የብሉይ ኪዳንን የትንቢት መጻሕፍት በምናጠናበት ጊዜ ሁሉ ሕዝቡ የወደፊቱን ነገር በተስፋና በጉጉት ይጠብቁ እንደነበር ተመልክተናል። ምንም እንኳ የእግዚአብሔር ሕዝብ በስደትና በመከራ ውስጥ ቢሆኑ ወይም አይሁድ በምድር ዙሪያ ሁሉ ተበትነው የሚኖሩ ቢሆኑም የእግዚአብሔር ቃል የወደፊቱን ነገር እንዲመለከቱ ያበረታታቸው ነበር፡፡ በብሉይ ኪዳን ውስጥ ከሚገኙ የወደፊት ተስፋዎች መካከል አይሁድ ይጠብቁት የነበረው ዋና ተስፋ የመሢሑን መምጣት ነበር። የእስራኤል ንጉሥና የምድር ሁሉ ገዥ እንደመሆኑ ለእግዚአብሔር ሕዝብ ሁሉንም ነገር ያስተካክላል። ይህ ቃል ኪዳን በጨለማ ውስጥ እንደሚበራ ብርሃንና በትልቅ ችግር ውስጥ እንደሚሰማ አበረታች የተስፋ ቃል ነበር።
የመጨረሻው የብሉይ ኪዳን መጽሐፍ ትንቢተ ሚልክያስ ስለ መሢሑ መምጣትና ከእርሱ በፊት ስለሚመጣው ኤልያስ የተስፋ ቃል በማስተላለፍ ይጠቃለላል። እግዚአብሔር ከሚልክያስ በኋላ አዳዲስ ትንቢቶቹን የሚናገሩ ነቢያት አልላከም። እነዚህም ዓመታት 400 የጸጥታ ዓመታት በመባል ይታወቃሉ። በእነዚህ 400 ዓመታት አይሁዶች የተሰጣቸውን ተስፋ ፍጻሜ ሲጠባበቁ ኖረዋል። ከ400 ዓመታት በኋላ ግን በሚልክያስ እንደተተነበየው በድንገት በምድረ በዳ የሚጮህ ሰው ድምፅ የተባለለት መጥምቁ ዮሐንስ የነቢያት መልእክት ይፈጸም ዘንድ የጊዜውን መድረስ በሚመለከት አዋጅ መናገር ጀመረ። መሢሑ መጣ። በብሉይ ኪዳን ሲጠበቁ የነበሩ ነገሮች በሙሉ መፈጸም ነበረባቸው። የሚያሳዝነው ነገር፥ መሢሑ፥ ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ በመጣ ጊዜ ሕዝቡ ሊቀበሉት አልተዘጋጁም ነበር፤ ስለዚህ ሳይቀበሉት ቀሩ።
አዲስ ኪዳን ይህንን የተስፋ ላይ ሐረግ ከብሉይ ኪዳን ቀጥሎአል። ዳሩ ግን የመጀመሪያ አመጣጡን ከልብ በማመን ምትክ ኢየሱስ ዳግም በሚመለስበት ጊዜ ያተኩራሉ። በዚያን ጊዜ በፍጥረታት ሁሉ ላይ በመግዛት፥ በብሉይ ኪዳን ውስጥ የተጻፉትን የበረከት ተስፋዎች በሙሉ ይፈጽማል። የኢየሱስ ክርስቶስን መመለስ የሚመለከተው ተስፋ ለእኛ ለክርስቲያኖች በስደት ጨለማ ውስጥ በምንሆንበት ጊዜ ብርሃን የሚሆነን «ተስፋ» ነው። ክርስቲያኖች በኢየሱስ ዳግመኛ መምጣት ቃል እርስ በእርስ እንድንጽናና ታዘናል (1ኛ ተሰሎንቄ 4፡13-18)። ክርስቲያኖች በዚህ በሚያልፍ የዓለም ነገር ላይ እምነታቸውንና ተስፋቸውን መጣል ጨርሶ የለባቸውም። ዜግነታቸው ሰማያዊ መሆኑን፥ ወደ መንግሥተ ሰማያት በመጓዝ ላይ ያሉ መናንያን መሆናቸውን፥ የእግዚአብሔር በረከት በሙላት የሚፈጸመው በሰማይ እንደሆነ ዘወትር ሊያስታውሱ ይገባል።
የውይይት ጥያቄ፥ ሀ) ክርስቲያኖች በከባድ ችግርና መከራ ውስጥ በሚሆኑበት ጊዜ ኢየሱስ ሲመለስ የሚያገኙትን ብሩህ ፍጻሜ፥ ተስፋ ማድረግ የሚያስፈልጋቸው ለምንድን ነው? ለ) ኢየሱስ ሲመለስ የሚፈጸሙልንን አንዳንድ የተስፋ ቃሎች ዘርዝር? ሐ) ክርስቲያኖች ወደ ሰማይ አገራቸው በሚደርሱበት ጊዜ ሊፈጸምላቸው ከተገባላቸው ተስፋ ይልቅ በዚህ ምድር ሊቀበሏቸው ባሉት በረከተች ላይ ብዙ ጊዜ የሚያተኩሩባቸውን አንዳንድ መንገዶች ዘርዝር።
የትንቢተ ሚልክያስ ጸሐፊ
ምንም እንኳ መጽሐፈ ዜና መዋዕል፥ ዕዝራና ነህምያ ከሚልክያስ በኋላ ሊጻፉ ቢችሉም፥ በብሉይ ኪዳን ውስጥ የእግዚአብሔርን ቃል የጻፈ የመጨረሻ ነቢይ ሚልክያስ ነበር። በመጽሐፉ ጸሐፊ ማንነት ላይ ምሁራን የተለያዩ አሳቦች አሏቸው። ስለዚህ ጉዳይ ሁለት ዐበይት አመለካከቶች አሉ፡-
1. በዕብራይስጥ «ሚልክያስ» የሚለው ስም ትርጉም «መልእክተኛዬ» ማለት ነው። ይህ ቃል አንዳንድ ጊዜ ነቢያትን፥ ካህናትንና መላእክትንም እንኳ ለመግለጥ የሚጠቅም ነበር። ስለዚህ ብዙ ምሁራን ሚልክያስ 1፡1 «የእግዚአብሔር ቃል ለእስራኤል በመልእክተኛው በኩል መጣ» ተብሎ መተርጐም አለበት ይላሉ። ይህ መልእክተኛ (ነቢይ) ማን እንደሆነ አይታወቅም። በአብዛኛዎቹ የነቢያት መጻሕፍት በተለየ ሁኔታ፥ ነቢዩ መቼ እንደኖረና የእግዚአብሔርን ቃል እንደተናገረ ወይም የማን ልጅ እንደሆነ የሚገልጹ የተለመዱ እውነቶች አልተሰጡም። ይህም ትንቢተ ሚልክያስ የተጻፈው በአንድ ባልታወቀ የእግዚአብሔር መልእክተኛ ነው የሚለውን አሳብ ይደግፋል። የሴፕቱዋጀንት ትርጉም የሚልክያስን ስም ሳይጠቅስ የእግዚአብሔር ቃል በመልእክተኛው በኩል እንደተላለፈ አድርጎ ይህን ጥቅስ ይተረጉማል።
2. ሌሎች ምሁራን ደግሞ ጸሐፊው “ሚልክያስ” ተብሎ ከመጠራቱም፥ መልእክቶቹን ያሰፈረው ራሱ ሚልክያስ ወይም ሌላ አንድ ጸሐፊ ነው ይላሉ። ከዚህ ሌላ ስለሚልክያስ የምናውቀው ምንም ነገር የለም። የአይሁድ ትውፊት ሚልክያስ የኖረው በሐጌና በዘካርያስ ዘመን እንደነበር ይናገራል። ሚልክያስ የታላቁ ምኩራብ የጸሐፍት ጉባኤ አባላትና ከባቢሎን ምርኮ በኋላ ለአይሁድ የሃይማኖት ሕይወት እውቅና ለመስጠት እገዛ ካደረጉት የአይሁድ መሪዎች አንዱ ነበር ይላሉ።
ትንቢተ ሚልክያስ የተጻፈበት ጊዜ
ሚልክያስ ይህን መጽሐፍ መቼ እንደጻፈው ስለማይናገር በይሁዳ ያገለገለው መቼ እንደሆነ መጽሐፉን በመመርመር መረጃ ማግኘት አለብን። አሁንም ምሁራን በዚህ ጉዳይ ላይ ያላቸው አሳብ የተለያየ ነው። አንዳንዶች ሚልክያስ የኖረውና ያገለገለው ዕዝራና ነህምያ በኖሩበት ዘመን ነው ይላሉ (450-430 ዓ.ዓ.)። በሚልክያስና በነህምያ ዘመን የነበረውን የአይሁዶች መንፈሳዊ ሁኔታ ብንመረምር ተመሳሳይ ነበረ። ለምሳሌ በሦስቱም መጻሕፍት ማለት በዕዝራ፥ በነህምያና በሚልክያስ ከአሕዛብ ጋር የተደረጉ ጋብቻዎች ችግር፥ ድሆችን ያለ አግባብ መበደል፥ ሰንበትን ባለማክበር ለሕግ ተገዥ አለመሆንና የቤተ መቅደሱ አገልግሎት ችላ መባል በጋራ ከተጠቀሱ ነገሮች ጥቂቶቹ ነበሩ።
ሌሎች ምሁራን ግን የዕብራይስጡን የአጻጻፍ ስልትና ሌሎች የቋንቋ ጉዳዮችን በመመልከት ሚልክያስ የተጻፈው ቀደም ሲል ዕዝራ ወደ ይሁዳ ከመምጣቱ በፊት ነው ይላሉ፤ የተጻፈውም ከ500-475 ዓ.ዓ. ነው ብለው ያስባሉ።
ትንቢተ ሚልክያስ የተጻፈው ከ475-425 ዓ.ዓ. ባለው ጊዜ ነው ማለት ከሁሉም የተሻለ አሳብ ነው።
(ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የብሉይ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)
የመመዘኛ ጥያቄዎችን ለማግኘት ከታች ያለውን ሊንክ (መስፈንጠሪያ) ይጫኑ፡፡