የመጽሐፈ መሳፍንት ዓላማ

እስራኤል በጠላቶችዋ ለምን ተሸነፈች? ያለማቋረጥ በባርነት ውስጥ የሆነችውስ ለምንድን ነው? እስራኤላውያን እግዚአብሔር የሰጣቸውን የተስፋ ቃል ኪዳን በረከት ያልተለማመዱት ለምንድን ነው? እግዚአብሔር ሊያድናቸው ስላልቻለ ነውን? የከነዓናውያንና የአሕዛብ አማልክት ብርቱ ስለሆኑ ነውን?

የመጽሐፈ መሳፍንት ጸሐፊ ለመመለስ የሚሞከራቸው ጥያቄዎች እነዚህ ናቸው። የመጽሐፈ መሳፍንት ጸሐፊ እስራኤላውያን ያ ሁሉ ሥቃይ የደረሰባቸው ለምን እንደሆነ ሊገልጥላቸው ይፈልግ ነበር። በመጽሐፈ መሳፍንት ውስጥ እስራኤላውያን ለምን እንደተሸነፉና በመከራ ውስጥ እንደተዘፈቁ የሚያሳዩ ሁለት ምክንያቶች ተሰውረው እናገኛለን፡

  1. እስራኤላውያን ብዙ መከራና ችግር የደረሰባቸው ለእግዚአብሔር ቃል ኪዳን በታዛዥነት ስላልኖሩ ነው። እግዚአብሔር እንዳልተጠነቀቀላቸው በማሰብ እርሱን ከመውቀስ ይልቅ፥ እስራኤላውያን ለወደቁበት አስጊ ሁኔታ ራሳቸውን ብቻ መውቀስ ነበረባቸው። እውነተኛ ንጉሣቸውን እግዚአብሔርን ትተው፥ የከነዓናውያንን አማልክት፥ ሥነ-ምግባራት፥ ሃይማኖታዊ ጉዳዮችና የአኗኗር ዘይቤዎች ስለተከተሉ እግዚአብሔር እየቀጣቸው ነበር። በኦሪት ዘዳግም እንደተጠቀሰው፥ ለእግዚአብሔር አለመታዘዝ ከእግዚአብሔር ዘንድ ፍርድን አስከተለባቸው። በመጽሐፈ መሳፍንት ውስጥ በተደጋጋሚ እንደምናነበው «የእስራኤል ልጆች በእግዚአብሔር ፊት ክፉ ነገርን አደረጉ» (መሳ. 2፡11፤ 3፡7፥ 12፤ 4፡1 ወዘተ.)። በመጽሐፈ መሳፍንት የሚገኙት የመጨረሻዎቹ ሁለት ታሪኮች የሚያሳዩት የእግዚአብሔር ሰዎች ምን ያህል ከፍተው እንደነበር ነው።

የሚያሳዝነው የእግዚአብሔር ሕዝብ በታሪክ ሁሉ በፊቱ የተቀደሰ ኑሮ ከመኖር ወደኋላ ማለታቸው ነው። በዚህ ፈንታ ዓለምን መሰሉ። ውጤቱም በራሳቸው ላይ የእግዚአብሔርን ፍርድ ማስከተል ሆነ። እግዚአብሔር በረከቱን ከእነርሱ ወሰደ። ወደ እግዚአብሔር መመለስን እምቢ ሲሉ፥ እግዚአብሔር ለምርኮ አሳልፎ ይሰጣቸውና በዓለም እንዲሸነፉ ያደርግ ነበር። ይህም ሆኖ ሳይመለሱ ሲቀሩ፥ እግዚአብሔር ይተዋቸው ነበር። በትንቢተ ሕዝቅኤል የእግዚአብሔር ክብር ኢየሩሳሌምንና ቤተ መቅደሱን እንዴት እንደተወ እናነባለን (ሕዝ. 10፡ 11፡23)። በአዲስ ኪዳን በጳውሎስ ከተጀመሩት አብዛኛዎቹ አብያተ ክርስቲያናት ቅድስናቸውን ስላጡ በመጨረሻ ተደመሰሱ ወይም ወደ መስጊድነት ተለወጡ፤ ስለዚህ አሁንም ቢሆን ያለማቋረጥ እርሱን ከተውንና እንደ ዓለም መኖር ከጀመርን እግዚአብሔር እኛንም ይተወናል።

የውይይት ጥያቄ፥ ሀ) ዛሬም ቢሆን ዓለምን የመምሰል አዝማሚያ በአብያተ ክርስቲያኖቻችን ውስጥ የሚታየው እንዴት ነው? ለ) በዘመነ መሳፍንት ከነበረው የእስራኤላውያን ታሪክ እንደ ማስጠንቀቂያ ልንወስደው የሚገባን ነገር ምንድን ነው? ሐ) እኛ ክርስቲያኖች ዓለምን መምሰል እንደሌለብን ለማስተማር መጽሐፈ መሳፍንትን እንዴት ልንጠቀምበት እንችላለን?

  1. እስራኤላውያን ከፍተኛ መከራና ችግር የደረሰባቸው ከእግዚአብሔር ጋር ያላቸውን ቃል ኪዳን ይጠብቁ ዘንድ የሚያስችላቸው ብቁ መሪ ስላላገኙ ነው። በመጽሐፈ መሳፍንት ኋለኛ ክፍል እንዲህ የሚል ቃል እናገኛለን፡- «በዚያም ዘመን ከእስራኤል ዘንድ ንጉሥ አልነበረም፤ ሰው ሁሉ በፊቱ መልካም መስሎ የታየውን ያደርግ ነበር» (መሳ. 21፡25)። እንደ ጸሐፊው አመለካከት፥ የእግዚአብሔር ሕዝብ የተሸነፉበትና በኃጢአት የወደቁበት አንዱ ምክንያት ጠንካራ መሪ ወይም የሚመራቸው ንጉሥ ስላልነበራቸው ነው። ከእግዚአብሔር ጋር የነበራቸውን የቃል ኪዳን ግንኙነት ለመጠበቅ የነገድ አመራር በቂ አልነበረም።

መጽሐፈ መሳፍንት የተጻፈው ምናልባት በዳዊት ጊዜ ስለሆነ ጸሐፊው እግዚአብሔርን የሚፈራ ጠንካራ መሪ፥ ሕዝቡ ለእግዚአብሔር ታማኝ ሆኖ ይኖር ዘንድ የሚጫወተውን ከፍተኛ ሚናና የሚሰጠውን ጥቅም ታላቅነት ተመልክቶ ይሆናል። ከኋለኛው ታሪክ እንደምንገነዘበው፥ ንጉሥ እግዚአብሔርን የሚፈራ ካልሆነ ሕዝቡ ወዲያውኑ እግዚአብሔርን ይተዋሉ። መጽሐፈ ነገሥት የሚያሳየን እስራኤል ነገሥታትን ማግኘቷ ብቻ ቃል ኪዳንን ለመጠበቅና ከእግዚአብሔር ፍርድ ለማምለጥ በቂ እንዳልሆነ ነው።

የእስራኤል ዋና ችግር ለሰማያዊ ንጉሥዋ አለመታዘዝዋ ነው። ምድራዊው ንጉሥ እግዚአብሔርን የሚፈራ ከሆነ፥ ሕዝቡ ለቃል ኪዳኑ ታዛዥ ሆኖ እንዲኖር ይረዳል። ንጉሡ ታዛዥ ባይሆንም እንኳ፥ እስራኤላውያን ለሰማያዊ ንጉሣቸው መታዘዛቸውን መቀጠል ነበረባቸው፤ ነገር ግን ልክ በመሳፍንት ዘመን እንደ ነበረው ፈጥነው በኃጢአት ይወድቁ ነበር።

የውይይት ጥያቄ፦ ሀ) ሕዝቡ ለእግዚአብሔር እየታዘዙ እንዲኖሩ እግዚአብሔርን ስለሚፈራ መሪ አስፈላጊነት ይህ ምን ያስተምረናል? ለ) መሪው ወደየትኛውም አቅጣጫ ቢመራ፥ እያንዳንዱ ክርስቲያን ግን የግል ግንኙነቱን ከእግዚአብሔር ጋር መጠበቅ እንዳለበት ይህ ምን ያስተምረናል?

መጽሐፈ መሳፍንት የሚያስተምረን የእግዚአብሔር ሰዎች በትእዛዙ በማይመላለሱበት ጊዜ፥ ፍርድን ብቻ ሳይሆን፥ ጥፋትንም ጭምር በራሳቸው ላይ እንደሚያመጡ ነው። ከመሳፍንት 17-21 ያለው ክፍል ዋና ትምህርት ለቃል ኪዳኑ አለመታዘዝ በሚኖርበት ጊዜ ሕዝቡ እግዚአብሔርን በመተው ሐሰተኛ አማልክትን እንደሚያመልኩ ነው። እግዚአብሔርን በሚተዉበት ጊዜ የቅን ፍርድ ጉድለትና የእርስ በርስ መጠፋፋት ይከሰታል። ፈሪሀ እግዚአብሔር በማይኖርበት ስፍራ፥ ፍትሐዊ ሕግጋት አይኖሩም፤ ውጤቱም የሕዝቡ ሁሉ መሠቃየት ነው። የመጽሐፍ ቅዱስ መመሪያዎች በሕጎቻቸው ውስጥ እንዲሠሩ ያልፈቀዱ ሕዝቦች ያጋጠሟቸው መቅሠፍት፥ የፍርድ መዛባት፥ ጉቦኝነት፥ ጦርነትና የመሳሰሉት ነገሮች ናቸው።

የውይይት ጥያቄ፥ ይህ በኢትዮጵያ እውነት መሆኑን እንዴት አየህ?

በመጽሐፈ መሳፍንት ውስጥ ሁለት ዋና ዋና የእግዚአብሔር ሥዕላዊ ሁኔታ እናያለን። የመጀመሪያው፥ የእግዚአብሔር የሥነ – ሥርዓት እርምጃ ነው። ሕዝቡ በኃጢአት በሚወድቁበት ጊዜ እግዚአብሔር አስቸጋሪ ነገሮችን ወደ ሕይወታቸው በማምጣት ሥነ ሥርዓትን (ዲስፕሊንን) ያስተምራቸው ነበር። የእግዚአብሔር ፍላጎት ሊያጠፋቸው አልነበረም፤ ነገር ግን ሕዝቡ ከኃጢአት እንዲርቁና እግዚአብሔርን በሚያስከብር መንገድ ለሕዝቡ ሁሉ የሚጠቅም ኑሮ እንዲኖሩ ነበር፤ (ዕብ. 12፡4-11 ተመልከት)።

በሁለተኛ ደረጃ በምሕረት የተሞላውን የታጋሹን የእግዚአብሔር ሥዕላዊ ሁኔታ እናያለን። እግዚአብሔር ሕዝቡ በሚተዉት ጊዜ በጽድቅ በመፍረድ ወዲያውኑ ሊቀጣቸው ይችል ነበር። ይህንንም ቢያደርግ ፍጹም ትክክል ነበር። ነገር ግን እግዚአብሔር ለብዙ መቶ ዓመታት በትዕግሥት በመሥራት ይቅርታውንና በሕይወታቸው ላይ የሚደርሰውን ችግር ልባቸውን ወደ እርሱ ለመመለስ ይጠቀሙበት ዘንድ ሞክሮ ነበር። እግዚአብሔር ሕዝቡ ታማኝ ባልሆኑበት ጊዜ እንኳ ለእነርሱ ታማኝ ነበር። ወደ እርሱ በጮኹ ጊዜ ጸሎታቸውን በመመለስ፥ እነርሱን ከባርነት ነፃ ለማድረግ የሚያስፈልገውን ያደርግ ነበር። እግዚአብሔር በምሕረቱ ነቢያትን እየላከ ያስጠነቅቃቸውና ለማውጣት መሳፍንትን ያስነሣላቸው ነበር።

የውይይት ጥያቄ፥ ሀ) እግዚአብሔር በአሁኑ ዘመንም ምሕረቱንና ትዕግሥቱን እያሳየን ያለው እንዴት ነው? ለ) የእግዚአብሔር ምሕረት በሕይወትህ የታየው እንዴት ነው? ሐ) ለአንተ ስላለው ትዕግሥት፥ ምሕረትና ጸጋ እግዚአብሔርን አመስግነው። 

(ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የብሉይ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)

1 thought on “የመጽሐፈ መሳፍንት ዓላማ”

Leave a Reply

Discover more from

Subscribe now to keep reading and get access to the full archive.

Continue reading