አንተ ግን ስትጸልይ፣ ወደ እልፍኝህ ግባ፣ መዝጊያህንም ዘግተህ በስውር ላለው አባትህ ጸልይ፣ በስውር የሚያይ አባትህም በግልጥ ይከፍልሀል፡፡ – ማቴዎስ 6፡6
ወደ እልፍኛችን ከገባንና በራችንን ከዘጋን በኋላ ልናደርግ የሚቸግረን ትልቁ ነገር ቢኖር መፀለይ ነው፡፡ አእምሮአችንን ለፀሎታችን ልንጠቀምበት በምንችለው ሁኔታ ማዘጋጀት አስቸጋሪው ሥራችን ይሆናል፡፡ የመጀመሪያ ውጊያችን የሚሆነው ሀሳባችንን ማሰባሰብና ለፀሎት ራሳችንን መግዛት ነው፡፡ በግል የፀሎት ጊዜ ያለው ታላቁ ጦርነት ሀሳባችንን ማሰባሰብና ለፀሎት ያልተዘጋጀውን አዕምሮአችንን ለዚሁ መንፈሳዊ ስራ እንዲነሳሳ ማድረግ ነው፡፡ ይህን ለማድረግ፣ በእግዚአብሔር ፊት በተመስጦ መሆን መማርና አዕምሮአችንን ማሰልጠን ይጠበቅብናል፡፡
ለፀሎት የተለየ ስፍራ ቢኖረን ይመረጣል፡፡ ያም ሆኖ ግን ወደዚህ ስፍራችን ስንገባ ሀሳባችን መባከኑ እንግዳ ነገር አይሆንም፣ ‹‹ይህ ነገር ዛሬ መሰራት አለበት››፤ ‹‹ያኛውን ደግሞ ነገ መጨረስ ይኖርብኛል፡፡›› የሚሉ ሀሳቦች በአዕምሮአችን መመላለስ ይጀምራሉ፡፡ በፀሎት ወቅት የተረጋጋ የአዕምሮ ሁኔታን ለመፍጠር፣ የአዕምሮአችንን ደጆች ለሚያንኳኩ ስሜቶቻችን ሆን ብለን ደጃችንን በመዝጋት፣ እርሱን ብቻ ማሰብ ይኖርብናል፡፡ እግዚአብሔር በስውር አለ፡፡ ከ ‹‹ስውር ስፍራውም›› ይመለከተናል፡፡ እርሱ የሚመለከተን፣ ሰዎች እኛን ወይም ራሳችን ራሳችንን እንደ ምንመለከተው አይደለም፡፡ እግዚአብሔር እኛን በሚያየን በዚህ ‹‹ስውር ስፍራ›› መኖር መለማመድ ስንጀምር እግዚአብሔርን መጠራጠር አይሆንልንም፡፡ ከማንም እና ከምንም ነገር በላይ ስለ እርሱ እርግጠኞች እንሆናለን፡፡ ወደዚህ ‹‹ስውር ስፍራ›› ስትገባ በእለት ተዕለት ሕይወትህ እግዚአብሔር በእርግጥ ትክክል እንደሆነ ታረጋግጣለህ፡፡ በሁሉም ጉዳዮች ላይ ከእግዚአብሔር ጋር የማውጋት ልማድ ይኑርህ፡፡ የማለዳው ጎህ ሲቀድ የሕይወትህን ደጆች ወለል አድርገህ ከፍተህ እግዚአብሔርን በፀሎት አስቀድም፡፡ ይህ ድርጊትህ በእርሱ ላይ ያለህን መደገፍ ያሳያልና፡፡ (My utmost for His Highest በ አስዋልድ ቻምበር የተጻፈ)