የትንቢተ ሚልክያስ ታሪካዊ ሥረ-መሠረት

ትንቢተ ሚልክያስ በዕዝራና በነህምያ ታሪክ ዘመን አካባቢ የተጻፈ ነው። ከትንቢተ ሐጌና ዘካርያስ ጥናታችን እንደሚታወሰው እነዚህ ሁለቱ፥ ነቢያት አይሁዶች ቤተ መቅደሱን እንዲሠሩ ያበረታቱ ነቢያት ነበሩ። በመጨረሻ በ516 ዓ.ዓ. የቤተ መቅደሱ ሥራ ተጠናቀቀ። አይሁድ የተሰጧቸውን የተስፋ ቃላት ፍጻሜ ይጠባበቁ ነበር። መሢሑ እንደሚመጣ ቢጠባበቁም፥ መምጣቱን በሚመለከት አንዳችም ምልክት አልታየም ነበር። ከእግዚአብሔር በረከትን በመቀበል በቁሳዊ ነገሮች እንደሚበለጽጉ አስበው ነበር፤ ዳሩ ግን እስካሁን ድረስ ድሆች ነበሩ። ከአሕዛብ መንግሥታት ነፃ ለመሆንና ራሳቸውን ለመቻል ፈልገው ይጠባበቁ ነበር፤ ነገር ግን እስካሁን ድረስ በፋርስ መንግሥት ውስጥ እጅግ አነስተኛና ከቁጥር የማይገባ አንድ ክፍለ ሀገር ነበሩ፡፡ ታላቅ ሕዝብ እንደሚሆን አስበው ነበር፤ ነገር ግን ብዙ አይሁድ ወደ አገራቸው ለመመለስ ፈቃደኞች ሳይሆኑ ቀሩ። የቤተ መቅደሱን ሥራ ለመጨረስ ከነበራቸው የስሜት ምጥቀት በፍጥነት በመውረድ፣ ተስፋቸው ተሟጥጦ ቅንነት በራቀው የአሳብ ማዕበል ውስጥ ተዘፈቁ። ለእግዚአብሔር የነበራቸውን መንፈሳዊ ግለት አጡ። እግዚአብሔር እንደሚወዳቸው ማሳብ ተሳናቸው።

በ458 ዓ.ዓ. በፋርስ ንጉሥ በአርጤክስስ ችሮታ ካህኑ ዕዝራ ከብዙ ሺህ አይሁድ ጋር ወደ አገሩ ተመለሰ። በእርሱ መንፈሳዊ አመራር የእግዚአብሔር ሕዝብ ንስሐ ለመግባትና ለሕጉ በመታዘዝ ለመኖር ተነቃቁ።

ከአሥራ ሦስት ዓመታት በኋላ፥ ማለትም በ445 ዓ.ዓ. ነህምያ ከብዙ አይሁዶች ጋር ተመለሰና የኢየሩሳሌምን ቅጥሮች ሠራ። ሕዝቡ ቤተ መቅደሱን ይሠሩ ዘንድ እንዳስቻሉት እንደ ሐና ዘካርያስ፥ ነህምያ ሕዝቡን ሁሉ ለማሳመንና የኢየሩሳሌምን ቅጥሮች እንዲሠሩ ለማድረግ ችሎ ነበር። ከዚህም በላይ ነህምያ በይሁዳ አንዳንድ ተሐድሶዎችን ለማምጣት ችሎ ነበር። ከእነዚህም መካከል ድሆችን መርዳት (ነህምያ 5፡2-13)፥ ድብልቅ ጋብቻዎችን ማስቆም፥ ሰንበትን መጠበቅ (ነህምያ 10፡30-31) መባቸውንና አሥራታቸውን ወደ ቤተ መቅደስ ማምጣት (ነህምያ 10፡37-39) ይገኙባቸዋል። በዚህ ጊዜ ሚልክያስ ከነህምያ ጋር እየሠራ ነበር ለማለት ይቻላል።

በ433 ዓ.ዓ. ነህምያ ከንጉሥ አርጤክስስ ጋር ለመሥራት ወደ ፋርስ ተመለሰ። እርሱ በሌለበት ሕዝቡ እንደገና በኃጢአት ወደቁ። ነህምያ ከብዙ ዓመታት በኋላ በተመለሰ ጊዜ ሕዝቡ አሥራታቸውን እንደማይከፍሉ፥ ሰንበትን እንደማያከብሩ፥ ከአሕዛብ ጋር እንደሚጋቡና ካህናቱም ምግባረ ብልሹዎች እንደሆኑ ደረሰበት (ነህምያ 13፡7-31)። በትንቢተ ሚልክያስ ከተጠቀሱት አንዳንድ ተመሳሳይ ኃጢአቶች መካከል እነዚህ ይገኙባቸዋል (ሚልክያስ 1፡6-14፤ 2፡14-16፤ 3፡8-11)። ስለዚህ ሚልክያስ ያገለገለው ነህምያ ወደ ፋርስ ሄዶ ሳለ ወይም በዚሁ ጊዜ ከነህምያ ጋር ሳይሆን አይቀርም።

ኃጢአት እንደ ማግኔት በመሆኑ የእግዚአብሔርን ሕዝብ ያለማቋረጥ ይስባል፡፡ የእግዚአብሔር ሕዝቦች መንፈሳዊ ግዴለሽነትንና በኃጢአት የመውደቅ ዝንባሌን ያለማቋረጥ ካልተዋጉ በስተቀር፥ አያሌ ጊዜ ሳይፈጅ መንፈሳዊ ግለታቸውንና ቅድስናቸውን ይጥላሉ። በቤተ ክርስቲያን መሪዎች ራስ ላይ ከተጣሉት ብዙ ዐበይት ኃላፊነቶች አንዱ የእዚአብሔር ሕዝብ ለኢየሱስ የነበራቸውን የመጀመሪያ ፍቅር እንዲጠብቁና ዓለምን ከመምሰል ይልቅ በእግዚአብሔር ፊት የንጽሕና ሕይወት እንዲኖሩ ማበረታታት ነው። ነህምያና በሚልክያስ ጊዜ በእስራኤላውያን የተፈጸመው ነገር ዛሬም በቤተ ክርስቲያን ደግሞ ሊፈጸም ይችላል።

የውይይት ጥያቄ፥ ሀ) በኃጢአት የመውደቅ ዝንባሌ በምታውቃቸው ክርስቲያኖች ሕይወት ውስጥ ሲፈጸም ያየኸው እንዴት ነው? ለ) ይህን ዝንባሌ በራስህ ሕይወት ውስጥ ያየኸው እንዴት ነው? ሐ) ይህን ነገር ለማሸነፍ ምን እያደረግህ ነው? መ) የቤተ ክርስቲያን መሪ እንደ መሆንህ ሰዎች ለእግዚአብሔር ያላቸው መንፈሳዊ ግለት ከፍተኛ እንዲሆንና የቤተ ክርስቲያን አባሎች በኃጢአት እንዳይወድቁ ምን ማድረግ ትችላለህ?

(ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የብሉይ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)

የመመዘኛ ጥያቄዎችን ለማግኘት ከታች ያለውን ሊንክ (መስፈንጠሪያ) ይጫኑ፡፡

Leave a Reply

%d bloggers like this: