዓለምን የኢኮኖሚ ሥርዓት ለማጥፋት ተዘጋጅቷል። በመጀመሪያ ግን ለአማኞች ጥሪውን ያቀርባል። «ሕዝቤ ሆይ፥ በኃጢያቷ እንዳትተባበሩ ከመቅሰፍቷም እንዳትቀበሉ ከእርሷ ዘንድ ውጡ። ኃጢአቷ እስከ ሰማይ ድረስ ደርሷልና።» እግዚአብሔር ይህን ሲል ክርስቲያኖች ዓለማውያን ከሚሠሩበትና ከሚኖሩበት አካባቢ እንዲርቁ መጠየቁ አይደለም። ክርስቲያኖች ወደሚኖሩበት አካባቢ በመሄዳችን ንጹሕ ሕይወት ልንኖር አንችልም። በዚህ ዓይነት በመራቅ ለዓለማውያን የምንመሰክርበትን ዕድል እናጣለን። እግዚአብሔር የሚለው ዓላማችን፥ አመለካከታችንና ተግባራችን የተለየ መሆን እንዳለበት ነው። የገንዘብ ፍቅር፥ ይበልጥ ተጨማሪ ቁሳዊ በረከቶችን ማግኘት ሕይወታችንን እንዳይቆጣጠር ይነግረናል። የእግዚአብሔርን መንግሥትና የዘላለምን ሕይወት አስቀድመን ልንሻ ይገባል። ይህ ዋንኛው ትኩረታችን ሊሆን ይገባል። በዚህ ዓይነት ንጹሐን ሆነን ከቆምን ከእግዚአብሔር ፍርድ እናመልጣለን። 

የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) ክርስቲያኖች ለቁሳዊ ነገሮች፥ ለሀብት፥ ለምቾት፥ ወዘተ… ባላቸው አመለካከት የነጋዴዋ ባቢሎን ሥርዓት አባል ሲሆኑ የተመለከትከው እንዴት ነው? ለ) አንዳንድ ጊዜ ክርስቲያኖች የሚያደርጓቸውና የገንዘብ ፍቅር ሕይወታቸውን እንደ ተቆጣጠረ የሚያሳዩ ነገሮች ምን ምንድን ናቸው? ሐ) እግዚአብሔር በዚህ ምዕራፍ ውስጥ ለሀብታም ክርስቲያኖች የሰጠው ማስጠንቀቂያ ምንድን ነው?

ዮሐንስ የነጋዴዋን ባቢሎንን መውደቅ በማሳየት ብዙውን ጊዜ የሌሎችን ሰዎች ጥረት ለራሳቸው መጠቀሚያ በማድረግ በራስ ወዳድነት ስለተመላለሱት የተለያዩ ሰዎች ያብራራል። ሥልጣናቸውን ለገንዘብ ማግኛ ስላዋሉት ነገሥታትና ገዢዎች ይናገራል። የኢኮኖሚ መዋቅራቸው በሚፈርስበት ጊዜ ጭንቀት ይውጣቸዋል። ከዚያም ቁሳቁሶችን በመግዛትና በመሽጥ ኑሯቸውን የሚገፉ ነጋዴዎች ተገልጸዋል። እነርሱም ሕይወታቸው ሲናጋና ባዶ እጃቸውን ሲቀሩ ያለቅሳሉ። በመጨረሻም፥ የውኃ ላይ መርከቦች ካፒቴኖች ተጠቅሰዋል። እነዚህም የዓለምን ቁሳዊ ሀብቶች የማጓጓዝ ኃላፊነት ያላቸውን ሁሉ የሚያመለክቱ ናቸው። የሚያጓጉዙት ነገር በማይኖርበት ጊዜ ኑሯቸው ይናጋል።

ዮሐንስ እግዚአብሔርን የሚቃወሙትን ማኅበረሰብ ሁሉ (ሃይማኖታዊ፥ ኢኮኖሚያዊ፥ ፖለቲካዊ) በተምሳሌትነት የምታመለክተው ባቢሎን የምትደመሰስ መሆኗን በመግለጽ ይህን ምዕራፍ ያጠናቅቃል። ሮማውያን ሙሉ በሙሉ እንዲደመስሷት ጥንታዊቷ የኢየሩሳሌም ከተማ፥ ንጉሥ ኢየሱስ ክርስቶስ የሰይጣንን ከተማ በሚደመስስበት ጊዜ ሐሳዊ መሢሕ፡ ነቢዩ፥ እንዲሁም ከእግዚአብሔርና ከሕዝቡ ይልቅ ባቢሎንን የመረጡ ሁሉ ይደመሰሳሉ። በዚህም ጊዜ የእግዚአብሔር ፍትሕ ይከናወናል። እርሱ የነቢያቱንና የቅዱሳኑን ሞት ተበቅሏልና። 

የውይይት ጥያቄ፡- ራእይ 19-22 አንብብ። ሀ) በምድር ያሉት ዓለማውያን (ራእይ 18) ለባቢሎን መደምሰስ የሰጡትን ምላሽ በሰማይ ያሉት አማኞች ከሰጡት ጋር አነጻጽር። ለ) ክርስቶስ በጠላቶቹ ላይ ያለው ኃይልና ድል ነሺነት የተገለጸው እንዴት ነው? ሐ) በተለያዩ የእግዚአብሔር ጠላቶች ላይ ምን እንደሚከሰት ግለጽ። መ) የዘላለም ክብር የተገለጸው እንዴት ነው?

(ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የአዲስ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)

Leave a Reply

Discover more from

Subscribe now to keep reading and get access to the full archive.

Continue reading