ዘዳግም 1-11

የውይይት ጥያቄ፥ ሀ) በምድራችንም ሆነ በዓለም ላይ ያሉትን አብያተ ክርስቲያናት ታሪክ ማወቅ አስፈላጊ የሚሆነው ለምንድን ነው? ለ) ባለፉት 20 ዓመታት የተፈጸመውን የቤተ ክርስቲያንህን ታሪክ በአጭሩ ጻፍ። ሐ) የተፈጸሙት መልካምና ክፉ ነገሮች ምንድን ናቸው? መ) የቤተ ክርስቲያንህን ታሪክ ማወቅ ማድረግ ስለሚገባህ ነገርና መውሰድ ስላለብህ ጥንቃቄ ለማስገንዘብ እንዴት ይረዳሃል?

ታሪክን፥ በተለይም ደግሞ የአብያተ ክርስቲያኖቻችንን ታሪክ ማወቅ ለሁላችንም ቢሆን በጣም ጠቃሚ ነው። ታሪክ ከታላላቅ መምህራኖቻችን አንዱ ነው። ታሪክ በተከታታይ ድርጊቶች ላይ የተመሠረተና የተቀናጀ ነው። እነዚህ ድርጊቶችና ለድርጊቶች መፈጸም ምክንያት የሆኑ ነገሮች መልካም አስተማሪዎች ናቸው። ለምሳሌ በእኛ ታሪክ ውስጥ የተፈጸሙ መልካም ነገሮች አሉ፤ ለሌሎች ወንጌልን የመንገር መልካም መንገዶች ታይተዋል፤ እነዚህ ነገሮች ዛሬም ለሌሎች ወንጌልን ለመናገር መመሪያ ሊሆን የሚችሉ መልካም ተግባራት ናቸው፤ ነገር ግን በሁሉም አብያተ ክርስቲያናት አሳዛኝ የሆኑ ድርጊቶች ተፈጽመዋል። የሐሰት ትምህርቶች ተስፋፍተዋል፤ በመሪዎች መካከል ቤተ ክርስቲያንን የሚከፋፍሉ ልዩነቶች ወዘተ. ታይተዋል። እነዚህን ነገሮች ልንመረምርና ምክንያታቸውን ልንረዳ፥ እንዳይደገምም ልንጠነቀቅ ወይም ልናሻሽላቸው ይገባል። አንድ ሰው እንደተናገረው፡- ታሪካችንን በተለይም ስሕተታችንን የማናውቅ ከሆነ ስሕተቶቻችንን መደጋገማችን አይቀርም። በየቤተ ክርስቲያኖቻችን የሚፈጸሙ ነገሮችን ሁልጊዜ መመርመር አለብን። መልካም ናቸውን? ለቤተ ክርስቲያንና ለወንጌል መስፋፋት ሥራ ወሳኝ ናቸው? እስካሁን እያደረግን ባለነው ነገር ልናሻሽላቸው የሚገቡ ነገሮች ወይም የምናደርጋቸው ነገሮች በተሻለ መንገድ ለማካሄድ እያደረግን ያለው ጥረት ምንድን ነው? እንዳይጠፉ ወይም እንዳይበላሹ ልንጠነቀቅላቸው የሚገቡ፥ ለቤተ ክርስቲያን በጣም አስፈላጊ ነገሮች ምንድን ናቸው? በማለት እየጠየቅን ተገቢውን ነገር ከታሪክ መማር አለብን። ያለፈውን ነገር ብቻ በማውሳት የታሪክ ባሪያዎች መሆን የለብንም፤ ነገር ግን ታሪካችንን ለጊዚያችን በሚስማማ መንገድ ለእግዚአብሔር ከሁሉ የላቀ ክብርን እንዲያመጣ ልንጠቀምበት ይገባል።

የውይይት ጥያቄ፦ ሀ) ከቤተ ክርስቲያንህ ነባር አባሎች መካከል ለአንዱ ቃለ መጠይቅ አድርግ። ቁልፍ የሆኑ የቤተ ክርስቲያንህን የቀድሞ ታሪኮች ጻፍ። ለ) የቤተ ክርስቲያናችንን የቀድሞ ታሪክ ማወቅ ለአሁኑ ዘመን የሚጠቅመው እንዴት ነው? ) ቤተ ክርስቲያን አባሎችዋ ታሪኳን እንዲያውቁና እንዲመዘግቡ ምን ማድረግ አለባት? 

አብዛኛው የብሉይ ኪዳን ክፍል ታሪክ ነው። እስራኤላውያን የእግዚአብሔር ሕዝብ እንደመሆናቸው መጠን ራሳቸውን እንዲያሻሽሉ የሚረዳ ታሪክ ነው። እግዚአብሔር በእነርሱ ወገን ሆኖ ሲሠራ ታላቅ ኃይል ያለው መሆኑን ለእስራኤላውያን የሚያስታውስ ታሪክ ነበር። አባቶቻቸው እንዳደረጉት በኃጢአት እንዳይወድቁ፥ ስለ መንፈሳዊ ውድቀት ግንዛቤ እንዲኖራቸው የሚያደርግ ማስጠንቀቂያም ነው። የአይሁድ ባሕልና ታሪክ ከእኛ የተለየ ቢሆንም፥ እግዚአእብሔርን በሚያስከብር መንገድ እንዴት መመላለስ እንደሚቻል ከመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ መማር እንችላለን።

አይሁድ ታሪክን መረዳት እንዳለባቸው ሙሴ ተገነዘበ፡፡ ስለዚህ ሕጉን ለሚቀጥለው ትውልድ መድገም ከመጀመሩ በፊት፥ የእስራኤል ሕዝብ ከግብፅ ከወጡ በኋላ ስላሳለፉት ነገር አጠር ያለ ታሪክ አቀረበ።

የውይይት ጥያቄ፡- ዘዳግ.1-11 አንብብ። ሀ) ሙሴ ለእስራኤላውያን ያስታወሳቸውን ዋና ዋና ታሪካዊ ድርጊቶች ዘርዝር፡ ለ) ሙሴ ስለ እግዚአብሔር በእነዚህ ምዕራፎች ውስጥ የሚያስተምረን ነገር ምንድነው? ሐ) በዚህ ክፍል የቀረቡትን ዋና ዋና ትእዛዛትና ከሕይወታችን ጋር እንዴት እንደሚዛመድም ጥቀስ። በቤተ ክርስቲያንህ ውስጥ ስብከት መስጠት የሚያስችሉ የተለያዩ ጥቅሶችና መንፈሳዊ መመሪያዎች ያሉባቸውን ዋና ዋና ክፍሎች ዘርዝር።

ሙሴና የእስራኤል ሕዝብ በተስፋይቱ ምድር ትይዩ በሞዓብ ሜዳማ ስፍራዎች ሰፈሩ። ሙሴ የእስራኤል ሕዝብ ወደ ተስፋይቱ ምድር የሚገቡበትና ወረራ በማካሄድ የሚይዙበት ጊዜ አሁን መሆኑን አውቆ ነበር። ወደ ከነዓን ከመግባታቸው በፊት ግን ሙሴ ከእግዚአብሔር ጋር ያላቸውን ቃል ኪዳን ለአዲሱ የእስራኤል ትውልድ በማስታወስ ቃል ኪዳኑን እንደገና ሊያጸና ፈለገ። ኦሪት ዘዳግም በዚህ ቃል ኪዳን ሁለተኛው የእስራኤል ትውልድና ከእግዚአብሔር ጋር የተሳሰሩበት ታሪክ የተመዘገበበት መጽሐፍ ነው።

  1. የእስራኤል ታሪክ (ዘዳ.1-3)

ለቃል ኪዳኑ መግቢያ ይሆን ዘንድ ሙሴ ያለፈው 40 ዓመት ታሪካቸውን ለእስራኤል ሕዝብ ያስታውሳቸዋል። እግዚአብሔር ከግብፅ እንዴት እንዳወጣቸው በዓይናቸው ያዩና መመስከር የሚችሉ ሦስት ሰዎች ብቻ አሁን በሕይወት ይገኙ ነበር። እነርሱም ሙሴ፥ ኢያሱና ካሌብ ነበሩ። አዲሱ ትውልድ ያለፈውን ታሪካቸውን የመርሳት አደጋ ያሠጋቸው ነበር፤ ስለዚህ ሕዝቡ በእምነትና በታዛዥነት በእግዚአብሔር ፊት ይመላለሱ ዘንድ፥ ለማበረታታት ሙሴ የ40 ዓመት ታሪካቸውን የሚመለከቱበትን ቁልፍ አሳቦች ይነግራቸዋል።

በኦሪት ዘዳግም ውስጥ የሲና ተራራ ብዙ ጊዜ የኮሬብ ተራራ በመባል ይታወቃል። በዚህ ክፍል የተጠቀሱ የሚከተሉትን ነገሮች ተመልከት፡-

ሀ. የእስራኤልን ሕዝብ በመምራት ሥራ ውስጥ ያግዙት ዘንድ ሙሴ መሪዎቹን ሾመ።

የውይይት ጥያቄ፡- ዘዳ.1፡16-18 አንብብ። ሀ) በዚህ ስፍራ የተሰጡት መመሪያዎች ዛሬም የቤተ ክርስቲያን መሪዎች ይከተሉአቸው ዘንድ ጠቃሚነታቸው እንዴት ነው? ለ) የቤተ ክርስቲያን መሪዎች እነዚህን መመሪያዎች የማይጠቀሙባቸው አንዳንድ ሁኔታዎች ምንድን ናቸው?

ለ. 12ቱ ሰላዮች የተስፋይቱን ምድር አይተው እንዲመለሱ ተልከው ነበር። እስራኤል ግን በእግዚአብሔር መታመንና ወደ ተስፋይቱ ምድር መግባት እምቢ አለች።

ሐ. የእስራኤላውያን በምድረ በዳ መንከራተት፥ 

መ. ሴዎንና ዐግ ዖግ የተባሉት ሁለት የከነዓናውያን ነገሥታት መሸነፍና የእስራኤላውያን ምድሪቱን መከፋፈል። 

  1. እስራኤላውያን እግዚአብሔርን ለማምለክ መሠረት የሚሆኑ የዋና ዋና ሕግጋት መግቢያ (ዘዳግ.4-11)

በዚህ ክፍል ውስጥ የሚገኙ ስድስት ዋና ዋና ትምህርቶችን ተመልከት፡-

ሀ. ከእግዚአብሔር የሆነ በረከትና እውነተኛ ጥበብ ለእርሱ ፍጹም በመታዘዝ ይገኛሉ። 

ለ. በከነዓን ምድር የተለመደውን የጣዖት አምልኮ እንዳይለማመዱ ከባድ ማስጠንቀቂያ ተሰጣቸው። «እግዚአብሔር የሚባላ እሳት» ስለሆነ ይህ በእስራኤላውያን ላይ ፍርድን ያመጣል። እግዚአብሔር የፍቅርና የጸጋ አምላክ ስለሆነ፥ እንደ ቀላል ቆጥረን ኃጢአት ብናደርግም አይፈርድብንም ብለን ልናስብ አይገባንም።

እግዚአብሔር ሊፈራም ሊወደድም ይገባል። እግዚአብሔር ብቻውን እውነተኛ አምላክ ስለሆኝ፥ እርሱን ብቻ ያመልኩ ዘንድ እስራኤላውያን ከፍተኛ ጥንቃቄ ማድረግ ነበረባቸው።

የውይይት ጥያቄ፡- ብዙ ጊዜ እግዚአብሔር «የሚባላ እሳት» መሆኑን የምንረሳውና ስለ ቅጣት ሳናስብ ቀርተን እርሱን የማንታዘዘው እንዴት ነው?

ሐ. የሕግጋት ሁሉ መሠረት የሆኑት አሥርቱ ትእዛዛት እንደገና መቅረብ። 

መ. ለእግዚአብሔር የመታዘዝ ትክክለኛው ምክንያት ለእርሱ ያለን ፍቅር መሆን አለበት። በሁለንተናቸው እግዚአብሔርን መውደድ ነበረባቸው። የእግዚአብሔርን ትእዛዛት እርስ በርስ መማማርና ልጆቻቸውንም ማስተማር እንዳለባቸው እርግጠኞች መሆን ነበረባቸው። ሙሴ የእግዚአብሔርን በረከት ከተቀበሉና መማማርና በቤቶች መኖር ከጀመሩ በኋላ እግዚአብሔርን እንዳይዘነጉ አስጠንቅቋቸዋል (ዘዳግ. 6፡10-12 ተመልከት)። 

የውይይት ጥያቄ፡- ከስደትና ከችግር ጊዜ ይልቅ በሰላምና በብልጽግና (ዘመን እግዚአብሔርን ማስታወስስ የሚከብደው ለምንድን ነው?

ሠ. ከእግዚአብሔር መንገድ ዞር እንዳያደርጉአቸው በከነዓን ምድር የሚኖሩትን አሕዛብ ሁሉ ማጥፋት ነበረባቸው።

ረ. እውነተኛ ታዛዥነት ሕግን በውጫዊ መንገድ መከተል ብቻ ሳይሆን የልብ መለወጥንም ያካትታል። ሥጋዊ የአካል ክፍላቸውን (ሸለፈታቸውን) ብቻ ሳይሆን፥ ልባቸውንም መግረዝ ነበረባቸው። መታዛዝ የሚጀምረው እግዚአብሔርን ከመፍራት፥ በመንገዱ ለመሄድ ከመወሰን፥ ከሁሉ በላይ ደግሞ ወደ መታዘዝ ከሚመራቸው በልባቸው ከሚኖር ፍቅር ነበር። 

የውይይት ጥያቄ፣ ሀ) ዛሬ ልባችን እንዴት እንደተገረዘና በፍጹም ልባችን እርሱን እንደወደድነው ማሳየት የምንችልበትን ምሳሌዎች ስጥ። ለ) በሁለንተናችን እግዚአብሔርን እንዴት መውደድ እንችላለን? 

(ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የብሉይ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)

Leave a Reply

%d