የመጽሐፍ ቅዱስ ሥርዓተ ትምሕርት ጥናት
«ሰው ምንድ ነው?» የሚለው ጥያቄ ያለጥርጥር እጅግ መሠረታዊ የሆነ የፍልስፍናና የሥነ-መለኮት ተግባራዊ ጥያቄ ነው። ሰዎች መጀመሪያ ከየት መጣን? ለምንስ መጣን? መሄጃችንስ ወዴት ይሆናል? የሚሉና ሌሎችም ተመሳሳይ ጥያቄዎች ናቸው። ፍልስፍና እነዚህን ጥያቄዎች ለማጥናትና መልስ ለማግኘት በየዘመናቱ በተነሱ ፈላስፋዎቹ አማካይነት የተለያዩ ሙከራዎችን አድርጓል። የብዙዎቹን ፍልስፍናዎች የአጠናን ዘዴና መልሶቻቸውን ስናይ፥ ሰዎች ለነዚህ ጥያቄዎች እርግጠኛ መልስ ለማግኘት አለመቻላቸውን እንረዳለን። ፍልስፍና ሰዎች ስለ ሰው ያሰቡትን ሊያስተምረን ሲጥር፥ መጽሐፍ ቅዱስ ግን የሰውን አፈጣጠር በማስመልከት በሥልጣን የተደገፈና የተሟላ ትምህርት ይሰጠናል። ለሌሎች መሠረታዊ ጥያቄዎችም አጥጋቢ መልስ አለው።
1. ሰው ፍጡር ነው
አንድ ሰው ስለ ሰው ዘር አመጣጥ ያለው አመለካከት ስለ ሰብአዊ ፍጡር የሚኖረውን እውቀትና አስተሳሰብ ይወስነዋል። ለምሳሌ ሰው በአዝጋሚ ለውጥ (Evolution) የመጣ ነው ብሎ ካመነ፥ የኃጢአትን አስከፊነትና የአዳኝን አስፈላጊነት ሙሉ በሙሉ ባይሰርዘው እንኳን እጅግ አቃልሎ ይመለከተዋል። በሌላ በኩል ሰው በአምላክ የተፈጠረ ነው ብሎ የሚያምን ከሆነ፥ ይህ ፅንሰ-አሳብ ሰው ኃላፊነት አለበት የሚለውን የተያያዘ አሳብ ይይዛል። ሰው በእግዚአብሔር ከተፈጠረ፥ በፈጣሪና በፍጡሩ መካከል የበላይና የበታች ግንኙነት አለ ማለት ነው። ይህ ከሆነ እንግዲህ ሰው የራሱን ዕድል በራሱ የሚወስን አይሆንም፤ ወይም ለራሱ ተጠያቂ የሆነ የመጨረሻ ባለሥልጣንም ለመሆን አይችልም። ፍጡራን በፈጣሪያቸው ተገዢ መሆናቸውን ነው የሥነ-ፍጥረት ትምህርት የሚያመለክተው። ነገር ግን ሰው ከዝቅተኛ የሕይወት አካል በአዝጋሚ ለውጥ ከተገኘ፥ ፈጣሪ ሊጠየቅበት አይችልም ማለት ነው።
የአዝጋሚ ለውጥ ትምህርት በየደረጃው በሰፊው የሚሰጥ ስለሆነ፥ በዚህ ክፍል ስለዚህ ፅንሰ-አሳብ ጥቂት አስተያየት መሰንዘሩ ብቻ በቂ ይሆናል። ይህ ፅንሰ-አሳብ ፍጥረት ሁሉ ከመጀመሪያይቱ “ሕዋስ” ቀስ በቀስ በተፈጥሮ ሂደት የተገኘ ነው ቢልም፥ የመጀመሪያዋ ሕዋስ ከየት እንደመጣች ግን አያመለክትም። በተወሰነ ደረጃ አንዳንድ ለውጦች መኖራቸውን ማንኛውም ክርስቲያን አይክድም። ነገር ግን የአዝጋሚ ለውጥ ፅንሰ-አሳብ ከዚህም የገዘፉ የለውጥ ትምህርቶችን ያካትታል። የቅርጽ፥ የዘርና ሌሎች ውስጣዊና ረቂቅ ለውጦች ሁሉ ያለ ፈጣሪ ተሳትፎ ይፈጸማሉ ብሎ ያስተምራል።
እንዴት ነው ይህ መሆን የሚችለው? እንደ አዝጋሚ ለውጥ እምነት አራማጆች (Evolutionists/ኢቮሉሽኒስቶች) አባባል፥ ይህ የሚከናወነው በሚውቴሽን (Mutation) ነው።
«ሚውቴሽን» ማለት በአንድ ድንገተኛ ሁኔታ የተነሳ በፍጥረታት ሕይወት መዋለድ ላይ የሚመጣ መላምታዊና ድንገታዊ ለውጥ ነው። በዚህም ረገድ ከወላጆቻቸው የተለዩ አዳዲስ ፍጡራን የሚፈጠሩ ሲሆን፥ አዲስ የሆኑት ልጆችም ራሳቸውን እንጂ አያት ቅድመ-አያቶቻቸውን የማይመስሉ ዘሮችን ይተካሉ።
ጠንካራ ጠንካራዎቹ በተፈጥሮ ምርጫ እየተጠበቁ በመቆየታቸው አዲስ የዘር ዓይነት ተገኘ እንደሚሉም ማስተዋል ይጠቅማል። በሂሳብ ጥበብ ቋንቋ ቀመሩ የሚከተለውን ይመስላል፦
{ሚውቴሽን} + {የተፈጥሮ ምርጫ} + {ጊዜ} = {አዝጋሚ ለውጥ}
አንድ ጸሐፊ ሲጽፍ፦ «ሜንደል (Mendel) በተባለ የለውጥ ተመራማሪ ለረዥም ጊዜ የታየው የለውጥ ሙከራ የተመሠረተው ሕያው በሆኑት ባሕርያት ላይ ብቻ እንጂ፥ አዳዲስ ባሕርያት በመፍጠር እንዳልሆነ ነው። ፍጹም የሆኑ አዳዲስ አካላት ማግኘቱን ያረጋገጠ ሙከራም የለም። ይሁን እንጂ በአዝጋሚ ለውጥ ትምህርት የዋናዎቹን የለውጥ ደረጃዎች ክልል የሚያመለክተው በፍጥረታት ውስጥ የአዳዲስ ባሕርያት መከሰት ነው» ብሏል።
ይህ መልስ ያላገኘ የአዝጋሚ ለውጥ እምነት አራማጆች መሠረታዊ ችግር ነው። እነዚህ አዳዲስ ነገሮች በምንም እኳኋን ይሁን በአዝጋሚ ለውጥ ተከስተዋል ብለው ማመን አለባቸው። ለምሳሌ አንድ እውቅ የሰው ዘር አመጣጥ ተመራማሪ (Anthropologist/አንትሮፖሎጂስት) የጀርባ አጥንት ያላቸው ፍጥረታት፥ አጥንት ከሌላቸው በእድገት እንደተገኙ ሲጽፍ፦ “ይህ በጣም ውስብስብ፥ ግልጥ ያልሆነና አሻሚ ጉዳይ ነው። ያም ሆነ ይህ አጥንት የሌላቸው እንስሳት በሆነ መንገድ የጀርባ አጥንት በማግኘት በኢቮሉሽን ተለውጠዋል” ብሏል። ይህ የግል እምነቱ ቢሆንም፥ የአስተሳሰብ ድክመት ይታይበታል።
የቅሪተ-አካል ዘገባም ከዚህ በፊት ሆነዋል የሚባሉ ነገሮችን ያመለክታል። አዝጋሚ ለውጥ ትክክል ቢሆን ኖሮ ለውጡ ሳይቋረጥ ከቀላል ወደ ውስብስብ የተሸጋገረበትን ሂደት ሊያመለክት ይገባ ነበር። ነገር ግን በቢሊዮን ከሚቆጠሩት የታወቁ ቅሪተ-አካላት ግኝቶችና ከፍተኛ የሕይወት ምድቦች መካከል ያለው ሽግግር ሆነ ተብሎ ተዘሏል! “አገናኞቹ ቀለበቶችም ከሚፈለጉበት ስፍራ ጠፍተዋል፤ ምናልባት ወደፊትም ብዙ አገናኝ ቀለበቶች ይጠፉ ይሆናል” በማለት አንድ ጸሐፊ ተናግረዋል።
2. መጽሐፍ ቅዱሳዊ የሰው አፈጣጠር ማስረጃዎች
መጽሐፍ ቅዱስ የሰውን አፈጣጠር አስመልክቶ በዝርዝር ስላሰፈረው ጉዳይ የተለያዩ አስተሳሰቦች ቢኖሩም፥ እውነተኛዎቹ ማስረጃዎች ግን በዚሁ መጽሐፍ ውስጥ ነው በግልጥ የሚገኙት። ዋና ዋናዎቹም ማስረጃዎች የሚከተሉት ናቸው፦
- ፩. እግዚአብሔር ፈጣሪ መሆኑ፦ እግዚአብሔር ፈጣሪ ስለመሆኑ በዘፍጥረት ምዕራፍ 1 ላይ ከአሥራ ሰባት ጊዜ በላይ ተገልጧል። እዚህ ላይ ትልቁ ጥያቄ «የቱ እግዚአብሔር?» የሚለው ነው። መልሱም ምዕራፉን የጻፈው ሰው ሙሴ የሚያውቀው እግዚአብሔር የሚል ይሆናል። ሙሴ በግሉ ማንነቱን፥ ሕያውነቱን፥ ተአምራት አድራጊነቱን የተረዳው አምላክ እግዚአብሔር ነው።
- ፪. የፍጥረት አደራረግ ሁኔታ፦ በዘፍጥረት መጽሐፍ ላይ የሰፈረው ቃል እግዚአብሔር ፍጥረታትን የፈጠረበትን ሁኔታ ይነግረናል። በዘፍጥረት 1፡1፥ 21 እና 27 ላይ ያለው ግስ፥ ከባዶ ነገር (Ex nihilo) እንደጀመረ ያስተምራል፤ ከዚያ በፊት ምንም አልነበረም። በዚህ ምዕራፍ እግዚአብሔር “ሠራ”፥ “ጠራ”፥ “አዘጋጀ”፥ “አበጀ”፥ “አደረገ”፥ “ወሰደ”፥ “ተከለ”… ወዘተ. የሚሉ ግሶች ይገኛሉ። በተጨማሪም ፍጥረታት “ቀን በቀን” ከመጀመሪያው (1፡1) እስከ መጨረሻው (2፡1) እንደተፈጠሩ ያመለክታል።
- ፫. የፍጥረት ቀናት ተከታታይነት፦ የፍጥረታትን መፈጠሪያ ጊዜ በተመለከተም በዘፍጥረት የተጠቀሰ ማረጋገጫ አለ። የቀኖች ተራ በዘፍጥረት 1:3 ይጀምራል። የነዚህን ቀኖች ትርጉም በተመለከተ አራት አመለካከቶች አሉ።
- በመጀመሪያ፦ እነዚያ ቀኖች እግዚአብሔር ስለ አፈጣጠሩ ሁኔታ ለሙሴ የገለጠባቸው ናቸው የሚል ግንዛቤ አለ። እንግዲህ እነዚህ “የመግለጥ ቀናት” ናቸው እንጂ ከመፍጠር ጋር ግንኙነት የላቸውም።
- ሁለተኛ፦ እነዚህ ቀናት ዘመናትን ነው የሚያመለክቱት (በብሉይ ኪዳን ቀን ረጅም ዘመንን ለማመልከት ተጽፏል፤ ኢዩ. 2፡31)። የምድር አፈጣጠር (Geological/ጂኦሎጂካል) ዘመናትም በቀላሉ በእነዚህ ይካተታሉ።
- ሦስተኛ፦ እውነተኛ ቀኖች ሲሆኑ (በ24 ሰዓት የሚለኩ) በመካከላቸው ሰፊ ክፍት ጊዜ አለ፥ ይህም የጂኦሎጂን ረጅም ዘመን ሊያጠቃልል ይችላል።
- አራተኛ፦ የፀሐይ ቀኖች ይባላሉ። እነዚህ ክፍተት የሌላቸውና ተከታታይ ናቸው። ይህም አመለካከት “ምሽትና ማለዳ” በሚለው ሐረግ ይገለጣል። በብሉይ ኪዳን ውስጥ የቁጥር ቅጽል ከ“ቀን” ጋር ሲጠቀስ ሁልጊዜ የሚያመለክተው እውነተኛውን የፀሐይ ቀን ነው። በዚህ አመለካከት መሠረት መሬት የተፈጠረችው በቅርብ ጊዜ ነው። ሰውም እንደቀሩት ሦስት ግምቶች ሳይሆን፥ ከሌሎቹ ፍጥረታት በኋላ በቅርብ ጊዜ መፈጠሩን እንረዳለን።(ማሳሰቢያ፦ ዘፍጥረት 1፡1 ከሌላው የምዕራፉ ክፍሎች ጋር ያለው ግንኙነትም አከራካሪ ሆኗል። አንዳንዶች ይህ ለመንደርደሪያነት ብቻ የሚያገለግል አረፍተ ነገር ነው ሲሉ፥ የቀሩት ደግሞ ቀደም ሲል ስለነበረና በኋላ ባልታወቀ ምክንያት ድምጥማጡ ስለጠፋ ፍጡር ነው የሚያወራው ይላሉ። ለዚህም የሚያቀርቡት ማስረጃ ቁጥር 2 ላይ የተጠቀሰውን ቃል ነው። ይህ ድንገተኛ የጥፋት አደጋ የተከሰተው በሰይጣን ውድቀት ነው ይላሉ። ይህ ጉዳይ ከዚህ ጥናታችን ጋር ቀጥታ ግንኙነት ያለው አይደለም።)
- ፬. የጥፋት ውኃ ውጤት፦ የጥፋት ውኃ ውጤት ያለጥርጥር ዛሬ የምናውቀውንም የዓለም ሁኔታ ለውጦታል፤ ስለዚህ ዓለም ከጥፋት ውኃ በፊት የነበራትን የተፈጥሮ ገጽታ ለመረዳት የጥፋት ውኃው ውጤት ሥዕል በማንም አእምሮ ሊኖር ይገባል። ይህ የጥፋት ውኃ በአንድ አካባቢ የተወሰነ ቢሆን ኖሮ፥ በዚያው አካባቢ ብቻ ነበር ለውጥ ሊያመጣ የሚችለው፤ መሬትን በሙሉ የሸፈነ ከነበረ ግን ውጤቱ እጅግ የተወሳሰበና ከግምታችን በላይ አስደንጋጭ ነበር ለማለት ይቻላል። እንዲህ ዓይነቱ ሁለንተናዊ ማጥለቅለቅ በጣም ብዙ ቅሪተ-አካላትን ሊተው እንደሚችል ይገመታል። ይህ ደግሞ በአንድ ዓመት ጊዜ ውስጥ የሚከናወን እንጂ፥ ጂኦሎጂያዊ ዘገባ እንደሚያመለከተው ረጅም ዓመታት የወሰደ ሂደት አይሆንም። ዓለም በሙሉ በውኃ ተጥለቅልቆ እንደነበር ማስረዳቱም ቀላል ነው። ስለ መርከቢቱም ግዝፈት በዘፍጥረት 7፡19-24 ላይ የተገለጠውን ልብ ይበሉ (ዘፍጥ. 6፡15)፤ መጥለቅለቁ የደረሰው በአንድ ክልል ብቻ ቢሆን ኖሮ፥ መርከብ አስፈላጊ ባልሆነ ነበር። ይህን የጥፋት ውኃ በ2ኛ ጴጥሮስ 3፡3-7 ላይ ማጤን ጠቃሚ ነው።
- ፭. የዕድገት ገጽታ (Apparent Age)፦ ፍጥረት ሁሉ በእግዚአብሔር ተፈጠረ እስከተባለ ድረስ፥ ከፍጥረታት አንዳንዶቹ ቀደም ሲል ረጅም ዕድሜ ያላቸው ይመስሉ እንደነበር መገንዘብ ያስፈልጋል። በዘፍጥረት ሂደት የአዳምና ሔዋን አፈጣጠር ሲታይ ጊዜ በሚጠይቅ የዕድገት ሂደት ያለፉ ቢመስሉም ገና ሲፈጠሩ ጎልማሳዎች ነበሩ። በኤደን የአትክልት ስፍራ ከነበሩት ዛፎች አንዳንዶቹ በጣም ትልልቆችና ረጅም ዕድሜ ያላቸው የሚመስሉ ነበሩ። ለምሳሌ ክርስቶስ በቃና ዘገሊላ የሠራው ወይን ጠጅ (ዮሐ. 2) ጣዕሙ የበሰለ ሲሆን፥ በእርግጥ ዝግጅቱ ጊዜ የፈጀ እንዳልነበረ እናውቃለን። የ 4000 እና 5000 ሰዎች የተመገቡት ምግብ ሁኔታም እንዲሁ ነው። ምግቡ ከደቂቃ በፊት የተሠራ ሲሆን፥ ሲበላ ግን ለብዙ ጊዜ የተሰናዳ ይመስላል።
- ፮. የታሪክ እውነታ ማረጋገጫ፦ እንደ ታሪክ እውነታ ሁሉ የፍጥረት ታሪክም በብዙ የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍሎች ተመዝግቦ እናገኛለን (ዘፀ. 20፡11፤ 1ኛ ዜና 1፡1; መዝ. 8፡3-6፤ ማቴ. 19፡4-5፤ ማር. 10፡6-7፤ ሉቃስ 3፡38፤ ሮሜ 5፡12-21፤ 1ኛ ቆሮ. 11፡9፤ 15፡22፣ 45፤ 2ኛ ቆሮ. 11፡3፤ 1ኛ ጢሞ. 2፡13-14 እና ይሁዳ 14ን ይመልከቱ)። አንድ ሰው በአንዳንድ ምክንያቶች ሳቢያ በዘፍጥረት 1-11 ከተጻፈው እውነተኛ ታሪክ ለመሸሽ ቢሞክር እንኳን፥ በመጽሐፍ ቅዱስ የተጻፉትን የፍጥረት ትምህርቶች (በተለይ የአዳምን ታሪክ) ሊያስወግድ አይችልም። ብዙዎች በዘፍጥረት ከ1-11 የሰፈረውን ታሪክ የሰው ምናባዊ ገለጣ ነው ይላሉ፤ እንዲያ ከሆነ ሌሎቹን ክፍሎች እንዴት ያብራሯቸው ይሆን?
3. ሰው ባለ ብዙ ገጽ ፍጡር ነው
በመሠረቱ ሰው ቁሳዊ (አካል) እና ቁሳዊ ያልሆነ (መንፈስ ወይም ነፍስ ያለው) ፍጡር ነው። ሁለቱም አሠራሮች የእግዚአብሔር ቀጥተኛ የፈጣሪነት ሥራ ውጤቶች ናቸው (ዘፍጥ. 2፡7)። እግዚአብሔር ሰውን በመልኩና በምሳሌው ፈጠረ (ዘፍጥ. 1:26፥ 5፡1)። ሰውን እጅግ ልዩ የሚያደርገው እግዚአብሔርን መምሰሉ ሲሆን፥ በኃጢአት ከወደቀ በኋላም ቢሆን ይህ አምሳያነቱ ሙሉ በሙሉ አልጠፋም። (1ኛ ቆሮ. 11፡7 እና ያዕ. 3፡9 ላይ የሰፈሩት ምክሮች ሰው የእግዚአብሔር አምሳያ መሆኑን ያረጋግጣሉ።)
ያ አምሳያነት ምንድነው? ለዚህ ጥያቄ ለዘመናት የተለያዩ መልሶች ሲሰጡ ኖረዋል። ከእነዚህም መልሶች ውስጥ የሰው የእግዚአብሔር አምሳያነቱ ከተፈጥሯዊ አካሉ ነው፥ ወይም ለሥነ-ምግባርና ለመንፈሳዊ ጉዳይ ባለው ችሎታ ነው (ችሎታው አሁንም ይኖረው ወይም ፈጽሞ ያጣው ይሆናል) የሚሉት ይገኙበታል። ምናልባት እውነቱ የብዙ ነገሮች ስብስብ በመሆኑ ይሆናል። ሰው የእግዚአብሔር አምሳል በመሆኑ ምድርን የመግዛት ሥልጣንና ሥነ-ምግባር የማስከበር ኃላፊነት ተሰጥቶታል፤ በኋላም ይህን ኃላፊነት በኃጢአት የተነሳ ተነጥቋል። ከዓለም ገዥነቱ ተሽሯል፥ በሥነ-ምግባሩም ተበላሽቷል። ያም ሆኖ ከፍጥረታት ሁሉ በእግዚአብሔር አምሳል የተፈጠረ እርሱ ብቻ መሆኑ ልዩ ያደርገዋል።
የሰው አካል (ቁሳዊው ክፍሉ) በጣም ብዙ ሥራ እንደሚያከናውን ግልጥ ነው። ማየት እንደ መስማት አይደለም። የስሜት ሥሮች አሠራር የተለያየና ራሱን የቻለ ቢሆንም፥ ከማየት፥ ከመስማትና ከሌሎችም ስሜቶች ጋር የሚያያዝበት መንገድ ይኖራል።
ቁሳዊ ያልሆነውንም የሰው ክፍል በዚህ ሁኔታ ማየቱ ምናልባት አስፈላጊ ይሆናል። ነፍስ፥ መንፈስ፥ ልብ፥ አእምሮ፥ ፈቃድና ሕሊና ቁሳዊ ያልሆኑ የሰው አካል ክፍሎች ሲሆኑ፥ በመካከላቸው ጥርት ያለ ልዩነት መፍጠሩ ያስቸግራል። ሰውን አካል፥ ነፍስና መንፈስ ነው ማለት በጣም ማቃለል ይመስላል። ምክንያቱም ነፍስና መንፈስ የሰውን ቁሳዊ ያልሆነ ክፍል በሙሉ ካለመግለጣቸውም በላይ ልዩነታቸው ሁልጊዜ ጉልህ ባለመሆኑ ነው።
- ለምሳሌ እግዚአብሔርን በፍጹም ነፍስህ ውደድ ተብሏል (ማቴ. 22፡37)።
- እንዲሁም “ነፍስን ከሚዋጋ ሥጋዊ ምኞት” የሚል ሌላ ጥቅስ እናገኛለን (1ኛ ጴጥ. 2፡11)።
- መንፈስ ጌታን ሊያከብር ይችላል (ሉቃስ 1፡46-47)።
- እንዲሁም መንፈስ እንደ ሥጋ እንደሚረክስ (2ኛ ቆሮ. 7፡1) ተጽፏል። በአንዳንድ ሁኔታዎች መንፈስ የሰውን ከፍተኛ አካል ያመላክታል (ሰዎች ሁሉ፥ ያልዳኑትንም ጨምሮ መንፈስ አላቸው፥ 1ኛ ቆሮ. 2፡11)።
“ልብ” (ደም የሚረጨውን የውስጥ አካል ማለት አይደለም) እንዲሁ የሰውን ቁሳዊ ያልሆነ ክፍል ሁሉ የሚያጠቃልል ይመስላል። የሰው ሕይወት የእውቀት ማኅደር እንደሆነም ተገልጧል (ማቴ. 15፡19-20)፤ ስሜታዊውን ሕይወት (መዝ. 37፡4፤ ሮሜ 9፡2)፥ ፈቃዳዊውን ሕይወት (ዘዳግ. 7፡23፥ ዕብ. 4፡7)፥ መንፈሳዊውን ሕይወት (ሮሜ 10፡9-10፤ ኤፌ. 3፡17) ሁሉ ያጠቃልላል።
ሕሊና በሰው ውድቀት የተጎዳ አካል ቢሆንም፥ አማኞችንም ሆነ የማያምኑትን ሰዎች ሊመራ የሚችል ውስጣዊ ምስክር ነው። ሮሜ 2፡15 እና 1ኛ ጢሞ. 4፡2ን በመመልከት በማያምኑት ሰዎች ውስጥ የሚታየውን ሕሊና ያስተውሉ። አማኙን በተመለከተ ግን ሕሊናው ከመንግሥት (ሮሜ 13፡5)፥ ከአሠሪው (1ኛ ጴጥ. 2:19)፥ ከወንድሞቹ (1ኛ ቆሮ. 8:7፥ 10፥ 12) ጋር መልካም ግንኙነት እንዲኖረው ይመራዋል።
በጌታ ደኅንነት ያላገኘ ሰው አእምሮ በአዲስ ኪዳን ውስጥ መልካም ያልሆነ ስም ተሰጥቶታል። የማይረባ (ሮሜ 1:28)፥ ከንቱ (ኤፌ. 4:17)፥ የረከሰ (ቲቶ 1:15)፥ የጨለመ (ኤፌ. 4:18)፥ በሰይጣን የታወረ (2ኛ ቆሮ. 4:4) ተብሏል። ይሁን እንጂ አንድ ሰው ክርስቶስን አዳኝ አድርጎ ሲቀበል፥ ሕይወቱንም ለጌታ ሲሰጥ የአእምሮ መታደስን ያገኛል (ሮሜ 12፡2)። ከዚያ በኋላ እግዚአብሔርን መውደድ እንችላለን (ማቴ. 22፡37)፤ የጌታን ፈቃድ እንረዳለን (ኤፌ. 5፡17)፤ በማስተዋል እናመሰግነዋለን (1ኛ ቆሮ. 14:15)።
የሰው ፈቃድ ሌላው በጣም ጠቃሚ የሆነና ቁሳዊ ያልሆነው የተፈጥሮ ክፍል ነው። ያልዳነ ሰው ፈቃድ መልካም ውጤት ይኖረው ይሆናል (ሐዋ. 27፡43)፤ የአማኞችም እንዲሁ ሊሆን ይችላል (ቲቶ 3፡8)፤ የዚህ ተቃራኒም ይሆን ይሆናል (1ኛ ጢሞ. 6:9፤ ያዕ. 4:4)።
እነዚህ ሁሉ ማብራሪያዎች ክርስቲያን ሁለት የተለያዩ ችሎታዎች ወይም ባሕርያት እንዳሉት ያመለክታሉ። ከመዳኑ በፊት ችሎታውን የሚጠቀምበት ራሱን ለማገልገልና ለማስደሰት ነው። ይህ አሮጌ ወይም የኃጢአት ባሕርይ ክፉ ለማድረግ ከመቻል አንጻር ብቻ አይደለም የሚተረጎመው፤ ከዚያ የላቀ ሊሆን ይችላል። ከአሮጌው ባሕርይ የመነጩ፥ ግን ያልከፉ ነገሮች አሉ። የአሮጌው ባሕርይ ዋና መለያ በድርጊቱ ሁሉ ራሱን ማዕከል ማድረግ ነው። በዳግም መወለድ ጊዜ እግዚአብሔርን ለማገልገል አዲስ ኃይል ወይም ባሕርይ ተሰጥቶናል (ሮሜ 6፡18-20፤ 2ኛ ጴጥ. 1:4፤ ኤፌ. 4:22-25ን ያጥኑ)።
4. የሁለቱ ተቃራኒ ባሕርያት ውጊያ (ምሳሌ)
አንድ ሰው ያሉት የሁለት ተቃራኒ ባሕርያት ግንኙነት በዚህ ወጣት ክርስቲያን ተገልጧል፦
«በልቤ ውስጥ ሁለት ትላልቅ ውሻዎች አሉ። አንደኛው ጥሩ ውሻ ነው፤ ይረዳኛል፥ እንክብካቤ ያደርግልኛል፥ ይጠብቀኛል። ሌላው ውሻ መጥፎና ከሃዲ ሲሆን ሁልጊዜ ችግር ውስጥ የሚጥለኝና የሚያሳዝነኝም ነው። እነዚህ ውሻዎች እርስ በእርሳቸው ይጠላላሉ። ሁሌም እየተጣሉ የበላይነትን ለማግኘት ይሞክራሉ። ነገር ግን ማናቸውም ቢሆኑ በመግደል ወይም አንዱ ሌላውን በማባረር ለማሸነፍ አይችሉም። ጥሩው ውሻ መጥፎውን አባርሮት ሰላም ለማግኘት ብችል እንዴት ደስ ባለኝ ነበር! ሕይወቴ በዚህ ቋሚ የሆነ ጦርነት በመሞላቱ የተረገምኩ ሆኛለሁ።»
አንድ ቀን መጋቢውን ስለዚህ ጉዳይ ጠየቅሁትና በጣም ጥሩ ምክር ሰጠኝ፦
“አእምሮህ ውስጥ የምትጨምረው ነገር ሁሉ ለአንደኛው ውሻ የሚሆን ምግብ ነው። የእግዚአብሔርን ቃል ያለማቋረጥ ብታነብ፥ መልካም ነገር ብታስብ እና የእግዚአብሔርን ፈቃድ ብትሻ ጥሩውን ውሻ መገብክ ማለት ነው። ነገር ግን ስለ ክፉ ነገሮችና ስለ ራስህ ብቻ ብታስብ ወይም ሰዎችን ለራስህ ጥቅም ለመጠጋት ብትሞክር የምትመግበው መጥፎውን ይሆናል” አለኝ። ቀጥሎም “አብልጠህ የመገብከው ውሻ ይበልጥ ጠንካራ ይሆናል፤ ድልም ያገኛል” አለ።
ምንጭ፦ “የመጽሐፍ ቅዱስ ሥርዓተ-ትምህርት ጥናት”፣ በዶክተር ቻርልስ ሲ. ራይሪ ተጽፎ፣ በሲሳይ ደሳለኝ የተተረጎመ እና በየላፕስሊ/ብሩክስ ፋውንዴሽን የታተመ ነው። ለዚህ ድንቅ አገልግሎታቸው እግዚአብሔር ይባርካቸው። ይህን ጽሑፍ ኮፒ እና ፕሪንት አድርጎ መጠቀም ይቻላል፤ ሆኖም ጽሑፉን መለወጥና ለሽያጭ ማዋል በሕግ የተከለከለ ነው።
