በዘጸአት ጊዜ የነበረው የግብፅ ታሪክ

የኢትዮጵያ ሕዝብ ታሪክ በዓለም ከሚፈጸመው ታሪክ ጋር በቅርብ የተቆራኘ እንደሆነ ሁሉ፥ የእስራኤል ሕዝብ ታሪክም ከጥንቱ ዓለም ጋር የተቆራኘ ነበር። ይህ ደግሞ በተለይ በዚያን ጊዜ ከሁሉም በላይ ገናና የነበረችውን ግብፅን በሚመለከት የበለጠ እውነትነት አለው።

የውይይት ጥያቄ፥ መዝ. 2፤ ኢሳ. 40፡ 15-25 አንብብ። ሀ) እነዚህ ቁጥሮች እግዚአብሔር በአሕዛብ ሁሉ ላይ ስላለው አገዛዝ ምን ያስተምሩናል? ለ) እነዚህ ቁጥሮች በአሁኑ ጊዜ እንዴት ያበረታቱናል?

እግዚአብሔር መንግሥታትን ሁሉ ይቆጣጠራል፤ ታሪካቸውንም ይወስናል። ደካሞች ይሁኑ ብርቱዎች ድንበራቸው የት ድረስ እንደሚሆን ሁሉ የሚወስን እግዚአብሔር ነው። እግዚአብሔር እስራኤላውያንን ወደ ግብፅ በማምጣት በእነርሱ ውስጥ የሠራው ከራብ ሊያድናቸው ብሎ ነው። እንደምታስታውሰው፥ እግዚአብሔር ይህንን ያደረገው የግብፅ ጠቅላይ ሚኒስትር ባደረገው በዮሴፍ መሪነት ነው። ነገር ግን በግብፅ በተፈጸሙት ክስተቶች ስሙ ይከበር ዘንድ በግብፅ ሕዝብ መካከልም ሠርቷል።

የውይይት ጥያቄ፥ ኢያ. 2፡8-11 አንብብ። በግብፅ የተፈጸሙት ታሪካዊ (ድርጊቶች በዚያን ጊዜ ለነበሩት የአሕዛብ መንግሥታት ሁሉ ምን አስተማራቸው?

መጽሐፍ ቅዱስ ስለ ግብፅ ታሪክ ብዙ አይነግረንም። ምክንያቱም የእግዚአብሔር ቃል ትኩረት ስለ ሕዝቡ ስለ እስራኤል፥ እንዲሁም በእነርሱ በኩልና በእነርሱም አማካይነት እንዴት እንደሠራ መናገር ነው፤ ዳሩ ግን በዚያ ጊዜ ስለነበረው ስለ ግብፅ መንግሥት ከዓለም ታሪክ ብዙ ለመማር እንችላለን። የኦሪት ዘጸአት ታሪክ የተፈጸመው አዲሱ የመንግሥት ዘመን በመባል ይታወቅ በነበረው የግብፅ ታሪክ ጊዜ ነበር በማለት ብዙ ምሁራን ያምናሉ።

የኢትዮጵያ ታሪክ በተለያዩ ጊዜያት ሊከፋፈል እንደሚችል ሁሉ፥ የግብፅ ታሪክም በተለያዩ ጊዜያት ሊከፋፈል ይችላል። በ1800 ዓ.ዓ. ግብፃውያን መካከለኛው መንግሥት እየተባለ በሚጠራው መንግሥታቸው ይኖሩ ነበር። በዚህ ዘመን መጨረሻ አካባቢ የግብፅ መንግሥት በጣም ተዳከመ። በ1700 ዓ.ዓ. አካባቢ ከእስያ የመጣ ሐይክሶስ የተባለ የሴም ዘር ሕዝብ ግብፅን በመውረር ሥልጣን ጨበጠ። እነዚህ ሕዝቦች ከአይሁድ ጋር የሚዛመዱና እንደ እነርሱም መጻተኞች ስለነበሩ አይሁድ ከሐይክሶሳውያን ጋር ጥሩ ግንኙነት ነበራቸው፤ ዳሩ ግን በ1550 አካባቢ ግብፆች ሐይኪሶሳውያንን አባረሩና መንግሥታቸውን እንደገና ተቆጣጠሩ። ይህ ዘመን ከ1546-1085 ዓ.ዓ. ድረስ የቆየ ሲሆን የአዲሱ መንግሥት ዘመን በመባል ይታወቅ ነበር። ይህም በግብፅ ታሪክ ውስጥ ታላቅ ጥንካሬና እድገት የታየበት ጊዜ ነበር።

ግብፃውያን በባዕዳን ተገዝተው ስለነበር በምድራቸው በሚኖሩ የውጭ ዜጎች ሕዝቦች ሁሉ ላይ ተቃውሞ አካሄዱና እንደ ሐይኪሶስ ያሉትን አንዳንዶቹን አባረሩ። እንደ አይሁድ ያሉትን ደግሞ ባሪያዎች አደረጉ። ኦሪት ዘጸአት 1-12 ግብፆች አይሁድን ባሪያ ያደረጉበትን ይህን ጊዜ ያንፀባርቃል። ግብፃውያን አይሁድ በኃይል እያደጉ እንዳይሄዱ የፈሩበትን ምክንያት ያስረዳል። ሐይኪሶሶች እንዳደረጉት አይሁድም ምድራቸውን እንዳይወስዱባቸውና እንዳይዙአቸው ይሠጉ ነበር።

የውይይት ጥያቄ፥ ቤተ ክርስቲያን ጠንክራ እንዳታድግ በሚፈልጉ በአንዳንድ በማያምኑ ሰዎች ላይ ይህ ተመሳሳይ ፍርሃት እንዴት ይታያል? 

የግብፃውያን ሃይማኖት 

የውይይት ጥያቄ፥ ዘጸአት 32:1-8 አንብብ። እስራኤላውያን እግዚአብሔርን የሚያሳዝን ምን ነገር አደረጉ?

እስራኤላውያን ከግብፃውያን ጋር ለ400 ዓመታት ኖረዋል። በዚህ ቆይታቸው ለእግዚአብሔር ባላቸው አምልኮ በንጽሕና መቆየት አልቻሉም። ይልቁንም የግብፃውያንን አማልክት ማምለክ ጀመሩ። በዘጸአት 32 እስራኤላውያን በእግዚአብሔር ላይ ሲያምፁና በጥጃ የሚመሰለውን የግብፃውያን አምላክ ሲያመልኩ እንመለከታለን።

የውይይት ጥያቄ፥ ሀ) ዛሬም ክርስቲያኖች ራሳችውን ለእግዚአብሔር ንጹሐን አድርገው ከመጠበቅ ይልቅ በዙሪያቸው ያሉትን ሕዝቦች አስተሳሰብና ልማድን መከተል የሚቀላቸው እንዴት ነው? አንዳንድ ምሳሌዎችን ጥቀስ። ለ) ቤተ ክርስቲያንህ አባሎችዋ ዓለምን እንደማይመስሉና በእግዚአብሔር ፊት በንጽሕና እንዳሉ ለማረጋገጥ በየጊዜው ምን ታደርጋለች? ሐ) ቤተ ክርስቲያን አባሎችዋን ከዓለም አሉታዊ ተጽዕኖ ለመጠበቅ ምን የተሻለ ነገር ማድረግ ትችላለች?

ግብፃውያን በርካታ የተለያዩ አማልክትን ያመልኩ ነበር። ከእነዚህ አማልክት መካከል አብዛኛዎቹ በተፈጠረው ዓለም ውስጥ ያሉ ነገሮች ይመስሉ ነበር። ለምሳሌ፡- የፀሐይ አምላክን፥ የጨረቃ ሴት አምላክን፥ ወፎችን፥ እንደ ወይፈን ያሉ እንስሳትን ወዘተ. ያመልኩ ነበር። በአገራቸው በአጠቃላይ እነዚህን አማልክት የሚያመልኩባቸውን በርካታ ቤተ መቅደሶች ሠርተው ነበር። ግብፃውያን በበርካታ አማልክት ያምኑ ስለነበር፥ የሌሎች ሕዝቦችን አማልክት በቀላሉ ማምለክ ይችሉ ነበር። እስራኤላውያንም እነዚህን አማልክት ለምደው ነበርና እነርሱን ለማምለክ ተመሳሳይ የሆኑ ምስሎችን መሥራት ጀመሩ። እግዚአብሔር ለእስራኤላውያን የመጀመሪያዎቹን ሁለት ትእዛዛት የሰጠው የእነዚህን በርካታ አማልክት አምልኮን በመቃወም ነበር።

የውይይት ጥያቄ፥ ዘጸ. 20፡ 1-6 አንብብ። ሀ) በዚህ ስፍራ የምናገኛቸው ሁለት ትእዛዛት ምንድን ናቸው? ለ) ስለ እስራኤል ሕዝብ ታሪክ ባለህ ግንዛቤ መሠረት ብዙ ጊዜ እነዚህን ትእዛዛት የሚጥሱት እንዴት ነበር?

በሲና ተራራ እግዚአብሔር ለእስራኤል ሕዝብ የሰጣቸው የመጀመሪያዎቹ ሁለቱ ትእዛዛት በግብፃውያን ዘንድ በጣም ተለምዶ የነበረውንና እስራኤላውያን በግብፅ በቆዩበት ጊዜ የተለማመዱትን የጣዖት አምልኮ የሚያመለክቱ ነበሩ። እንደ አጋጣሚ እስራኤላውያን በታሪካቸው ሁሉ ከጣዖት አምልኮ ጋር ይታገሉ ነበር።

በመጀመሪያው ትእዛዝ እግዚአብሔር ለእስራኤላውያን የነገራቸው እውነተኛ አምላክ የሆነውን እርሱን ብቻ እንጂ ሌሎች አማልክትን እንዳያመልኩ ነበር። ሁለተኛው ትእዛዝ የሚናገረው ደግሞ በጊዜው በጣም የተለመደውን የተቀረፀ ምስልን ወይም እግዚአብሔርን የሚወክል ነገር ማድረግን የሚመለከት ነበር። አማልክቶቻቸው በጥጃ ወይም በእባብ ወዘተ. የተመሰሉ ነበሩ። እነዚህንም ምስሎች ያመልኩ ነበር። እግዚአብሔር እርሱን የሚመስሉበትን አንዳችም ነገር እንዳያደርጉ አይሁድን በጥብቅ አዝዞአቸዋል።

የውይይት ጥያቄ፥ ሀ) እግዚአብሔር ሰዎች እርሱን የሚመስሉበትን አንዳችም ምስል ወይም ቅርፅ እንዳያደርጉ የፈለገበት ምክንያት ምን ይመስልሃል?ለ) ሰዎች በቤታቸው ወይም በቤተ ክርስቲያናቸው የሚያንጠለጥሉት የኢየሱስ ሥዕልስ ጉዳይ እንዴት ነው? እነዚህ የእግዚአብሔር ምስሎች ናቸውን? መልስህን አብራራ። ሐ) ክርስቲያኖች የኢየሱስን ሥዕል በቤታቸው መስቀል አለባቸውን? መልስህን አብራራ።

እግዚአብሔር መንፈስ ነው፥ በመሆኑም ማንኛውንም የተፈጠረ ነገር አይመስልም። ሰው እግዚአብሔርን በአንድ ዓይነት ቅርፅ ወይም ምስል ለመመሰል የሚያደርገው ሙከራ እርሱን ማክበር ሳይሆን ማዋረድ ነው። ሰው የእግዚአብሔርን ኃይልና ክብር ሙላት ለማወቅም ሆነ ለመገመት አይችልም፤ ስለዚህ እንዲህ ላለው ታላቅ አምላክ ክብርን የሚሰጥ ነገር ማዘጋጀት አንችልም።

ክርስቲያኖች በቤትም ሆነ በቤተ ክርስቲያን የኢየሱስን ሥዕል ስለ መስቀል የተለያየ አመለካከት አላቸው። ሙስሊሞች በቤታቸውም ሆነ መስጊዳቸው ማንኛውንም ዓይነት የእግዚአብሔር ምስል ላለማድረግ ይጠነቀቃሉ። ስለ ክርስቲያኖች የሚነቅፉት ነገር ቢኖር ራሳቸውን ክርስቲያን ብለው የሚጠሩ እነዚህ ሰዎች የእግዚአብሔርን፥ የኢየሱስን ወይም የመላእክትን ሥዕል በቤተ ክርስቲያናቸው ወይም በቤታቸው ያደርጋሉ ብለው ነው። ይህ ነገር እግዚአብሔርን የማያስከብርና ትእዛዙንም የሚቃረን ነው ብለው ያምናሉ።

ክርስቲያኖች ማንኛውንም የኢየሱስን ሥዕል በቤተ ክርስቲያናቸውም ሆነ በቤታቸው ስለ መስቀል እጅግ መጠንቀቅ አለባቸው። ለዚህም አራት ዋና ዋና ምክንያቶች አሉ፡

  1. በዘጸ. 20፡4-6 የሚገኘው ሁለተኛው ትእዛዝ፥ ይህ በእግዚአብሔር ፊት ትክክል እንዳልሆነ በግልጥ የሚያሳይ ይመስላል። 
  2. ሥዕሎቹ ኢየሱስን አያስከብሩም። እንዴት ኢየሱስን በትክክል ወይም ብቃት ባለው መንገድ መግለጥ ወይም መሣል ይቻላል? መጀመሪያ፥ በአሁኑ ጊዜ ከሚኖሩ ሰዎች ኢየሱስን ያየ ስለሌለ ምን እንደሚመስል አናውቅም። ሥዕሉን መሥራት የምንችለው ባሕላዊ አስተሳሰባችንን መሠረት በማድረግ ብቻ ነው። ሁለተኛ፥ ኢየሱስ ከሰው ብልጫ ያለው ነው። እርሱ አምላክ ነው። እንደ አምላክነቱ ክብሩን፥ ኃይሉን፥ ችሉታውን፥ ግርማ ሞገሱን፥ ቅድስናውንና ፍቅሩን ወዘተ. በሚገባ ልንገልጥ አንችልም። 
  3. ሥዕሎች ለክርስቲያኖች በቀላሉ የማሰናከያ ዓለት ሊሆኑ ይችላሉ፤ በመጀመሪያ፥ የኢየሱስን ሥዕል ስንሰቅል መጥፎ ነገር ሆኖ ላይሰማን ይችላል። ስለ ኢየሱስ «እንድናስብና» ሕልውናው «እንዲሰማን» ብቻ ያደርጋል እንላለን። ወዲያውኑ ግን ወደ ኢየሱስ ምስል መጸለይ እንጀምራለን፤ በአእምሮአችንም ውስጥ ያ ሥዕል ይቀረፃል። እንግዲህ የምንጸልየው ለምስሉ እንጂ ለኢየሱስ አይደለም ማለት ነው። በቤተ ክርስቲያን ታሪክ ሁሉ የሚታየው የክርስቲያኖች ዝንባሌ ሥዕሎችን ወደሚመለክ ነገር መለወጥ ነው። ይህ ደግሞ በተለይ በካቶሊክና በኦርቶዶክስ አብያተ ክርስቲያናት ይታያል።

የውይይት ጥያቄ፥ አንዳንድ የኦርቶዶክስ አማኞች ሥዕሎችን ወይም ሐውልቶችን ሲያመልኩ እንዴት እንዳየህ ግለጥ። ይህ እግዚአብሔርን የሚያስከብር ነው ወይስ የሚያዋርድ? 

  1. ሥዕሎች መጥፎ ምስክርነትን የሚያሳዩ ናቸው። በተለይ ሥዕል የምናመልክ ለሚመስላቸው ሙስሊሞችና አንዳንድ የኦርቶዶክስ ክርስቲያኖች መጥፎ ምስክርነት ይሆናሉ። ሥዕሎች በእምነታችንና በምስክርነታችን ላይ የሚያመጡት አደጋ ሊሰጡን ከሚችሉት ከማንኛውም ዓይነት ጥቅም ይልቅ የሚያመዝን ነው። ስለዚህ እነዚህን ሥዕሎች በቤተ ክርቲያንም ሆነ በቤታችን አለመስቀል የሚመረጥ ይመስላል።

እስራኤላውያን ከግብፅ ነፃ የወጡበት ጊዜ

እስራኤላውያን ግብፅን ለቀው ወደ ከነዓን መጓዝ ስለ ጀመሩበት ጊዜ ምሁራን ያለማቋረጥ ይከራከራሉ። ሁሉም ምሁራን የሚስማሙት ይህ ነጻ የመውጣት ተግባር የተፈጸመው ከ1450-1200 ዓ.ዓ. ባለ ጊዜ እንደ ሆነ ነው። ምሁራን የሚቀበሉዋቸው ሁለት ዋና ዋና ጊዜያት አሉ። በመጀመሪያ፥ የኋለኛ ጊዜያትን የሚቀበሉትን እናገኛለን። እነዚህ ምሁራን የዘጸአት ታሪክ የተፈጸመው ልክ በመጽሐፍ ቅዱስ እንደተጻፈው አይደለም ይላሉ። ጊዜን በሚመለከትም ኦሪት ዘጸአት ሕዝቡ ከግብፅ የወጡበትን ትክክለኛ ቀን አልዘገበም በማለት የሚተማመኑትና ምክንያት የሚያቀርቡትም ከመጽሐፍ ቅዱስ ውጭ በከርሰ-ምድር ጥናትና በታሪካዊ መረጃዎች ላይ በመመሥረት ነው። ስለዚህ ከግብፅ የመውጣት ታሪክ የተፈጸመው በ1321-1205 ዓ.ዓ. አካባቢ እንደሆነ ይናገራሉ።

በመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ የሚያምኑ ምሁራን ከግብፅ የመውጣት ታሪክ የተፈጸመው ቀደም ብሎ ነው በማለት ቀኑን ወደ 1450 ዓ.ዓ. ይወስዱታል። ይህንን ቀን የመረጡበት ምክንያት በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ በሚገኙ ሁለት ጥቅሶች ሳቢያ ነው፤ እነርሱም፡- መሳ. 11፡26 እና 1ኛ ነገሥ. 6፡1 ናቸው።

የውይይት ጥያቄ፥ መሳ. 11፡26ና 1ኛ ነገ. 6፡1 አንብብ። እነዚህ ቁጥሮች እስራኤላውያን ከግብፅ ከወጡ በኋላ ምን ያህል ጊዜ አልፎአል ይላሉ? 

በመሳ. 11፡26 እስራኤላውያን አንዳንድ ከተሞችን ለ300 ዓመታት ይዘው እንደነበር ይናገራል። ስለዚህ ከዘመነ መሳፍንት ጀምሮ ስናየው እስራኤል ከነዓንን በኢያሱ አማካይነት ከወረሱ 300 ዓመታት አልፈዋል ማለት ነው። ይሁን እንጂ በመሳፍንት ያለውን ጊዜ ጥርት አድርጎ ለመግለጽ አስቸጋሪ ስለሆነ፥ እስራኤላውያን ከግብፅ የወጡበትን ቀን ለመወሰን አይረዳንም።

በ1ኛ ነገሥ. 6፡1 ደግሞ ከግብፅ የመውጣት ታሪክ ከተፈጸመ 480 ዓመታት ማለፋቸውን ይናገራል። ይህም ቀን እስራኤላውያን ከግብፅ የወጡበትን ጊዜ በበለጠ ቅርበት ለመወሰን ይረዳናል። ምሁራን ከተለያዩ መረጃዎች በመነሣት የሰሎሞን መንግሥት አራተኛው ዓመት 966 ዓ.ዓ. እንደሆነ አረጋግጠዋል። ስለዚህ ከግብፅ የመውጣት ታሪክ የተከናወነው ከ480 ዓመታት በፊት ከሆነ የተፈጸመው በ1446 ዓ.ዓ. አካባቢ ነው ማለት ነው። ይህም እስራኤላውያን ከግብፅ የወጡበት ጊዜ እንደሆነ ልንጠራጠር የምንችልበት ምክንያት የለም። 

(ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የብሉይ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)

Leave a Reply

Discover more from

Subscribe now to keep reading and get access to the full archive.

Continue reading